በሰሜን ኢትዮጵያ በድጋሚ ግጭት ለመቀስቀስና ቀጣናዊ ሰላምን ለማደፍረስ ከሻዕቢያ ጋር ጽምዶ ፈጥሮ አደገኛ እንቅስቃሴ ላይ በሚገኘው ትህነግ (ህወሃት) አመራሮችና በቅርብ የቤተሰብ አባላቶቻቸው ላይ ያነጣጠረ የቪዛ እገዳ መጣሉን ተከትሎ የአሜሪካ መንግስት በይፋ አስታውቋል።
ይህ ውሳኔ ይፋ የሆነው በኢትዮጵያ ውስጥ በሕጋዊ መንገድ ተመዝግቦ የመንቀሳቀስ ፍቃዱ የተሰረዘውና ሕገወጥ ተብሎ የተፈረጀው የትህነግ ታጣቂ ኃይል ከመከላከያ ሠራዊት ጋር በቅርቡ በፈጠረው ቀጥተኛ የጦርነት ትንኮሳ ሳቢያ ነው።
ትህነግ በተደጋጋሚ በቆሰቆሰው የሰሜኑ ጦርነት አንድ ሚሊዮን ያህል የንጹሃን ዜጎች ህይወት መጥፋቱ እንዲሁም በብዙ ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ወገኖች ለከፋ ረሃብና ለስደት መዳረጋቸው እየታወቀ ራሱን የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጪ ግምባር ብሎ የሚጠራው አሸባሪ አሁንም ለሰላም እያሳየ ያለው እምቢተኝነት ዋሽንግተንን ብቻ ሳይሆን ሁሉንም ወገኖች በእጅጉ ያሳሰበ ጉዳይ ሆኗል፤ መግለጫውም የአሜሪካንን ስጋት በዚሁ ልክ ገልጿል። ሲቀጥልም፤ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የሰሜን ኢትዮጵያ ነዋሪዎች ጦርነቱ በድጋሚ ሊቀሰቀስ ይችላል ከሚል ከፍተኛ ስጋት የተነሳ አሁንም ቀያቸውን ጥለው እየተሰደዱ ይገኛሉ ብሏል።
የዩናይትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ በመ/ቤታቸው ድረገጽ ባወጡት ይፋዊ መግለጫ መሠረት ይህ የቪዛ እገዳ በትግራይ ክልል ያለውን ቀውስ በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት የሚደረገውን ጥረት በሚያደናቅፉ ግለሰቦች ላይ በቀጥታ ተፈጻሚ ይሆናል።
አሜሪካ በሰላምና በክብር መኖር ከሚፈልገው መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ በተለይም ደግሞ በስቃይ ውስጥ ካለው የትግራይ ህዝብ ጎን በጽናት እንደምትቆም በመግለጫው ገልጻለች። ዋሽንግተን በሰጠችው መግለጫ “የአሜሪካ መንግሥት ሰላምንና ቀጣናዊ መረጋጋትን አደጋ ላይ የሚጥሉ የትህነግ ባለሥልጣናትን እና ሌሎች ግለሰቦችን ድርጊት በይፋ ለማጋለጥና ተጠያቂነትን ለማስፈን በእጁ ያሉትን መሣሪያዎች ሁሉ መጠቀሙን ይቀጥላል” በማለት ጉዳዩን በጥብቅ ትኩረት እንደምትከታተለው በይፋ አረጋግጣለች።
በተያያዘም ይህ የአሜሪካ መንግሥት ቀጥተኛ እርምጃ በቅርቡ በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ በአንዳንድ ወገኖች ሲሰራጭ የነበረውንና የኢትዮጵያን ዲፕሎማሲያዊ ሚና ለማሳነስ የሚሞክሩ መሠረተ ቢስ ወሬዎችን ሙሉ በሙሉ ውድቅ ያደረገ ሆኗል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በጂ ሰባት (G7) ስብሰባ ላይ አለመገኘታቸውን ተገን በማድረግ ኢትዮጵያ በቀጣናው በኬንያና በግብፅ ተበልጣለች የሚሉ የባንዳ ትረካዎች ቢሰሙም ይህ አዲስ የቪዛ ማዕቀብ ግን ዋሽንግተን ለአፍሪካ ቀንድ ሰላምና መረጋጋት በዋናነት የምትነጋገረውና የምትወስነው ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር ብቻ መሆኑን ያረጋገጠ ነው።
አሜሪካ የትህነግን ህገወጥ ትንኮሳ በይፋ በማውገዝ የወሰደችው ይኸው እርምጃ የኢትዮጵያ መንግስት ህግን ለማስከበርና ሉዓላዊነቱን ለመጠበቅ የሚያደርገውን ጥረት በተዘዋዋሪ የሚደግፍና የአገሪቱን ቀጣናዊ መሪነት በድጋሚ ያረጋገጠ ታላቅ የዲፕሎማሲ ድል ተደርጎ ተወስዷል።
መግለጫው በዋቢነት በጠቀሰው 212(a)(3)(C) የሚለው (Immigration and Nationality Act) የሕግ አንቀጽ መሠረት፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ መመሪያ ካስተላለፉ በኋላ የሚቀጥሉት ተግባራዊ እርምጃዎች ይወሰዳሉ።
በቅድሚያ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከደኅንነትና ከዲፕሎማሲ አካላት ጋር በመተባበር፣ በዚህ ማዕቀብ ውስጥ የሚካተቱትን የትህነግ አመራሮችንና የቅርብ የቤተሰብ አባላቶቻቸውን ትክክለኛ የስም ዝርዝር የማጠናቀር ሥራ ያከናውናል።
በቀጣይ በዓለም ዙሪያ የሚገኙ የአሜሪካ ኤምባሲዎችና ቆንስላዎች በዝርዝሩ ውስጥ ያሉትን ግለሰቦች አዲስ የቪዛ ጥያቄ እንዳይቀበሉ፤ ውድቅ እንዲያደርጉ መመሪያ ይደርሳቸዋል። በተጨማሪም፣ እነዚህ ግለሰቦች ቀደም ብለው የያዟቸው ሕጋዊ የአሜሪካ ቪዛዎች ካሉ በሙሉ ይሰረዛሉ።
ይህ እርምጃ የተወሰደው በውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ላይ የሚመጡ አሉታዊ ተፅዕኖዎችን ለመከላከል በተደነገገው ሕግ መሠረት በመሆኑ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሩ የተከለከሉትን ቪዛዎችና የተጠበቁትን ብሔራዊ ጥቅሞች በተመለከተ በአስቸኳይ ለአሜሪካ ኮንግረስ ይፋዊ ሪፖርት ያቀርባል። ይህም የአሜሪካ መንግሥት ያጸደቀው በፕሬዚዳንት መለዋወጥ የማይቀየር ሕጋዊ ሰነድ ሆኖ በቋሚነት ይቀመጣል።
በአጠቃላይ ይህ የአሜሪካ መንግሥት ውሳኔ በሕገወጥነት ለሚንቀሳቀሱና የሰላም አማራጮችን ለሚያናንቁ የትህነግ አክራሪዎች ግልጽና የማያሻማ የማስጠንቀቂያ መልእክት ያስተላለፈ ነው። ከትህነግ ጋር ትሥሥር ያላቸውና በትህነግ ላይ ተንጠልጥለው አገር እያፈረሱ ያሉ ኃይሎች ውጤቱ ደረጃውን ጠብቆ ይደርሳቸዋል።
ማዕቀቡ በኮንግረሱ መዝገብ ላይ በቋሚነት እንዲቀመጥ መደረጉ እርምጃው የረጅም ጊዜና ወደኋላ የማይመለስ መሆኑን የሚያሳይ ሲሆን፣ ለዓመታት በአገር ውስጥና በዲፕሎማሲው መድረክ ሲሸረቡ የነበሩ የጥፋት ሤራዎችንም ሙሉ በሙሉ ያመከነ ነው። ውሳኔው የኢትዮጵያን ብሔራዊ ሉዓላዊነትና የሕግ ማስከበር እርምጃ በተግባር ከመደገፍ ባሻገር፣ አገሪቱ ለአፍሪካ ቀንድ አስተማማኝ ሰላምና መረጋጋት ብቸኛዋና ዋነኛዋ የዋሽንግተን ስትራቴጂካዊ አጋር መሆኗን ለዓለም ማኅበረሰብ በድጋሚ ያረጋገጠበት ታሪካዊ ምዕራፍ ሆኖ ይመዘገባል።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ



Leave a Reply