• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ

August 13, 2025 12:58 am by Editor 2 Comments

ሰሞኑን ሞዐ ተዋሕዶ አየሩን ሞልቶታል። በተለይ በቅርቡ ከሞዐ ተዋሕዶ አመራሮች መካከል አንዱ የሆኑት አቶ ፋንታኹን ዋቄ የሰጡት ቃለ ምልልስ ወደኋላ ሄደን ብዙ ነገሮችን እንድንዳስስ የሚያስደርግ ሆኗል። የዛሬ ሦስት ዓመት በቀነኒሳ ሆቴል ዶ/ር ወንደሰን በሚመራው ስብሰባ መግለጫ በሰጡበት ወቅት የተናገሩትና ሰሞኑን የተሰማውን ጉዳይ ባጭሩ ለማስቀመጥ እንሞክራለን። ይህንን በማድረግም የሞዐ ተዋሕዶን ሁኔታ ለየት ባለ ሁኔታ ለማየት እንሞክራለን፤ እንደተባለው ሞዐ ሃሳብ የሚያመጣና ወደ ሕዝቡ የሚያሰርጽ ንቅናቄ ነው? ወይስ ሌላ ተልዕኮ አለው? የሚለውን በንጽጽር እናያለን።

የዛሬ ሦስት ዓመት አካባቢ በቀነኒሳ ሆቴል ከተካሄደው የሞዐ ተዋሕዶ ስብሰባ በኋላ የማኅበረ ቅዱሳን ሚዲያ ከሶስት የሞዐ ተዋሕዶ አመራሮች ጋር ውይይት አድርጎ ነበር። በውይይቱ የተገኙት መምህር ገብረመድኅን እንየው፣ መምህር ያረጋል አበጋዝና መምህር ፋንታኹን ዋቄ ሲሆኑ ከተነሱላቸው ጥያቄዎች ጥቂቱን ብቻ በመውሰድ የሰጡትን ምላሻቸውን እናያለን።

ከቀረቡላቸው ጥያቄዎች አንዱ የውክልና ጉዳይ ነበር። እናንተን ማን ወክሏችሁ ነው ይህንን ጉዳይ በኦርቶዶክስ ምዕመናን እና በቤተ ክርስቲያኗ ስም የምታራምዱት የሚል ነበር። ይህ ጥያቄ ትንሽ ያበሳጫቸው እንደነበር ከምላሻቸው መረዳት ቻላል። ለጥያቄው የሰጡት ምላሽ፤ በቅድሚያ ሲኖዶሱ በተደጋጋሚ ጥሪ ሲያደርግ እንደነበርና የእርሱ አካሄድ ለዚያ ምላሽ እንደሆነ፤ ከዚያም በዋነኛነት ያስረዱት ጉዳቱና ችግሩ የሚታይና ማስረጃም ሆነ ውክልና የሚያስፈልገው እንዳልሆነ ነው። እንዲያውም የውክልና ጥያቄ ሤራዊና በውስጡ ትክክለኛ እሳቤ የሌለው የተንኮልና ውዳቂ ሃሳብ እንደሆነ በእንደምታ አመልክተዋል።

የሞዐ ሰዎች የውክልናን ጥያቄ ሲመልሱ ባለመናገር ያሳወቁት ነገር ማንም ምዕመን ተሰብስቦ ወይም ከየትኛውም የቤተ ክርስቲያኒቱ መምሪያ በጉዳዩ ላይ እንዲሠሩበት ተጠይቀው ሳይሆን የኦርቶዶክስን ችግር እናውቅላታለን፤ ለችግሯ መፍትሔ እንፈልግላታለን ከሚል ነው። በሌላ አነጋገር በአውቅልሃለሁ ባይነት ነው የተነሱት እንጂ ውክልና ኖሯቸው አይደለም።

በመሠረቱ ይህ ስህተት አይደለም። ነገር ግን የሞዐ ሰዎች በነጻ አውጪ ግምባር የተደራጁትን ቡድኖች (ኦነግ፣ ትህነግ፣ ኦብነግ፣ …) በጣም ያወግዛሉ፤ ይነቅፋሉ። ከዚህ አኳያ የውክልናው ጥያቄ እነርሱንም ልክ እንደ ነጻ አውጪ ግምባሮች ያለ ሕዝብ ውክልና በእናውቅልሃለን ባይነት የተነሱ መሆናቸውን የሚያረጋግጥ ነው። ነጻ አውጪ ግምባሮች “ነጻ አወጣዋለሁ” በሚሉት ሕዝብ ስም የሚደራጁት በብዙ መልኩ አዋጪ ስለሆነ ነው እንጂ፤ ሕዝቡ ተሰብስቦ ነጻ የሚያወጣን ቡድን ያስፈልጋል ብሎ ስላቋቋማቸው አይደለም፤ ሞዐም እንዲሁ ነው።

ስለዚህ ሞዐ ተዋሕዶ አመሠራረቱ እንደ አብዛኛው ነጻ አውጪ ግምባር በአውቅልሃለሁ፤ ችግርህን እረዳልሃለሁ፤ ወዘተ በሚል ነው። ከላይ እንዳልነው ይህ ስህተት ላይሆን ይችላል፤ ነገር ግን በተመሳሳይ ሁኔታ በነጻ አውጪ ስም የተቋቋሙትን ጎጠኛ፣ ጭፍንና ሀገር አጥፊ ቡድኖችን ለመውቀስ የሞራል ልዕልና አይሰጥም። እነርሱም በሕዝብ ስም ለጥቅምና ለዓላማ ነው የተዋቀሩት፤ ሞዐም እንዲሁ በብዙኃኑ የኦርቶዶክስ አማኝ ስም ለራሱ ዓላማ የተዋቀረ ነው።

የሞዐ ሰዎች በተደጋጋሚ የሚያነሱት ነገር ፍትሕ፣ ርትዕ፣ እውነት፣ ሐቅ ወዘተ የተሰኙ ኦርቶዶክሳዊ እሴቶች የሚሏቸውን ነው። ትክክል ነው ኦርቶዶክስ የእነዚህና የሌሎች እጅግ የላቁ እሴቶች ባለቤት ነች፤ ሕዝብንም በዚህ መሥመር አንጻለች፤ አብቅታለች። ተጽዕኖዋም የሚታይ እና ዘመናትን የዘለቀ፤ ድንበር የተሻገረ ነው።

በቀነኒሳ ሆቴል በተደረገው ስብሰባም ሆነ በቀጣይ በተደረጉ ቃለ ምልልሶችም ሆነ ውይይቶች የሞዐ ሰዎች ስለ እውነት አጥብቀው ይናገራሉ፤ ራሳቸውንም የእውነት ጠበቃ አድርገው ያቀርባሉ። ይህንን እነርሱ “አምላካዊ እውነት” ያሉትን ይዘው ደግሞ አሸናፊ እንደሚሆኑ በተደጋጋሚ ሲናገሩ ተደምጠዋል።

ነገር ግን ሰሞኑን አቶ ፋንታኹን ዋቄ በሰጡት ቃለ መጠይቅ ላይ ፋኖን ያደራጁት ብቻ ሳይሆን፣ አሁንም ፋኖ እየተመራ ያለው በሞዐ ተሐድሶ አስተሳሰብና እሴት እንደሆነ ገልጸዋል። እንዲያውም አሳምነው ጽጌ ስለ ሞዐ አደረጃጀትና ሃሳብ ሰምተው የሞዐ አደራጆችን ሲያነጋግሯቸው ሃሳቡን እርሳቸው (አሳምነው) የተቀበሉት ብቻ ሳይሆን የኔም ሃሳብ ነው፤ በሉ እኔና እናንተ አልተነጋገርንም ብለው ሁለቱም በየፊናቸው እንዲሠሩ ተስማምተው መለያየታቸውን አቶ ፋንታኹን ተናግረዋል።

ይህ አሁን የተሰማ የሞዐ ተዋሕዶ ዓላማና ሃሳብ ነውንጂ ቀነኒሳ ሆቴል ሲመሠረት በትጥቅ ትግል መንግሥትን ለመገልበጥ ነው ዋናው ሃሳባችን የሚል ነገር አልተነገረም። በቀጣይ በተሰጡ መግለጫዎችም የትኛውም የሞዐ ሃሳብ አራማጅ ይህንን በግልጽ ተናግሮ አያውቅም። ይኼ ታዲያ ውሸት አይደለም? ለቅዱስ ዓላማ ነው የተነሳነው፤ የያዝነው መሣሪያ እውነት ነው፤ አምላካዊ ነው፤ ሲል ከነበረ ቡድንና አመራር በዚህ ልክ መዋሸትና መሠሪ መሆን ግብዝነት አይደለም? የሞራል ልዕልናውስ የት ላይ ነው? ለሌላውስ ተከታይ (ምዕመን) ምን ዓይነት አርአያነት ነው?

በአውቅልሃለሁ ባይነት ተጀምሮ የሕዝብን ስሜት በስሑት ዓላማ የቀሰቀሰ፤ ድብቅ ሤራ የሚጠነስስ፤ ፍጹም እውነት ላይ ነው የተመሠረትነው በሚል ሰላማዊ እንቅስቃሴ የሚያደርግ መስሎ ሃሳብ ከፊቱ ብረት ከኋላው ያደረገ፤ ሥልጣን ለመቆጣጠር ሲል መጣሁልህ ያለውን ሕዝብ የሚያሰቃይ ቡድን፤ ምኑ ነው ሰላማዊ እንቅስቃሴ የሚባለው? ይልቅ በግልጹ ሞዐ ተዋሕዶ ነጻ አውጪ ግምባር (ሞነግ) ቢባል ለደጋፊም ለተቃዋሚው ብዙ ነገር ያቀልል ነበር።

ሞዐውያን የልዕለ እሴት ባለቤት ነን ይላሉ፤ በንግግራቸውም ይህንኑ አሳምረውና አጣፍጠው ይናገራሉ። ለቅድስት ቤተ ክርስቲያንና ለምዕመኗ ነው የቆምነው ይላሉ። ነገር ግን የትግራይን ጉዳይ አያነሱም። ቤተ ክርስቲያን የተዋረደችውና ቀኖናዋ የተረገጠው በኦሮሞ ጳጳሳት መሪነት የጫካ ሲኖዶስ ሲመሠረት ብቻ ሳይሆን በትግራይም መንበረ ሰላማ ሲመሠረት ነው።

የትግራዩ እንዲያውም እጅግ የከፋ ነው። የመንበረ ሰላማን አካሄድ ሲኖዶሱ በግልጽ አውግዟል፤ አካሄዱንም ኮንኗል። መንበረ ሰላማም የሲኖዶሱን ውሳኔ ንቆና አልቀበልም ብሎ በራሱ መንገድ ሄዷል። ከላይ እንደገለጽነው ለሞዐ የውክልና ጥያቄ ሲቀርብለት የሰጠው አንዱ መከራከሪያ ነጥብ በኢትዮጵያ እየተከሰተ ያለውን ነገር በተመለከተ ሲኖዶሱ ጥሪ አቅርቧል፤ እኛም ለዚያ ምላሽ ለመስጠት ነው ሞዐን ያቋቋምነው ብለዋል። ታዲያ ሲኖዶሱ የመንበረ ሰላማን አካሄድ አውግዞ ላወጣው መግለጫ ሞዐ ድጋፍ መስጠትና ለዚህ ሀገርን ለሚከፋፍል ቡድን ምላሽ ለመስጠት አሁን ባለው ቁመና ልክ ለምን አልተደራጀም? ቤተ ክርስቲያን ተዋረደች፤ “መንፈስ ቅዱስ የሚመራው ሲኖዶስ ውሳኔ ተናቀ” ብሎ ሞዐ ለምን ምዕመናንን አላስተባበረም?

እንደ ጫካው ሲኖዶስ የትግራይ መንበረ ሰላማም ለቤተ ክርስቲያን ኅልውና በጣም አስጊ ነው፤ ለሞዐ ግን አይደለም። ይህ የአገሪቱን ፓትሪያርክ ወደ ትግራይ ሲሄዱ ተቀብዬ አላነጋግርም፤ አላስገባም ያለ ቡድን እያስከተለ ያለው ጉዳት ለሞዐ የአጀንዳው አካል አይደለም፤ የቤተ ክርስቲያን ስደት መገለጫ አይደለም። ሲሆንማ ቤተ ክርስቲያን ማቅ መልበስ፣ ማልቀስ፣ እግዚኦ ማለት ያለባትና ኅልውናዋ የተደፈረው አሁን ነበር።

ሃቁ ይህ ሆኖ ሳለ የሞዐ ተዋሕዶ ጥላቻ እና አግላይና ጸረ መንግሥት ዓቋም ከየት መጣ የሚለው ጥያቄ እውነተኛ ምላሽ ስለሚያስፈልገው የምንመለስበት አጀንዳ ይሆናል።

ሞዐውያን በየሚዲያው እንደሚናገሩት ወይም ቀነኒሳ ሆቴል እንደሰጡት መግለጫና ማብራሪያ በላቀ የሞራል ልዕልና ውስጥ ያሉ፤ ኢትዮጵያን ለመታደግ የተነሱ ሰላማዊ ታጋዮች ሳይሆኑ በሃይማኖት ሰበብ ሁሉን የመቆጣጠር ምኞት ያላቸው፤ ተከታዮቻቸውን ከሃይማኖት ጋር በተቀላቀለ ጭፍን ፕሮፖጋንዳ የሚመሩ፤ በፊት ለፊት ሰላማዊ እንዲያውም መንፈሣዊ ታጋይ ነን እያሉ በስውር ግን የታጠቀ፣ ጨካኝ፣ አራጅ፣ ነውረኛ ቡድንን በቁጥጥራቸው ሥር ያደረጉና የሚመሩ “ነጻ አውጪ ግምባር” ናቸው። ስለዚህ “ሞዐ ተዋሕዶ ነጻ አውጪ ግምባር – ሞነግ” የሚለው በትክክል የሚገልጻቸው መጠሪያ ነው።

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ

Filed Under: Left Column, Politics, Religion Tagged With: Fano, Moa Tewahido, State and religion, ሞነግ, ሞዐ ተዋሕዶ

Reader Interactions

Comments

  1. ተርፋሳ says

    August 30, 2025 03:52 pm at 3:52 pm

    የተሻለ ፕሮፓጋንዳ ነሥራት ብትችሉ ጥሩ ነው። ይህ ሕጻን እንኳ የማያሳስት ተራ የኩሽት ድምጽ ነው።

    Reply
  2. motuma says

    March 12, 2026 11:08 pm at 11:08 pm

    Maaloo baayee baqeqtani. Salfechu hinjiru?

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

Recent Posts

  • ለሱዳንና ኤርትራ ሲከራከሩ የነበሩት አበባው ባለመመረጣቸው “በጣም ተድጃለሁ” አሉ June 26, 2026 12:29 am
  • “ትህነግ ወደ ዓለምአቀፍ ወንጀለኛነትና አሸባሪነት እየተምዘገዘገ ነው” June 25, 2026 01:00 am
  • አሜሪካ በሕገወጡ ትህነግ አመራሮች ላይ ጠንካራ የቪዛ እገዳ ጣለ June 18, 2026 10:29 am
  • እንደ ሌሊት ወፏ የሚንቀሳቀሰው ኢህአፓ/ትብብር   June 18, 2026 09:36 am
  • የታርጋ ጫጫታ June 15, 2026 05:16 pm
  • ፋንታኹን ዋቄ ከአሜሪካ የሃይማኖት እልቂት አወጁ June 15, 2026 02:12 am
  • ሕገወጡ ትህነግ ወጣቶችን ለዳግም ዕልቂት እያሰናዳ ለፈረንጆች “ኢትዮጵያን አውግዙልኝ” እያለ ነው June 11, 2026 12:57 am
  • በሐዘንና ግልፅ ደብዳቤ ስም የተሸፈነ የድህረ ምርጫ ሀገር የማተራመስ ስትራቴጂ June 10, 2026 12:19 am
  • የጽምዶ ልክፍት June 9, 2026 12:49 am
  • ገዳዩ ማነው? አስገዳዩስ ማነው? June 5, 2026 02:37 pm
  • ጽንፈኝነት ግን በኢትዮጵያ ምድር ፈጽሞ ቦታ የለውም! June 5, 2026 01:47 pm
  • የትብብሩ “ብናሸንፍም ፓርላማ አንገባም” መግለጫ “ወንበር ስታጡ ነው” የሚል ከፍተኛ ተቃውሞ አስነሳ June 4, 2026 12:04 am
  • አዲሱ የትራምፕ የምርጫ መመሪያ፡ የአሜሪካ ዲፕሎማቶችን አፍ ያስዘጋ፤ ተቃዋሚዎች ተስፋ ያስቆረጠ June 3, 2026 08:50 pm
  • “ኢህአፓ ከምርጫው በኋላ ይሰነጠቃል” May 29, 2026 07:07 pm
  • ሪፖርተር፡ “ስውር ተልዕኮ” – በከባድ ወንጀል ሊከሰስ May 6, 2026 11:55 pm
  • የፋኖ ኃይል በደረሰበት ጉዳት ሃምሳ ሺህ የሚጠጋ ትጥቅ ጥሎ ጠፋ April 29, 2026 02:27 pm
  • አዲሱ የቴድሮስ ካሳሁን 888 ኮድ፤ እንደ 666?! April 15, 2026 05:53 am
  • ምኑ ነው ያሳቃችሁ፤ ያስደሰታችሁ? April 2, 2026 10:52 am
  • የጀዋር መሃመድ የፖለቲካ ማንነት እና የባዕዳን ተልዕኮ April 2, 2026 10:16 am
  • ከግብፅ በዳያስፖራ ትርምስ ጠማቂዎች በኩል ፋኖ ወደ አዲስ አበባ የላከው “ስጦታ” March 27, 2026 09:14 am
  • “ሰላማዊ ታጋዮቹ” እነ ልደቱ ከአራጁ ሸኔ ጋር ተጣምረዋል March 25, 2026 01:04 pm
  • ጸረ-ኢትዮጵያዊ የሆነው የሪፖርተር አዘጋገብ March 19, 2026 11:54 am
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ የኦሮሚያ የልማት ድርጅቶች March 18, 2026 10:48 am
  • የጃኖ ስጦታና የዶሮ ፖለቲካ በጎንደር March 10, 2026 09:24 am
Copyright © 2026 · Goolgule