
- ሀገር ሙሉ ሕዝብ በሴፍቲኔት እየተረዳ አይደለም
- የዓለም ባንክ የሰጠው ዕርዳታ ለ700 ሺህ ሕዝብ ብቻ የሚውል ነው
ሰላሳ ዓመት ሞላኝ የሚለውና ብዙዎችም የሚዲያ ጽናት፣ አውራ፣ ወዘተ እያሉ የሚጠሩት አውሬው ሪፖርተር ሀገር ለማፍረስ ቀስ እያለ በመሸርሸር ሥራ ላይ እንደተሠማራ ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በተደጋጋሚ በርካታ መረጃዎች አውጥቶበታል፤ ማውጣቱንም ይቀጥላል።
አፍቃሪ ትህነግ የሆነው ሪፖርተርና ባለቤቱ አማረ አረጋዊ ዜና መቀሸብ የተካኑበት ሞያቸው ነው። አካሄዱ ግልጽና ጽንፈኛ የመቃወም ስልት የተከተለ ሳይሆን እንደ ምስጥ ከውስጥ የመቦርቦርና ቀፎ አድርጎ የማስቀረት ነው። በዚህ ስልት የሚዘገቡትን የዜና ዘገባዎችን ማሰራጨት ለሪፖርተር አይጠበቅበትም፤ አፈ-ሰማይ የሆነው የማኅበራዊ ሚዲያ ተቀላቢ፤ ይህ ሁሉንም ማለትም በመንግሥትም፣ በግልም፣ በግብፅም፣ በሻዕቢያም፣ ወዘተ የሚቀለቡትን የሚጨምር ነው፤ በሙሉ ዜናውን ያላንዳች ችግር በማሰራጨት ለሪፖርተር በትጋት ይሠራሉ።
ከሁለት ሳምንት በፊት የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ በሴፍቲ ኔት ለሚታገዙ የሚውል 200 ሚሊዮን ዶላር ማጽደቁን ይፋ አድርጎ ነበር። ሪፖርተር ይቺን ዜና ያቀረባት ልክ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ በሴፍቲ ኔት እየተረዳ እንደሆነ በማስመሰል ነው። የሰጠው ርዕስም፤ “የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ ለሴፍቲኔት ፕሮግራም የሚውል የ200 ሚሊዮን ዶላር ብድር ማፅደቁን አስታወቀ” የሚል ነበር። ይህንን የሪፖርተር መረጃ ብስራት fm፣ አዲስ ስታንዳርድ፣ ጌጡ፣ ወዘተ ተቀባብለውታል፤ አቀባብለውታል።
ገንዘቡን የሰጠው የዓለም ባንክ እንኳ በዚህ ልክ ልበ-ሙሉነት ርዕስ አልሰጠውም። በባንኩ ድረገጽ ላይ የወጣው መረጃ የተሰጠው ርዕስ እንዲህ የሚል ነው፤ Ethiopia: A New Phase of Support for Safety Nets will Foster Resilience and Create Pathways to Decent Jobs.
ይህ የዓለም ባንክ ዕርዳታ የሪፖርተር ባለቤት የሆነው ትህነግ ኢትዮጵያን ሲግጥ በነበረበትም ጊዜ ሲሰጥ የኖረ ነው። የዛሬ 14 ዓመት የተሰጠውን ዕርዳታ ብቻ ብንመለከት ለማኅበራዊ ሴፍቲ ኔት ብቻ ባንዴ 370 ሚሊዮን ዶላር ነበር የሰጠው። የዋለውም ባጠቃላይ ለ8.3 ሚሊዮን ዜጎች ሲሆን:
- ከዚህ ውስጥ ሥር የሰደደ የምግብ ዕጦት ለደረሰባቸው 7.6 ሚሊዮን ዜጎች
- ከተሰጠው ውስጥ 70 ሚሊዮን ዶላር ደግሞ በአፍሪካ ቀንድ በደረሰው ድርቅ ለተጎዱ
- ሴፍቲኔቱ የሚያካልላቸው ወረዳዎች 319፤ ክልሎቹም አፋር፣ አማራ፣ ድሬዳዋ፣ ሐረሪ፣ ኦሮሚያ፣ ሶማሊ፣ ደቡብ ሕዝብና ትግራይ ናቸው።
ያሁኑስ ገንዝብ? ስንት እና ለምን ተግባር እንዲሁም ለነማን ነው የሚውለው?
- የተሰጠው ገንዘብ ሁለት መቶ (200) ሚሊዮን ነው
- የሚውለው ለ700 ሺህ ዜጎች ነው
- ዓላማው ለሥራ ፈጠራ ለሚውሉ ፕሮጀክቶች፣
- ለምግብ ደኅንነት
- የአየር ንብረት ለመቋቋም (በቅርቡ በጋሞ ለደረሰው አደጋ አስቀድሞ መከላከያ ሊውል ይችላል)
- በኑሮ ውድነት ምክንያት ለችግር ተጋላጭ ለሆኑ ቤተሰቦች ነው።
በአጠቃላይ ገንዘቡ የሚውለው ዜጎችን ከተረጂነት በማላቀቅ በዘላቂነት ራሳቸውን የሚችሉበትን መንገድ ለማመቻቸት ወይም በሁለት እግራቸው እንዲቆሙ ለማገዝ ነው። እንጂ ከትህነግ ዘመን ጀምሮ እስካሁን ድረስ ለኅሊና በሚሰቀጥጥ ትህነግ በሴፍቲኔት እያሰቃየ እንዳለው የትግራይ ወገናችን በድህነት እንዲቀጥል ለማስደረግ አይደለም።
እንዲያውም በትክክል ከተሠራ የዜናው ዋና ርዕስና ሐሳብ መሆን የነበረበት ሌላ ነው። ከላይ እንደተገለጸው የዛሬ 14 ዓመት ለ8.3 ሚሊዮን የሴፍቲኔት ተረጂ የዓለም ባንክ ከረዳና አሁን ደግሞ ለ700 ሺህ ብቻ ከረዳ 7.6 ሚሊዮን የሴፍቲኔት ተረጂ ምን ሆነ? ቁጥሩ መጨመር ሲገባው በዚህ ልክ ለምን ቀነሰ? በሌላ አነጋገር ከ90 በመቶ በላይ የሆነው የሴፍቲኔት ተረጂ ምን ሆነ? መልሱን ሪፖርተር ሊጽፈው አይችልም። “የሙያ ሥነምግባሩ” አይፈቅድለትም። መልሱ ግን ቀላል ነው – ከተረጂነት ስለተላቀቁ ነው!!
የትህነግ ሰዎች እጅግ ጭከና በተሞላበት ሁኔታ የትግራይህን ሕዝብ እስካሁን ድረስ በሴፍቲኔት አቆራምደው እያሰቃዩና የነሱ ተገዢ እያደረጉ የሚፈጽሙትን ግፍ መዘገብ ለሪፖርተር የሙያ ግዴታ አይደለም። እጅግ የሚያሳዝነውና ግራ የሚያጋባው እንዲህ ዓይነቱን የሀገር ጸር የሆነ ሚዲያ መንግሥትም፣ የመንግሥት የልማት ድርጅቶችም፣ የግል ንግድ ባለቤቶችም፣ ሁሉም በሚባል ደረጃ በማስታወቂያና በስፖንሰርነት አይዞህ፣ ሀገር ቦርቡርልን እያሉ በገንዘብ እየተከንባከቡ መደገፋቸው ነው።
ሪፖርተርም ባለቤቱም አውሬዎች ናቸው። አውሬ ደግሞ ወዳጅ የለውም፤ አውሬ አይለምድም፤ ያሳደገውን፣ ያበላ ያጠጣውንም ስልቅጥ አድርጎ የሚበላ፤ የበላበትን ወጭት ሰባሪ ጨካኝ ነው። ጊዜው እስኪደርስለት ግን አድብቶና አድፍጦ ይጠብቃል፤ መበላቱን ያላወቀ ደግሞ “ኑርልኝ” እያለ አውሬውን ይቀልባል፤ ይሸልማል።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ



Leave a Reply