
* ዳያስፖራው ራሱን ከትግሉ እያገለለ ነው
ከሚያዚያ 6 ቀን 2018 ዓም ጀምሮ በተደረገ ተከታታይ ስምሪት የፋኖ ኃይል እጅግ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰበት ተገለጸ። በተለይ በራያ ቆቦ ወረዳ የተደረገው ሥምሪት ባካባቢው በሚገኘው የፋኖ ኃይል የደረሰው ጉዳት መጠነ ሰፊ እንደሆነ ተመልክቷል። በፋኖ ተስፋ የቆረጠው ዳያስፖራ ከሚኖርበት ሀገር የገጠመው ችግር ተጨምሮ ለፋኖ የሚሰጠውን ድጋፍ እየቀነሰ ነው።
እስከ ዛሬ ድረስ በራያ ቆቦ ወረዳ በአማያ፣ በባይባዋ፣ በፀበለት እና አካባቢው በተደረገው ተከታታይ ስምሪት የመከላከያ ሠራዊት በፋኖ ላይ ባደረሰው ከፍተኛ ምት ንብረቱን፣ ትጥቁን እና ተተኳሹን በመተው ከአካባቢው ሲለቅቅ የሰሜን ምስራቅ ዕዝ 802ኛ ኮር አካል የሆነው 48ኛ ክፍለ ጦር በተጠቀሱት ቦታዎች እና ልዩ ሥፍራው “አካምባ” በሚባል ቦታ ፈጥኖ በመድረስ የፋኖው ኃይል ጥሎት እና አንጠባጥቦት የሸሸውን ንብረት በቁጥጥር ሥር አውሏዋል።
በዚህም መሠረት፦
የ82 ሚ/ሜ ሞርተር ጥይት – 515
የ82 ሚ/ሜ ሞርተር ፊውዝ – 520
የ82 ሚ/ሜ ሞርተር ካምሱር – 43
የ12.7 ሚ/ሜ ዶሽቃ ጥይት – 818
የመትረዬስ/ብሬን ጥይት – 47080
ቆመህ ጠብቀኝ መሣሪያ – 48
የተተካይ ክላሽ ብሬን – 1
የኤኬኤም ክላሽ ማፅጃ – 137 የተገኘ መሆኑን መረጃው ይጠቁማል።
ከውስጥም ከውጪም ከፍተኛ የመበታተን አደጋ የተጋረጠበት የፋኖ ኃይል እየደረሰበት ያለውን ጫና መቋቋም እያቃተው እንደሆነ ይሰማል። በፊት ላይ በሚሊዮን የሚቆጠር ዶላርና ዩሮ በቀላሉ ለመሰብሰብ ይችል የነበረው የውጪው ደጋፊ በተለያዩ ምክንያቶች እጁን ወደ ኪስ ማስገባት እየቸገረው መጥቷል። ከፋኖ እየከዳ ለመንግሥት እጁን የሚሰጠው ሠራዊትና አመራር ጉዳይም ሌላው ተስፋ አስቆራጭ ሆኗል።
በተለይ በቅርቡ በማኅበራዊ ሚዲያ ሲሰራጭ የታየና ለፋኖ የገቢ ማሰባሰቢያ ተብሎ የተጠራ ስብሰባ “በቂ ሰው ስላልተገኘ” በሚል መበተኑ ተበትኗል። በሥፍራው የነበሩና በሁኔታው እጅግ የተናደዱ ሰዎች በስብሰባ ጠሪዎች ላይ ጥቃት ለመሰንዘር እንደሞከሩና ይህንን የተመለከቱትም ወዲያውኑ ጸጥታ አስከባሪ በመጥራት ሁኔታውን ለመቆጣጠር ችለዋል።
ሰለሞን ቦጋለ የተባለ ግለሰብ የፋኖ ደጋፊ መሆኑ ተጠቅሶ ወደ ኢትዮጵያ ከተጠረዘና በተለይ በዚሁ ዜና ላይ ፋኖ ሦስተኛ ደረጃ አሸባሪ ተብሎ ከተጠቀሰ በኋላ የፋኖ ደጋፊ ደብቁኝ እያለ መምጣቱ በገሃድ የሚታይ ሐቅ ሆኗል። የትራምፕ አስተዳደር የአሜሪካ ዜግነት ያላቸውን ጭምር ዜግነታቸውን እየገፈፈ ወደ መጡበት ሀገር መመለስ መጀመሩ በማንኛውም ቡድን የዳያስፖራ ደጋፊ ዘንድ ከፍተኛ ሽብር ፈጥሯል።
በተለይ ዱሮ ሶማሌያዊ ነኝ፣ የመናዊ ነኝ፣ ሱዳናዊ ነኝ እያሉ አሜሪካ ጥገኝነት የጠየቁና ዜግነት ያገኙ በርካታዎች ሊመለሱ የሚችሉበትን ሀገር ሲያስቡት የፈጠረባቸው ጭንቀት እጅግ ከፍተኛ እንደሆነ ይፋ ያልሆኑ በየአካባቢው በሚደረጉ ኢመደበኛ ስብሰባዎች ላይ የሚሰማ ትርክት ሆኗል። የገቢ ማሰባሰቢያ ስብሰባዎች መሰረዛቸውና በአካል የሚደረጉ ሰላማዊ ሰልፎች ወደ ድረገጽ ትዕይንት መቀየራቸው ከዚሁ ጋር የተያያዘ እንደሆነ በስፋት ይሰማል።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ



Leave a Reply