
* ለመሆኑ የቴዲ ኢትዮጵያ የት ትሆን ያለችው?
ታዋቂው አርቲስት ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) አዲሱን አልበሙን በስምንተኛው ወር፣ በስምንተኛው ቀን፣ በስምንተኛዋ ሰዓት ለመልቀቅ መወሰኑ በቁጥር ስሌት (Gematria) ዙሪያ መነጋጋሪያ አጀንዳ ፈጥሯል። ይህ “888” የተሰኘው ቁጥር በአጋጣሚ የተመረጠ እንዳልሆነና አርቲስቱ ሆን ብሎ መልዕክት ለማስተላለፍ የተጠቀመበት ነው የሚሉ ወገኖችም አሉ። በክርስትና እምነት 777 የመለኮት ቁጥር ሲሆን፣ 666 ደግሞ የባቢሎን፣ የአውሬው ወይም የክርስቶስ ተቃዋሚ ቁጥር ተደርጎ እንደሚወሰድ ሁሉ፣ 888 ምንን ሊወክል ይችላል የሚለው ጥያቄ የብዙዎችን ትኩረት ስቧል።
ከመንፈሳዊ ትርጓሜ አንፃር፣ 888 በግሪክ ቋንቋ የኢየሱስ (Ιησούς) ስም መጠሪያ ሆኖ የሚያገለግልና ከፍጽምና በላይ የሆነን መለኮታዊ ኃይል ወይም አዲስ ጅማሮን የሚያመለክት ቁጥር ነው። ቁጥር 7 የፍጹምነት ምልክት እንደሆነ ሁሉ፣ 888 ደግሞ ከዚያም የላቀውን ሰማያዊ ኃይል ይወክላል። ቁጥሩ የሀብት፣ የስኬት እና በመንፈሳዊና ቁሳዊ ነገሮች መካከል ያለን ሚዛን የሚያመላክት ሲሆን፣ አንድ የሕይወት ምዕራፍ አብቅቶ የተሻለ ምዕራፍ መጀመሩን እንደሚያበስር ይገለጻል።
ቴዲ አፍሮም ይህን ቁጥር መጠቀሙ አሁን ካለው የሀገሪቱ ተጨባጭ ሁኔታ ጋር በማያያዝ፣ አዲስ የተስፋ ምዕራፍ መጀመሩን ለማብሰር ካለው ፍላጎት ሊመነጭ እንደሚችል ግምቶች አሉ። ሌሎች ደግሞ “ብልጽግና ስምንት ዓመት ገዝቷል፤ ይበቃዋል” ነው ቴዲ እያለ ያለው ሲሉ ጉዳዩን ከብሔር አኳያ ለማያያዝ የሚፈልጉ ደግሞ በገዳ ሥርዓት አባ ገዳ የሚመረጠው በየስምንት ዓመቱ ስለሆነ የዐቢይ ኦሮሙማ አገዛዝ ይብቃህ ሊባል ይገባዋል የሚል የነውጥ/ለውጥ ኮድ መልዕክት አለው ይላሉ። በማስረጃነትም ቴዲ የዓድዋ በዓልን አስመልክቶ ይህንን “ስርዓት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በቃ ልንለው” ይገባል በማለት በማኅበራዊ ድረገጹ ያስተላለፈውን መልዕክት ይጠቅሳሉ።
በሌላ በኩል፣ 888 በሙዚቃው ኢንዱስትሪ ውስጥ ከአሉታዊና ከምሥጢራዊ ማኅበራት (ኢሉሚናቲ) ጋር ግንኙነት እንዳለው የሚገልጹ መረጃዎች አሉ። አንዳንዶች ቁጥሩ ሰዎችን ለማታለል፣ አዲስ የዓለም ሥርዓትን (New World Order) ለማስተዋወቅ ወይም በገንዘብና በቁሳዊ ስኬት ላይ ብቻ ያተኮረ የስግብግብነት ምልክት እንደሆነ ይተረጉሙታል። በተጨማሪም ቁጥሩን ለጥንቆላና ሰዎችን በሐሳብ ለመቆጣጠር (Mind Control) እንደሚጠቀሙበት የሚገልጹ ወገኖች፣ በታዋቂ ሰዎች ዘንድ ሲጠቀስ “በማር የተለወሰ መርዝ” ሊሆን እንደሚችል ስጋታቸውን ይገልጻሉ።
እንዲህ ያሉ ምሥጢራዊ ቁጥሮችን መጠቀም የሰዎችን የማወቅ ጉጉት በመቀስቀስ ለዝናና ለገበያ ማሟሟቂያ የሚውል “Mystery Marketing” ሊሆን እንደሚችልም ይገመታል። አርቲስቶች ራሳቸውን እንደ መንፈሳዊ መሪና አዳኝ አድርገው ለማቅረብና ደጋፊዎቻቸው እንደ ደቀ መዝሙር እንዲከተሏቸው ለማድረግ እንዲህ ያሉ ኮዶችን ሊጠቀሙ ይችላሉ። ይህ አካሄድ አድናቂዎች ከአድናቆት ባለፈ የ”ደቀ መዝሙርነት” ስሜት እንዲያድርባቸውና አርቲስቱን እንደ ንጉሥ ወይም ጥበበኛ መሪ እንዲመለከቱት ለማድረግ የታለመ ስልታዊ የምስል ግንባታ እንደሆነም ይገለጻል።
በአጠቃላይ፣ የ888 ምርጫ በቴዲ አፍሮና በደጋፊዎቹ መካከል ያለውን ግንኙነት ወደ መንፈሳዊ ከፍታ የሚወስድና አርቲስቱ “እኔ ከብርሃኑ ወገን ነኝ” የሚል ምስል ለመፍጠር የተጠቀመበት መንገድ እንደሆነ ይነገራል። ቁጥሩ የብልጽግና ምልክት በመሆኑም፣ ቴዲ የደረሰበት የዝናና የሀብት ከፍታ ከመለኮታዊ ድጋፍ ጋር የተያያዘ መሆኑን ለማሳየት ያስችለዋል። ይህ በምሥጢራዊነት የተሞላ የአልበም መግለጫ አየሩን እንዲቆጣጠርና በኢንዱስትሪው ውስጥ ትልቅ አጀንዳ ሆኖ እንዲቀጥል በማድረግ ብልጽግና በመደመር ሳይሆን የሚመጣው በኢቶሪካ ነው፤ ለዚህም ደግሞ መለኮታዊ ድጋፍ አለን የሚል የአጸፋ ምላሽ ተደርጎ ሊታይ ይችላል።
ዓመጽን፣ ለውጥን ማነሳሳት እና 888
በሙዚቃ ታሪክ ውስጥ ቁጥሮች ሰዎችን ለአንድ ዓላማ ለማንቀሳቀስ ይውላሉ። ከዚህ አኳያ ከታሰበበት 888 ለለውጥ ማቀጣጠያ፣ ለውስጥ አብዮት ማነሳሻ፣ ለዓመጽ ማቀጣጠያ ማገለገሉ ከብዙ በጥቂቱ ነው።
ከሥርዓት ለውጥ ጥሪ አንጻር 888 “አዲስ ጅምርን” ይወክላል። በመሆኑም 888ን ዘፋኞች በአገራቸው ውስጥ ያለውን ነባሩን ፖለቲካዊ ወይም ማኅበራዊ ሥርዓት በመቃወም “አዲስ ዓለም” ለመፍጠር በሚያደርጉት እንቅስቃሴ ውስጥ እንደ መፈክር ሊጠቀሙበት ይችላሉ። ይህ በአድናቂዎች ዘንድ “አሮጌውን ሥርዓት አፍርሱ” የሚል የዓመጽ መንፈስ መቀስቀሻ ተደርጎ ይወሰዳል።
እንግዲህ ቴዲ ከየትኛው ጎን ሆኖ ይህን መለያ እንደመረጠ ይፋ ስላላደረገ አፍ ሞልቶ መናገር ባይቻልም፣ በቅርቡ እነ አቶ ነዓምን፣ “ታዋቂ ሰዎችን፣ የኪነት ሰዎችን፣ ተጽዕኖ ፈጣሪዎችን፣ ወዘተ እንጠቀማለን” በማለት በኢትዮጵያ ምርጫውን ተቀባይነት እንዳይኖረው (በእርሱ ቋንቋ delegitimize) ለማድረግ በተጀመረው የዓመጽ አደራጅ ቴክኒክ ኮሚቴ ስብሰባ ላይ ከተናገሩት ጋር ይገጥማል በሚል ስጋት የገባቸው ጥቂት አይደሉም።
የዚሁ የእነ አቶ ነዓምን እና አቶ ልደቱ ድርጅት የፕሮፓጋንዳ ክንፎች “እንጠብቅሃለን” በማለት በቴዲ አፍሮ አልበም ስም የተሸለመ ጥብቆ ደምቀው በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ዘመቻ መጀመራቸው ባለቤቱ አምለሰት “ጥቁር ልበሱ” በሚል ስታቀጣጥለው የነበረውን የውክልና ዘመቻ የሚያስታውስ መሆኑን የሚጠቅሱ አሉ። በዚህ በከሸፈው “ጥቁር ልበሱ፤ ወደ አራት ኪሎ ገስግሱ” ዘመቻ ወቅት “ከአራት ኪሎ ለዙፋኑ ቅርብ ከሆኑ መመሪያ እየጠበቅን ነው” ሲሉ የተሰሙ መኖራቸው የሚታወስ ነው። ይህ ጊዜው ሲደርስ የሚዘረገፍ የአራት ኪሎ ስብስብ ገድል ነው።



የውስጥ አብዮት ለማስነሳት የሚውለው 888ን “እንደ ምልክት የሚጠቀሙ አድናቂዎች ራሳቸውን እንደ አንድ ልዩ ሠራዊት እንዲቆጥሩ በማድረግ፣ ዘፋኙ የሚሰጠውን ማንኛውንም ትዕዛዝ ወይም ዓቋም ያለ ጥርጣሬ እንዲቀበሉ ሊያደርጋቸው ይችላል” የሚሉት ወገኖች “ይህቺን ካንጠለጠልህ ጥይት አይመታህም” ልክ እንደሚባለው ዓይነት የድግምት ተጽዕኖ እንደሚመለከቱት ይገልጻሉ።
ወቅቱን ጠብቆ የተለቀቀው “ናዕት”
ቴዲ አፍሮ ዘመን ተሻጋሪ በሆኑ የሙዚቃ ሥራዎቹ የሚታወቅ ነው፤ ሁኔታዎችን ዓይቶ የሚወስደው እርምጃና የሚለቀው ነጠላ ዘፈን በአንዳንዶች ዘንድ “ጥቅመኛ” የሚል ስያሜ የሚያሰጠው ቢሆንም ድፍረቱ ግን አሁንም አየሩን እንዲቆጣጠር አድርጎታል። ከበርካታ ዓመታት በፊት አንድ የትግራይ ተወላጅ ሙስሊም ወጣት በሶማሊያ የተበየነበትን ፍርድ ቴዲ በሺዎች ብር ከፍሎ፣ ነጻ አስወጥቶ፣ ከቤተሰቡ እንዲቀላል ያደረገበት የሚረሳ አይደለም።
በዚህ ልክ ታላቅ ሥራ የሠራው ቴዲ ሌላም የማይታወቅ ወይም ብዙም የሚይጠረጠርበት ምሥጢራዊ ማንነትም አለው። በትህነግ ዳግም ወረራ አማራ ክልል ወደ ዓመድነት ሲቀየር፣ በቃላት ሊገለጽ የማይችል አስደንጋጭ፣ ሊታመን የማይችል ግፍ፣ ዝርፊያ፣ አስገድዶ መድፈር፣ የጅምላ ጭፍጨፋ ሲፈጸም፣ አፋር ክልል ሲወደም፤ ቤተ እምነቶች ሲረክሱ፣ መነኮሳት ሲደፈሩ፣ የምነና ቆባቸውን ጥለው ማቅ ሲለብሱ፣ ጀግኖቹ የኢትዮጵያ ተምሳሌቶች ሲገደሉ፣ ገዳዮቹና ጨፍጫፊዎቹ በገሃድ እየታወቁ የቴዲ ዝምታ ሌላው ጥያቄን የጫረ ጉዳይ ሆኖ ያለፈና እስካሁን መልስ ያልተገኘለት ጉዳይ ነው። አሁን ላይ የሕዝብ ሰቆቃ ድምፅ ነኝ በማለት በጽሑፍና በዘፈን እንደሚያደርገው ያኔም ተመሳሳይ ነገር አለማድረጉ ምን ይሆን ምሥጢሩ የሚያሰኝ ሆኖ ቀርቷል።






ወረራውን ለመመከት ከልሒቅ እስከ ደቂቅ፤ ከምሑር እስከ ተማሪ፤ የሕክምና ባለሙያዎች፣ አርቲስቶች፣ በግምባር ለመፋለም ብቻ ሳይሆን ሠራዊቱን ለማነቃቃት በግምባር እየተገኙ ስለ ኢትዮጵያ ሲያዜሙ፣ ወታደሩን ሲያደፋፍሩ፣ ደሙን ሲጠርጉ፣ ቁስሉን ሲያጥቡ፣ ቀለቡን ሲያዘጋጁ፣ ቴዲ “ፍቅር ያሸንፋል” ብሎ ይመስላል ዝምታን ነበር የመረጠው። የብልጽግና ሹመኛ የነበረው ዮናስ ዘውዴ “ቴዲን በአካል አውቀዋለሁ፤ ለህልውና ዘመቻው እንዲቀሰቅስ ብዙ ተለምኖ፤ ብዙ ተጎትጉቶ ነበር እርሱ ግን ወይ ፍንክች” ብሎ እንደነበር ሰሞኑን ባጋራው መረጃ መግለጹን ልብ ይሏል።
ከወረራው በኋላም የግፍ ገፈት ቀማሾችን መልሶ ለማቋቋም ርብርብ ሲደረግ፣ ገንዘብ ሲሰበሰብ፣ ተፈናቃዮች ወደ ቀዬአቸው እንዲመለሱ ሕዝብ ሲረዳዳ፣ … ሠንደቋን የሙጥኝ ብሎ በየመድረኩ የሚታየው ቴዲ አንዲት ኮንሰርት አድርጎ ለተፈናቃዮች መርጃ የሚውል ገንዘብ ሲያሰባስብ አለመታየቱ የቴዲ “ኢትዮጵያ” በነጠላ ዘፈኑና በመድረክ ላይ ብቻ ትሆን ያለችው የሚያስብል ሆኖ አልፏል።
በዚያን ወቅት (የዛሬ አራት ዓመት) “ናዕት” በሚል ርዕስ ያወጣው ዘፈኑ ሲያልቅ “መታሰቢያነቱ ላለፉት አራት ዓመታት በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች አለአግባብ በግፍ ለተገደሉ፣ አካላቸው ለጎደለ እና ከመኖሪያ ቀያቸው ለተፈናቀሉ ንጹሐን ዜጎች በሙሉ ይሁን” ይላል። “መታሰቢያነቱ” ነው የሚለው እንጂ “ገቢው” አላለም!!
ሌላው የሚጠቀሰው ጉዳይ “ናዕት” የሕዝብ ጩኸት ነው፤ የሕዝብ ድምፅ ነው የተባለለትን ያህል የወጣበት ጊዜ ሳይጠቀስ የሚታለፍ አይደለም። እንደ አርቲስትና እንደ ኢትዮጵያዊ ቴዲ የሕዝብን ድምፅ በ“ናዕት” በዚህ መልኩ ማሰማቱ ችግር የለውም። ጥያቄ የሚፈጥረው ግን የተለቀቀበት ቀን ነው – ቴዲ የዛሬ አራት ዓመት አካባቢ “ሳር ያለመልማል ዛሬም በእልፍ አእላፍ ሬሳ” የሚል ስንኝ ያለበትን “ናዕት” የለቀቀው “አረንጓዴው አሻራ” የችግኝ ተከላ በሚጀመርበት ዕለት ነበር። በርግጥ የዘፈኑ ዓላማና የተለቀቀበት ቀን የሕዝብ ድምፅ መሆን ነው ወይስ በሕዝብ ድምፅ ስም ሌላ ዓላማ ይኖረው ይሆን ብሎ የሚያስጠይቅ ነው። የአሁኗ 888ስ እንዲሁ በጥናት የተከሰተች ኮድ ናት ወይስ የኪነ ጥበብ ብቻ ውጤት ነች?

ወደኋላ መለስ ብለን ትህነግ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሕዝብ በሚያሰቃይበት ጊዜ እና በጅምላ በሚጨፈጭፍበት ጊዜ፤ የወልቃይት ሕዝብ መግቢያ አጥቶ በጅምላ ሲታረድ በነበረበት ዘመን በቴዲ ሚስት አምለሰት መሪነት “አረንጓዴ መሬት” የሚል ችግኝ መትከል ፕሮጀክት ነድፋ ታስተዋውቅ ነበር (ጎልጉል የሠራው ዘገባ እዚህ ላይ ይገኛል)። ፕሮጀክቱ በሒልተን ሆቴል ሲተዋወቅም ቴዲ የመጀመሪያ ልጁ ሚካኤል ያለበትን ፎቶ በትልቁ አሠርቶ ለሚስቱ መድረክ ላይ ሲያበረክት እንዲህ ነበር ያለው፤ “ሚካኤል ችግኝ ነው። … ችግኝ ይተክላል”።
የባለቤቱን የችግኝ መትከል ፕሮጀክት በመደገፍ ይህንን በአደባባይ የተናገረው ቴዲ በናዕት ዘፈኑ “ሳር ያለመልማል ዛሬም በእልፍ አእላፍ ሬሳ” ብሎ ቀን ጠብቆ በችግኝ ተከላ ማስጀመሪያ ዕለት ነጠላ ዜማ መልቀቁን፤ በደጋፊዎቹ “ንጉሡ” እየተባለ የሚጠራው ቴዲ የሚሠራው ለማን ነው የሚል ጥያቄ ይጭራል። ለጎረቤትና ለታሪካዊ ጠላቶቻችን ነው እንዳይባል “ኢትዮጵያ” እያለ የሚያዜምላት አገሩን በዚህ ልክ አሳልፎ ሊሸጥ ይችላል ብሎ እንዴት ማሰብ ይቻላል?
ኢቶሪካ ሌላ ጊዜውን ጠብቆ የወጣ “ናዕት”?
“ጦርነት ሁሉ በማስመሰልና በማታለል ላይ የተመሠረተ ነው” ይላል ሱን ዙ ስለ ጦርነት ጥበብ ሲናገር፤ “ማጥቃት በምንችልበት ጊዜ ዓቅም የለሽና የማንችል ሆነን እንታያለን፤ ኃይል መጠቀም በምንችልበት ጊዜ ምንም የማናደርግ ሥራፈት መስለን መታየት አለብን፤ ስንቀርብ ጠላታችን በጣም የራቁ ናቸው ብሎ እንዲያስብ ማሳመን አለብን፤ ስንርቅ ደግሞ የቀረብን እንዲመስለው አድርገን ማሳመን አለብን”።
ሐሙስ የሚለቀቀው የቴዲ አፍሮ አልበም ታቅዶበት ይሁን ወይም እየሆኑ ባሉ አጋጣሚዎች ትኩረት እየሳበ ነው። ከላይ እንደገለጸነው የ888 “ምሥጢርም” ሆነ የኢቶሪካ አልበም ምንነት ጊዜውን ጠብቆ የሚታወቅ ነው የሚሆነው። በቁጥሩ ምን ድብቅ መልዕክት እያስተላለፈ ይሆን? ወይስ እንዲሁ የሀበሻ ሤራ ነው? ወይስ እንዲሁ ደስ ብሎትና ነገሩ ተገጣጥሞበት ነው?
“ዘፈንና ዘፋኝነት ኃጢአት ነው”፤ “ዘፋኞች መንግሥተ ሰማያትን አይወርሱም” በሚለው አስተምህሮ የሚታወቁ የቤተ ክህነት ሰዎች፤ ማለትም ሰባኪያንና መምህራን “ኢቶሪካ” ዘፈን ሳይሆን ከሰማይ የተላከ የመላእክት ዝማሬ አድርገው እየመሰከሩለት ነው።
በማኅበራዊ ሚዲያ በርካታ ተከታይ ያላቸውና በትምህርታቸው የሚታወቁት መምህር ዶ/ር አረጋ አባተ “ኢቶሪካ”ን በተመለከተ አጭር ጽሑፍ ለቅቀዋል። ብልጽግናን አምርረው የሚቃወሙትና የሞዐ ተዋህዶ ግምባር ቀደም ደጋፊና ቀስቃሽ የሆኑት መምህር አረጋ ስለ ቴዲና ስለ አልበሙ ሲናገሩ እንዲህ በማለት ይጀምራሉ “እንኳን ዘፈን መዝሙሩም ማድመጥ የምወድ ሰው አይደለሁም። ኤዲት ማድረግ ካልሆነ ትኩረት የሚፈልግ ሥራ ስሠራ ጸጥ ያለ ቦታ ነው የምመርጠው። ሕይወቴ እንዲያ ስለሆነ መዝሙርም ቢሆን የማድመጥ ልምድ የለኝም። የቴዲን ግን ብዙዎቹም ሙዚቃዎቹን ሰምቻለሁ። … ሙዚቃው ሲወጣ ቢሮ እየሠራሁ እሰማዋለሁ” በማለት መዝሙር መስማት ብዙም የማይወዱት የሃይማኖት መምህሩ ለኢቶሪካ ቅስቀሳ አድርገዋል።
ከላይ እንደጠቀስነው ከሻዕቢያ ተልዕኮና ገንዘብ ተቀብለው “ሕዝባዊ ዓመፅ” በመቀስቀስ ምርጫውን “ሕገወጥ” ለማድረግ ከሚንቀሳቀሱት እነ አቶ ነዓምን ጀምሮ ከላይ እስከተጠቀሱት የሃይማኖት መምህር አረጋ ድረስ ኢቶሪካን ወደ አራት ኪሎ የሚያደርስ ተስፋቸው አድርገውታል። የሚያደርገውን ነገር፤ የሚመርጠውን ቀን፤ የሚናገርበትን ሚዲያ፤ ወዘተ በጥንቃቄ እንደሚያከናውን በቅርብ ወዳጆቹ የሚነገርለት ቴዲ ስምንተኛውን ወር፣ ስምንተኛውን ቀንና ስምንተኛው ሰዓት (888) አለምክንያት አልመረጠም። መሳካት አለመሳካቱ እንዳለ ሆኖ “ናዕት” በታቀደለት ቀንና ጊዜ እንደወጣ ሁሉ ኢቶሪካም እንዲሁ በዕቅድ የተደረገ ለመሆኑ ብዙ ጠቋሚ ነገሮች አሉ። ውጤቱና ሌላው ጉዳይ ሰሞኑን በሀገራችን ከሚከሰተው የፖለቲካ አቅጣጫ አኳያ የሚታይ ይሆናል።
ማጠቃለያ፤ ቴዲ በዘፈን ሥራው የተካነ ነው፤ የሚያወጣቸው ዘፈኖች ተወዳጅ ናቸው፤ ስለ ኢትዮጵያ የሚናገረው ልብን ይነካል፤ ስሜትን ይኮረኩራል፤ በዚህ ዓይነት የልዕልና ማማ ላይ ያለው ቴዲ በዚሁ ልክ ስለ ሀገር፤ ስለ ኢትዮጵያ ብሎ ጥቂት ርቀት ሲሄድ ግን አይታይም። እርሱ በሙዚቃው የሚያወድሳትንና ከልጆቹ ጋር በሰላም እንዲኖሩ የሕይወት መስዋዕትነት እየከፈለ፤ ደሙን እያፈሰሰ የኢትዮጵያን ዳር ድንበር ለሚያስጠብቀው ወታደር ቴዲ ያደረገው ምን ነገር አለ? እንደ ቀደምት አርቲስቶች ለሠራዊቱ ሲያዜም ወይም ግምባር ሄዶ ሲያነቃቃ አይታይም። የፍቅር መልዕክተኛ ስለሆነ ነው ከተባለም ዕውቅናውንና ሃብቱን ተጠቅሞ ለሀገር የሚጠቅም፤ ሥራ የሚፈጥር መሠረተ ልማት ሲገነባ አይታይም። በመድረክ እንደሚታየው ትህትናው ለአረጋውንም ሆነ ለችግረኞች የሚሆን ይኼ ነው የሚባል የሠራው ተጠቃሽ የማኅበራዊ ጉዳይ ሥራ የለም፤ ቢያንስ ዝናውን ተጠቅሞ ሕዝብን አስተባብሮ በላብ ተነክሮና በእንባ ታጅቦ ለሚያዜምላት ኢትዮጵያ የሚሆን ስሙ የሚጠራበት መሠረተ ልማት ሠርቶ አይታወቅም። ታዲያ የቴዲ ማንነት የትኛው ነው? የቴዲስ ኢትዮጵያ የት ይሆን ያለችው?
በመጨረሻም ደራሲው አንድሬ ማልሩ በተናገረው እናብቃ፤ “የሰው ልጅ ማንነቱ፣ ነኝ ብሎ የሚያስበው ወይም በገሃድ የሚታየውና የሚያሳየው ሳይሆን እውነተኛ ማንነቱ የደበቀው ነው”።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ






Leave a Reply