
ጎንደር ወዴየት እየሄደች ነው? ጎንደር እስከመቼ በውሸት ሪፖርት ትደበቃለች? መቼ ነው በጎንደር የጃኖ ስጦታ እና የዶሮ ፖለቲካ የተሸፈነችበት ጭምብል የሚገለጠው? ይህ መሠረታዊ ጥያቄ ምላሽ ያሻዋል።
የጎንደር የፖለቲካ አመራር ራሳቸውን ለሥራ ያተጉ፣ ተግባራቸውን በወቅቱ የሚከወኑ ለመምሰል የሚያሳዩትን ድራማ እስከመቼ ነው የሚገፉበት? እስከመቼ ነው ዝምስ የሚባሉት?
ጎንደር ለሚመጡ ባለሥልጣናት የባሕል አልባሳትን በማልበስና የጎንደርን ዶሮ በመጋብዝ ታታሪ መምሰል፣ ከዚያም በላይ “ወደ ቤት የምትወሰዱት” በማለት በአገልግል ዶሮ፣ በጀሪካ ቅቤና ማር እየሞሉ ውለታ ማስቀመጥ ፖለቲካ ሳይሆን፣ አድሮ መንግሥትን ዋጋ የማስከፈል ጉዳይ እንደሆነ እንዴት ይዘነጋል?
መቼ ነው የጎንደር ባለሥልጣናት ከጃኖ ስጦታና አገልግል ቋጠራ የውለታ ፖለቲካ በመውጣት የሚያስተዳድሩትን ሕዝብ በቅጡ የሚመሩት? የሚጠብቁት? ያለ ስጋት እንዲኖር የሚያደርጉት?
ሙስሊም ክርስቲያን ሳይል ከመንግሥት ጎን የቆመ ሕዝብ በአስተዳደር ድክመት ለምን መከራ ያያል? ከውስጥ ሆነው በጥቅም ትሥሥርና ሚሊሻ ጨምሮ በስሙ ከሸፈቱ ጋር ውስጥ ሆነው ሽፋን በመስጠት ንጹሐን እንዲገደሉ የሚደረገው እስከመቼ ነው።
ከትላንት በስቲያ በጎንደር ኡስታዝ መሐመድ ዘይኑ ላይ የተፈጸመው ግድያ፣ የአንድ የሙስሊም ሞት ተደርጎ የሚታይ አይደለም። ይልቁኑም አብሮ በሚበላ፣ በሚጠጣና በማኅበራዊ ሕይወቱ ከቶውንም የማይነጣጠለውን የሙስሊምና የክርስቲያን ማኅበረሰብ ለማጋደል የተደረገ ሤራ ነው።
ከዛሬ አምስት 5 ዓመት በፊት በሁለቱ ዕምነት ተከታዮች መካከል ተፈጥሮ የነበረውን ችግር በጥበብና በማስተዋል ከፈቱት መካከል እኚሁ አሁን የተገደሉት ኡስታዝ ቀዳሚው ናቸው። ቁርሾ እንዳይኖር፣ ትክክለኛ ዕርቅ እንዲወርድ ትልቁን ሥራ የፈጸሙት መልካም ሰው ኡስታዝ ግድያን ከተራ ዝርፊያ ጋር ማገናኘት እናንተ በጃኖና በዶሮ ወጥ ስጦታ የምትታወቁትን አመራሮች ነጻ አያደርጋችሁም።
ደግነቱ በሁሉ ሕዝብ እገሌ ከእገሌ ሳይባል፣ ቀብራቸው ላይ በመገኘት የዶሮ ፖለቲካ ለሚጫወቱት ሁሉ፣ በጨዋ ደንብ ትምህርት ሰጥቷቸዋል። ለኡስታዝ ነፍስ ይማር እያልኩ መንግሥት ከሰማ የሚከተለውን ለማለት እወዳለሁ።
አድማጭ፣ የሚሰማ መሪ ከተገኘ፣ ብልጽግና ሆይ እባክህ ሁሉንም ነገር በቁጥጥራቸው ሥር ያደረጉና በዝረፊያ የካበቱትን የዶሮ ፖለቲካ ዥዋዠዌ ተጫዋቾችን አጥራ። በርካታ የሚነሱ ጉዳዮች አሉና ጥልቅ ማጣራት ተደርጎ ጎንደርን የማጽዳት ሥራ እንዲሠራ ለማሳሰብ እወዳለሁ።
የከተማዋን ፖለቲካዊና ኤኮኖሚዊ ተግዳሮቶች አቻችለውና አሳልጠው ይመራሉ የተባሉ አመራሮች ሕልማቸው ወሳኝ የገቢያ ማዕከሎች በኮሪደር ስም በማስተከል ወንድምና እህቶቻቸውን አደራጅቶ ማስገባት ሆኗል። ይህ ነው ሕዝብን ተጠቃሚ አድርገናል እየተባለ በጃኖና ዶሮ ፖለቲካ ታጅቦ የቅጥፈት ሪፖርት የሚቀርበበት ሐቅ።
አንዳንድ ባለሃብቶችን ጽንፈኛ ነህ ብሎ በማሰር ገንዘብ መቀበል፣ ገንዘብ ተቀብሎ መልቀቅ፣ በመንግሥት ድጋፍና መዋጮ ሰበብ ራሰን ማበልጸግ የተለመደ ባሕል ሆኗል።
ግድያን ማጥፋት፣ ሰላምን ማስፈንና ሕዝብ በእርጋታ እንዲኖር ማድረግ ጉዳያቸው ስላልሆነ ነገም ከነገ ወዲያም በተመሳሳይ መልኩ ግድያው ላለመቀጠሉ ዋስትና የለም። እኛም “እገሌ መልካም ሰው ነበር” ብለን ከንፈር ከመምጠጥ ውጪ አማራጭ አይኖረንም።
ዛሬ ላይ የተገደሉት የሃይማኖት መሪ ቀደም ሲል ተለኩሶ የጠፋው እሳት ዳግም ማቀጠጠያ ክብሪት ናቸው። ትላንት የነበረውን ቁርሾ እንደያጠፋ ታቅዷል። ድርጊቱ በዕቅድ የተከነወነ ተግባር ነው። ዓላማው በሁለቱ ሃይማኖቶች ምዕመን መካከል ግጭት በመፈጠር ከተማውን ለዝርፊያ ማዘጋጀት ነው።
አሥራ አንድ ምዕመን ሞባይል ብቻ በመዘረፉ መምህሩን ነጥሎ መግደል ዓላማው ግልፅና የማያሻማ ነው። የዚህ ሁሉ ጥፋት ተጠያቂዎች በአገልግል ዶሮ ፖለቲካ ሚኒስትር ለመሆን የሚሽቀዳደሙት የመዋቅሩ አካላት እንጂ ሌላ ማንም አይደለም።
መንግሥት ሆይ! ይህ የመጨረሻ የማንቂያ ደወል ይሁን። ይህን ጉዳይ ከሥሩ ማጽዳት ለነገ ሊባል አይገባም። ይህ ጉዳይ ከሥሩ ካልተበረበረና ተመሳስሎ የተሰገሰገው የውሰጥ አመራር ካልተፈተሸ ሀገር የጃርት መዋያ መሆኗ አይቀርም።
ጎንደር በብዙ ፈተናዎች ተፈትና አልፋለች። የጎንደር ልባም ሕዝብ ሁሉንም መከራ እንደ አመጣጡ አሳልፏል። ይህ የሚያማቸው እያደር የጥፋት ድግሳቸውን ከዶሮ ፖለቲከኞች ጋር ሆነው ይደግሳሉ። ዛሬ ጎንደር ስስ በሆነችበት ሃይማኖት ጉዳይ ነገር በማቀጣጠል ውድቀትን ማፋጠን እንደ ሀገር አይጠቅምም።
እነዚህ አዝማሪ ደርድረው፣ የባሕል ልብሰ አልብሰው፣ ዶሮ ጋብዘው፣ ዶሮ በአገልግል፣ ማር እና ቅቤ በጀሪካን የሚሸከሙት የመንግሥት ባለሥልጣናት እውነት ለምን ይህ ችግር ተፈጠረ? እስከ አሁንስ ለምን ጊዜ እየጠበቀ ያመረቅዛል? ብለው ይፈትሹ። እውነታው የውሸት ሪፖርት እና በዶሮ ፖለቲካ ሚኒስትር የመሆን ሕልም ውጤት ሆኖ ታገኙታላችሁ!!
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ


Leave a Reply