
ዛሬ የትግራይ ክልልን እንዲያስተዳድሩ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የተቀመጡት አቶ ጌታቸው ረዳ ከሚታወቁባቸው የሽፍትነት ዘመን ንግግራቸው መካከል “ዐቢይ ግድቡን ሸጦታል” የሚለው ነው። ዛሬ ደግሞ ከዶ/ር ዐቢይ ጋር ሆነው አራተኛውን ሙሌት ቦታው ድረስ በመሄድ አክብረዋል። ያኔ ተሸጧል ሲባል አብረው ያመኑና ዜናውን ያራገቡ መልስ ሊሰጡበት የሚገባው ጥያቄ፤
1ኛ. ግድቡ አልተሸጠም ነበር ወይም
2ኛ. የተሸጠው ተመልሷል ወይም
3ኛ ይህ አሁን ሞልቶ የሚታየው ግድብ ከተሸጠ በኋላ በአዲስ መልክ የተሠራ ነው።
መልሱን ለአቶ ጌታቸውና ደጋፊዎቻቸው እንተውና ኢትዮ12 ስለ አራተኛው ሙሌት በተመለከተ የዘገበውን ከዚህ በታች አቅርበነዋል።
ኢትዮጵያን ቋሚ ባለዕዳ የሚያደርገው የህዳሴ ግድብ ስምምነት ላይ መንግሥት የመፈረም ፍላጎት እያሳየች እንደሆነ ውስጥ አዋቂዎች እንደነገሯቸው ጠቅሰው የዘገቡ ነበሩ። እውነታው ግን ሌላ ነበር። “የኢትዮጵያን ጥቅም አሳልፈን አንሰጥም” ነበር የተባለው። አባይ ተገደበ። የህዳሴው ግድብ ሙሌት የውስጥ ከሃዲዎችና የውጭ የተቀነባበረ ጫናዎችን ባሸነፉ ጀግኖች የውሃ ሙሌቱን ተጠናቀቀ። ሕዝብ ደስታውን እየገለጸ ነው።
የዜናውን ብስራት የሰሙ “አቤት ሞገስ” በሚል እናቱ ከርስ ላይ ሞልቶ ለተኛው ውሃ የቅምጥል ስም ሰጥተዋል። አባይን ሲረግሙ የነበሩና ሮሮ ሲያሰሙ የነበሩ የኪነ ጥበብ ውጤቶችም ቃናቸውን ቀይረው ለህዳሴው ሞገስ የሚሰጥ ስራ እንዲያቀርቡ የጠየቁ ጥቂት አይደሉም። “ማልቀስና ማውገዝ የሚያስቀር” ሲሉ አዳዲስ የውዳሴና የስኬት ታሪክን የሚዘክሩ ስራዎችን በፍጹም ኢትዮጵያዊነት እንዲያቀርቡ ነው የተጠየቀው። ችግኝ ሲተከል ተነስተው እርግማን የሚያሰሙ “ወዴት ናችሁ” የሚያሰኘው የህዳሴው ገድል የጨዋ ኢትዮጵያዊያን የጥበብ ስራ ይጠብቃል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሜሪካ በፕሬዚዳንት ትራምፕ ተጽዕኖ ፈጣሪነትና በዓለም ባንክ እጅ ጠምዛዥነት ሲደረግ የነበረውን ድርድር አስመልክቶ “የህዳሴ ግድብ ስምምነት ፊርማ እንዲዘገይ አመራር ሰጥቻለሁ” ሲሉ ምስክሮች ያሉበትን ሃቅ ለፓርላማ ገልጸው ነበር። ዶ/ር ዐቢይ ረቂቁን ተመለከቱ፣ የትራምፕን፣ የዓለም ባንክ ፕሬዚዳንት እና የአሜሪካውን የገንዘብ ሚ/ር አነጋገሩ፤ ፍላጎታቸው ምን እንደሆነ በስልክ ንግግራቸው ተረዱ፤ ረቂቁ እንዳይፈረም ትዕዛዝ ሰጡ። እንዲያውም በውጭ አገር ከሚገኙ ኢትዮጵያውያን ባለሙያዎች የሚሰጣቸው የሙያ ምክር ጠቃሚ መሆኑን በመጥቀስ ምስጋና ሁሉ አቅርበው ነበር። ይህ ሊያስመሰግናቸውና ሲገባ “የህዳሴው ግድብ ላይ ክህደት ፈጸሙ” ተብሎ በትህነግ መሪነት ተዘመተባቸው።
የዛሬው የትግራይ ክልል መሪ አቶ ጌታቸው ረዳ “ዐቢይ የህዳሴ ግድብን ሸጦታል” በሚል የትህነግ “እረኛውን ምታ በጎቹ ይበተናሉ” ዘመቻ ማስፈጸሚያ አጀንዳ ተደርጎም ነበር። ኢንጂነር ስለሺ በቀለ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ተዕዛዝ በጫና የተጀመረው ንግግር እንዲቋረጥ መደረጉን አደባባይ ሲመሰክሩም የማጥላላትና የጥላቻ ዘመቻ የሚያካሂዱት ክፍሎችና “ሚስጥር ሰማን” ያሉት ዜናቸውንም ሆነ መረጃቸውን ለማረም ፈቃድ አላሳዩም።
በዝርፊያ ዳዋ የተመታው፣ እውቀት በሌላቸው ሲመራ የነበረውና የቅጥፈት ሪፖርት እየቀረበበት ሌቦች ተጋምደው ሲያርመጠምጡት የነበረው የህዳሴ ግድብ በዚህ ደረጃ እያለ ያልተነፈሱ አልነበሩም። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ኮሚቴ አቋቁመው ችግሩን በመግለጥ ዳዋው እንዲጸዳ አድርገው ስራው ሲጀመር ነበር ጎን ለጎን ስም ማጥፋቱ የተጀመረው።
በተለይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ላይ ትኩረት አድርጎ በቅብብሎሽ፣ በዲጂታል ወያኔ አዝማችነት ሲረጭ የነበረው ስም ማጥፋት በሕዳሴው ግድብ አራተኛና የመጨረሻ ሙሌት በተሳካ ሁኔታ መጠናቀቁን ባበሰሩት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ሰበር ዜና መታተሙ የአዲሱ ዓመት በረከት ሆኗል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) “ኢትዮጵያውያን ተባብረን በመሥራታችን ፈጣሪ ረድቶናል” ሲሉ በግል የማኅበራዊ ትሥሥር ገፃቸው ምስጋናቸውን ሁሉን ለሚያውቅና ሁሉን ቻይ ለሆነው አምላካቸው አቅርበዋል።
“በገንዘባቸው፣ በዕውቀታቸው፣ በጉልበታቸውና በጸሎታቸው በሥራው ውስጥ የተሳተፋችሁ ሁሉ እንኳን ደስ አላችሁ፤ ይህ ኅብረታችን በሌሎች ጉዳዮቻችንም ሊደገም ይገባዋል” ሲሉም “ህዳሴውን ግድብ ሸጡ፣ ኢትዮጵያን ባለዕዳ የሚያደርግ ስምምነት እንዲፈረም መመሪያ ሰጡ” በሚል የስም ማጥፋት ሲያካሂዱባቸው ለነበሩት ጭምር ጥሪ አቅርበዋል።
“ብዙ ፈተና ነበረው፤ ወደኋላ እንድንመለስ ብዙ ተጎትተን ነበር” ሲሉ እዚህ የተደረሰበትን መንገድ በጥቅሉ ያስታወሱት ዐቢይ አሕመድ፣ “በውስጥ ፈተና በውጭ ጫና ነበረብን፤ ከፈጣሪ ጋር የመጣውን ሁሉ ተቋቁመን ለዚህ ደርሰናል፤ ነገር ግን የዳገቱ ጫፍ ላይ ደረስን እንጂ ዳገቱን ወጥተን አልጨረስነውም” ሲሉ መከራና ድሉን አጣቅሰው፣ የወደፊቱን እርምጃ አመላክተዋል።
“በቀጣዩ ጊዜ ያቀድነውን አጠናቅቀን ፈጣሪን እንደምናመሰግን እምነቴ ነው ” ካሉ በኋላ “ለግድቡ የምናደርገውን ማናቸውንም ድጋፍ እስከ ፍጻሜው እንድንቀጥል በዚሁ አጋጣሚ አደራ እላለሁ” ሲሉም መልዕክት አስተላልፈዋል።
የህዳሴው ግድብ ግንባታ ዘጠና በመቶ ተጠናቋል። ቀሪው አስር በመቶ ብቻ ነው። ይህ በቅኝ ግዛት ወቅት በእንግሊዝ አደራዳሪነት በተደረገ የደባ ስምምነት ከኢትዮጵያ ተነጥቆ የነበረ ሃብት አራተኛውን ሙሌት ተጠናቅቆ ግድቡ አናት ላይ በኩራት ተኝቶ ማየት ልብን ያርዳል። አባይ ዘፈን መሆኑ ቀርቶ ሕይወት ሆኗል።
ግብፅ 66 በመቶ፣ ሱዳን 22 በመቶ ድርሻ እንዲቀራመቱና ኢትዮጵያ የውሃው ባለቤት ሆና ሳለ በዜሮ እጇን ታጥባ ያለ አንዳች ድርሻ እንድትቀመጥ ነበር የታቀደልን። በዚሁ አይን ያወጣ የዝርፊያ ክፍፍል ከግብጽና ሱዳን የተረፈው 12 በመቶ የሚሆነው ውሃው የሚተን ሆኖ ግምት የወጣለት ነው።
የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ አስጀምረውት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ፣ ሌብነቱን፣ የቴክኒክ ችግሩን ቀርፈው፣ ከውስጥ የጥላቻና የስም ማጥፋት ዘመቻውን ተቋቁመው፣ ከውጭ ባንዶች ጭምር የሚያሳድሩትን ጫና ተቋቁመው በሕዝብ ድጋፍ ህዳሴው ግድብ አፍ እስከ ገደፉ ሞልቶ ሲሽኮረመም አሳይተዋልና አገር ተደስቷል።
ሌት ከቀን ሰለቸኝ ሳይል ግንባታው እንዳይስተጓጎልና ተላላኪ ተምቾች ጉዳት እንዳያደርሱበት እንደ ንስር ነቅቶ ለጠበቀው የኢትዮጵያ መከላከያ ኃይል ዜጎች በማህበራዊ ገጾቻቸው ምስጋና አቅርበዋል።
የህዳሴውን ግድብ ለመገንባት የሚያስፈልገው ገንዘብ ቢለዋወጥም በወቅቱ ገበያ ቀደም ሲል ማለት ነው 80 ቢሊየን ብር (ከ4 ቢሊየን የአሜሪካ ዶላር በላይ) መሆኑ ተመልክቶ ነበር። ግድቡ 145 ሜትር ከፍታ አለው። ወደ ጎን ደግሞ 1 ሺህ 780 ሜትር ይረዝማል። የውሃ ኑክሊየር ማለት ይቻላል።
ግድቡ ይይዛል ተብሎ የሚጠበቀውን 74 ቢሊየን ሜትር ኪዩብ ውሃ ሙሉ በሙሉ ሲያከማች፣ የተጠራቀመው ውሃ የሚተኛበት አማካይ ስፍራ ርዝመቱ ከ246 ኪሎ ሜትር በላይ የደርሳል ተብሏል። ለዚህም ነው የህዳሴው ግድብ በቤኒሻንጉል ውስጥ የሚሰራ አንድ ትልቅ ከተማ የተባለው።
የዋናው ግድብ ውፍረት የግድቡ ግርጌ ላይ 130 ሜትር ሲሆን፤ የግድቡ ጫፍ ወይም የላይኛው ክፍል ደግሞ 11 ሜትር ነው። ግድቡ የሚሸፍነው የቦታ ስፋት ደግሞ 1 ሺህ 680 ስኩዌር ኪሎ ሜትር መሆኑን የግድቡ ጽሕፈት ቤት ቀደም ባሉት ዓመታት ማስታወቁ ይታወሳል። ግድቡ ሲጠናቀቅ ውሃ የሚተኛበት መሬት ርዝመት 246 ኪሎ ሜትር ነው።
የህዳሴው ግድብ በርካታ ደሴቶች ባለቤት እንደሆነ የተገለጸ ሲሆን፣ የቱሪስት ኢንዱስትሪ እንደሚስፋፋበት ተመልክቷል። ራሱን የቻለ አገር እንደሆነ የሚነገርለት ይህ ግድብ የአሳ ምርት መጀመሩም ታውቋል። ሁለት ተርባይኖች ኤሌክትሪክ ማምረት የጀመሩ ሲሆን በቅርቡ በሙሉ ኃይሉ የኤሌክትሪክ አቅርቦቱን ያሳድጋል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ 6450 ሜጋዋት ኃይል የማምረት አቅም አለው። ከዚሁ ሃይል ውስጥ ለአገር ውስጥ ፍጆታ ከሚውለው ውጭ 2000 ሜጋዋት ሃይል ለጎረቤት አገራት የሚሸጥ ነው። ከዚህ ሽያጭ በወቅቱ ገበያ በዓመት እስከ 600 ሚሊዮን ዶላር ገቢ እንደሚገኝ ከሶስት ዓመት በፊት ተገልጾ ነበር።

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply