• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

“በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ

July 22, 2025 01:28 am by Editor 1 Comment

ሃራ ወይም ነጻ ተብሎ በሚጠራው መሬት ላይ ሠፍሮ የሚገኘው “የትግራይ የሰላም ኃይሎች” (TPF) ብሎ የሚጠራው ታጣቂ ኃይል በያዝነው ዓመት መጨረሻ ሙሉ ትግራይን እንደሚቆጣጠር አስታወቀ። “ጸጥተኛ” ብለው ለሚጠሩት አቢዮት ሠራዊቱ እየተዘጋጀ እንደሆነም ተነግሯል።

ይህ የተገለጸው በፈረንሳይኛ ቋንቋ በድረገጽ የሚታተመውና አፍሪክ XXI (Afrique XXI) የተባለው ጋዜጣ ከጥቂት ቀናት በፊት በትግራይ ላይ በሠራው ዘገባ ነው። ዘገባው በሃራ ምድር የሰፈሩትን የትግራይ የሰላም ኃይል/ቲፒኤፍ ተብለው ከሚጠሩት ታጣቂዎች ጋር ቃለ ምልልስ ካደረገ በኋላ ነው።

የሰላም ኃይሉ አባላት በአብዛኛው ከዚህ በፊት በትህነግ ሥር ከነበረው የትግራይ መከላከያ ኃይል ወይም ቲዲኤፍ (TDF) ከሚባለው ከድተው የወጡ ናቸው። በተለይ ካለፈው መጋቢት ወር ጀምሮ በብዛት ከቲዲኤፍ እየኮበለሉ ወደ አፋር ምድር ሲገቡ መቆየታቸው ይታወሳል።

ባጭር ጊዜ ውስጥም በዕዝ የተደራጁ ሲሆን ማረጋገጥ ባይቻልም ከፌዴራል መንግሥቱም ሥልታዊ ድጋፍ የሚደረግላቸው መሆኑን ዘገባው አመልክቷል። ዋና ዓላማቸውም አሁን ላይ ከሻዕቢያ ጋር የገጠመውንና ሕጋዊ ማንነቱ በምርጫ ቦርድ የተገፈፈውን ትህነግን ከሥልጣን ማስወገድ ነው።

ሸዊት ቢተው ጋዜጣው ካነጋገራቸው መካከል አንዷ ናት፣ “እዚህ የሚታዩ ባይሆኑም በሁሉም ቦታ ግን ወታደሮች አሉን” ስትል ቦታ እያመላከተች መብራሪያ መስጠቷን ጋዜጣው ዘግቧል። በአፋር ምድር ሆና ከጋዜጣው ጋር ቃለ ምልልስ ያደረገችው ሸዊት “በሬጂመንቶች መካከል ውድድር እያካሄድን ነው” በማለት በስፍራው ከፍተኛ ፀሐይ ቃጠሎ ምክንያት ጠዋትና ማታ ላይ ስለሚካሄደው የእግር ኳስ ውድድር ገልጻለች።

ሸዊት “ናፅናት” ተብሎ የሚጠራው ፓርቲ የቀድሞ አመራር አባል የነበረች ሲሆን አባቷ ቢተው ቀደም ሲል በትህነግ ውስጥ ነባር ከፍተኛ አመራር ነበር። ጋዜጣው እንዳለው ሸዊት የሰላም ኃይል ተብሎ በተቋቋመው የታጣቂዎች ቡድን አመሠራረት ላይ ተሳትፎ አላት።

ሌላው ጋዜጣው ያነጋገረው ሔኖክ ተስፋይ የተባለ የቀድሞ የቲዲኤፍ አባል “በጦርነቱ ጊዜ በምዕራብና በሰሜን ያሉትን ግዛቶች መልሰን መውሰድ ይገባን ነበር” ይላል። “ነገር ግን አዛዦቻችን በስሱ እንኳን እንዳንጠይቅ አስቆሙን፤ የነርሱ ብቸኛ ዓላማ ወደ አዲስ አበባ በመገስገስ ሥልጣን መልሶ መያዝ ነበር። ከፕሪቶሪያ ስምምነት በኋላ ኮሎኔሎቹና ጄነራሎቹ የትህነግ ወታደሮች እንደምንሆን ነበር የነገሩን፤ እኛ ግን የተዋጋነው ትህነግን ለመታደግ ሳይሆን የትግራይን ሕዝብ ለመታደግ ነበር” ሲል ለጋዜጣው ያስረዳል።

ሔኖክ ተስፋይ
ሔኖክ ተስፋይ

የጌታቸው ረዳ የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳዳሪ ሆኖ መሾም በትግራይ ለውጥ እንዳመጣ በሦስት ጥይት የቆሰለው ሔኖክ ይናገራል። “በፊት ጊዜ ሰላማዊ ሰልፍ ስናደርግ ይደበድቡን፣ ያሰቃዩን፣ ያዋርዱን ነበር። ለዚህም ነው ብዙ የትግራይ ልጅ እየተማረረ አገሩ ለቅቆ ወደ ሊቢያ ወይም አረብ አገር የተሰደደው” ይላል ሔኖክ። አክሎም “ጌታቸው ከመጣ በኋላ ግን የተለየ ነገር አሳየን። በምንም ዓይነት እንደፈለጉ ማሰር እንዳይኖር አደረገ፤ በነጻነት እንድንናገር ፈቀደልን” በማለት ልዩነቱን አመላክቷል።

“ጌታቸው የፈቀደው ነጻነት ያልተስማማቸው የፈረሰው ትህነግ መሪዎች አካሄዱን ለማስቆም ቆርጠው ተነሱ። በደብረጽዮን መሪነትና በሻዕቢያ አዝማችነት በያዝነው ዓመት መጋቢት ወር ጌታቸው ከሥልጣኑ በመፈንቀሉ ከሞት አምልጦ ወደ አዲስ አበባ ገባ” በማለት ሔኖክ ለጋዜጣው አስረድቷል።

በወቅቱ የነበረውን ሁኔታ በማስታወስ የሚናገረው የ42 ዓመቱ የሒሳብ መምህር ካህሳይ ኪዳኔ ደግሞ “የትህነግ ሰዎች ከከተማ ውጪ አውጥተው ደበደቡን፤ ያ አልበቃ ብሏቸው እንደሚገድሉን አስፈራሩን” ይላል። ይህ ሲሆን የዚያኑ ጊዜ ብረት አንስቶ ወደ ሃራ ምድር መግባቱን አመልክቷል።

የሰላም ኃይሉ አመራሮች በሥራቸው ያለውን ታጣቂ ቁጥር ይህ ነው ብለው ለመናገር ባይፈልጉም በብዙ መቶዎች በአንዳንዶችም ግምት በሺዎች የሚቆጠሩ የሰላም ኃይሉን እንደተቀላቀሉ ይናገራሉ።      

አብዛኛው ኃይል በአፋር ምድር የሚገኝ ሲሆን ከመቀሌ 110 ኪሜ ርቀት በስተምስራቅ ላይ በምትገኘው ላኮራ ተብላ በምትጠራው ቦታ ላይ ያለውን ኃይል የምታዝዘው ሸዊት ቢተው ሁለት የሰላም ኃይል ግምባሮች በአፋር፣ ሦስተኛው ደግሞ በምዕራብ በኩል ወደ ሽሬ ቀረብ ብሎ እንደሚገኝ ታስረዳለች።

ከእነዚህ ሦስት ግምባሮች “የጸጥታ አብዮት” በማለት የሚጠሩትን ዘመቻ ለማካሄድ የሰላም ኃይሉ በዝግጅት ላይ እንዳለ ይናገራሉ። “በዚህ ዓመት መጨረሻ ላይ ትግራይን በሙሉ እንቆጣጠራለን” ትላለች ሸዊት። በሌላ አነጋገር የሰላም ኃይሉ አዲሱን ዓመት ትግራይ ለማክበር ማቀዱን ነው እየተናገረ ያለው።

ጋዜጣው ቃለ ምልልሱን ያደረገው የሰኔ ወር ከማለቁ በፊት ሲሆን ቃለ ምልልሱ ከተደረገ ከሁለት ሳምንት በኋላ የሰላም ኃይሉ ከአፋር እየለቀቀ የመጨረሻውን ጥቃት ለመሰንዘር ወደ ትግራይ ዘልቆ መግባቱ ተመልክቷል።

የሰላም ኃይሉ ዋና መሪዎች ኃይላቸው ሙሉ በሙሉ ትግራይ ውስጥ እንደሚገኝ ከሳምንታት በፊት ማስታወቃቸው አይዘነጋም።

በተደጋጋሚ እንደተሰማው ከጦርነቱ ማብቂያ ጀምሮ ሕገወጥ የሰዎች ዝውውር የሙስና ወይም የወርቅ ንግድ ውንጀላዎች መስፋፋታቸው ወታደራዊ አለመግባባቶችን አባብሰዋል። “የትህነግ አባላት በጦርነቱ ወቅት የተዘረፉ ዕቃዎችን በመሸጥ ትርፍ አግኝተዋል። ያኔ መናገር አልቻልንም፣ ከሰላም ስምምነት በኋላ ግን ወደ ወርቅና መዳብ ማዕድን ንግድ ገቡ” ስትል ሸዊት ቢተው በምሬት ትናግራለች።

በግጭቱ ወቅት የአካባቢው አስተዳደር መፍረሱ ሕገ-ወጥ ማዕድን አውጪዎች ከትህነግ ባለሥልጣናትና አዛዦች ጋር በመመሳጠር በግልፅ አብረው መሥራት ጀመሩ።

ከፕሪቶሪያው ስምምነት በኋላ በተከሰተው በተኩስ አቁም ወቅት ከተመዘገቡት 270,000 የቲዲኤፍ አባላት መካከል ከ20,000 የሚያንሱ አሁንም በሥራ ላይ መሆናቸውን ጋዜጣው አመልክቷል።

በጦርነቱ ውስጥ የተሳተፈና ለደኅንነቱ ሲባል ስሙ ያልተገለጸ ምሑር “እኛ ቲዲኤፍ የተቀላቀልንበት ምክንያት ሁኔታው አስገዳጅ ስለነበር እንጂ፣ እንደ ኢትዮጵያ የሀገር መከላከያ ሠራዊት የሰለጠነ ሠራዊት አልነበረም” ይላል። እውነታው ግን በወቅቱ ከቤተሰብ በምርቃትና በሽልማት ወደ ጦር ሜዳ ሲላኩ እንደነበር ራሳቸው ያሰራጩትና የሰጡት ወኔ የተሞላ ምስክርነት ሕያው ነው።

“ቲዲኤፍ ምንም ግልጽ የሆነ የፖለቲካ ዓላማ የለውም” የሚል አዲስ ትርክት የተሰማበት ይህ ሪፖርት፣ አሁን ላይ ቲዲኤፍን ተቀላቅለው የነበሩ በርካታ ገበሬዎች፣ ነጋዴዎች፣ መምህራን እና የቡድኑ አባል የሆኑ ተማሪዎች ለቅቀው ወጥተዋል። ጥለው ከወጡት ውስጥ አብዛኞቹ አሁንም ቃል የተገባውን 90,000 ብር (600 ዶላር) ካሳ ይጠብቃሉ። በዚህ ትጥቅ ማስፈታትና መልሶ የማቋቋም (ዲዲአር) ፕሮግራም እስከ ሰኔ መጨረሻ ድረስ 48,308 የሚጠጉት የተጠቀሰውን ገንዘብ የወሰዱ ናቸው። ሁለት መቶ ሺህ የሚሆኑት እስካሁን ሳንቲም አልተቀበሉም።

ቲዲኤፍ ውስጥ ያሉትን በተመለከተ አንድ ስሙ ያልተጠቀሰ ተመራማሪ ሲናገር “ወታደራዊ ውሳኔዎችን በተመለከተ ቲዲኤፍ ውስጥ ያሉት ተምታቶባቸዋል። ምክያቱም ወደቤታቸው መመለስ አይችሉም፤ አንዳንዶቹ ቤታቸው ፈርሷል፤ አንዳንዶቹ ከተፈናቀሉበት መኖሪያቸው መመልስ አይችሉም። አንዳንዶቹ ቤተሰቦቻቸው ሞተዋል። በዚህ ምክንያት የመጠጥና አደንዛዥ ዕጽ ተጠቃሚ ወይም ሱሰኛ ሆነዋል” ብሏል።

ተመራማሪው አክሎ ሲያስረዳ እነዚህ የቲዲኤፍ ታጣቂዎች ምንም እንኳን ከላይ የተዘረዘሩት ችግሮች ውስጥ ሆነው በግራ መጋባት ውስጥ ቢሆኑም ልባቸው አፋር ሃራ መሬት ካለው ኃይል ጋር ነው።

የአራትና የሁለት ዓመት ልጆቿን መቀሌ ትታ የመጣችው የቀድሞ ፖሊስ ሠራዊት አባል የሃያ ዘጠኝ ዓመቷ ገነት ወልደሥላሴ ለጋዜጣው ስትናገር፣ “ልጆቻቸውን በጦርነቱ ያጡ እናቶች አይቻለሁ፣ ልጆቻቸው ቢኖሩ ኖሮ ይጦሯቸው ነበር። ትህነግ ለእነዚህ እናቶች እግዚአብሔርን ያጥናችሁ እንኳን አላላቸውም። የእኛ ቀዳሚ አጀንዳ ትህነግን መገርሰስ ነው። ከማስወገድ ባሻገር አመራሩ ወደ ፍርድ ማቅረብ ነው ዕቅዳችን። ይህ ደግሞ ኃይል አይጠይቅም። መፍትሔውም ጦርነት ውስጥ በመግባት ሳይሆን በአመራር፣ በሰላምና በሀሳብ በማሸነፍ ነው” ስትል ተናግራለች።

በቅርቡ በጌታቸው ረዳ የተመሠረተው ስምረት ፓርቲ ከቲፒኤፍ ጋር በጥምረት እየሠራ ይገኛል። ይህንን አስመልክቶ የፓርቲው ቃል አቀባይ የሆነው ረዳኢ ሃለፎም “(ከቲፒኤፍ) ጋር የምንለያይ ቢሆንም ግባቸውን እኛም እንጋራለን፤ የነሱ ሕልም ቀጣይ ደም መፋሰስን ማስቀረት ስለሆነ ከትግራይ ጋር የተስማማ ነው” ይላል።

“ትህነግ በቅርቡ በፈቃዱ ከሥልጣኑ ይለቅቅ ይሆናል፤ አለበለዚያ ግን ከፌዴራል ጋር ሆነን በግድ እንዲለቁ እናደርጋለን” ይላል የ29 ዓመቱ ዮሐንስ ወልዳይ። ይህንኑ ሃሳብ በማጠናከር ሸዊት ቢተው ስትናገር “በርግጥ ፍርሃት አለብኝ – ትግራይ እስካሁን አልፈወሰችም፤ እኛ ጦርነት አንፈልግም፤ ግን ደግሞ ምንም አማራጭ የለንም … ሚሊዮኖችን ለመታደግ ጥቂት መቶዎች መሰዋታቸው አስፈላጊ ይሆናል” ትላለች።

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Left Column, Politics Tagged With: afar, getachew reda, operation dismantle tplf, simret, tdf, TPF

Reader Interactions

Comments

  1. Tesfa says

    July 24, 2025 02:34 pm at 2:34 pm

    አሳዛኙ የሃበሻ ፓለቲካ መልኩን እየቀየረና እያስቀየረ እንሆ ዛሬም ግብ ግብ ላይ ነው። መቼ ይሆን በንግግር ነገሮችን ፈትተን በሰላም ወጥተን የምንገባው? ዝንተ ዓለም የባሩድ ሽታ እንዳሸተቱ መኖር እንዴት ባለ ስሌት ነው መኖር የሚባለው? በቅርቡ የኤርትራው የእድሜ ልክ መሪ በሰጠው ትረካ አሁንም ያዙኝ ልቀቁኝ ኢትዮጵያ ልትወረኝ ነው እያለ የራሱን የውስጥ ችግር መሸፈኛና የዓረቡን ዓለም ድጋፍ መለመኛ ሰበብ ስለሚሆንለት ይመቸው። ተናግሮ የማይደክመው የውሽት ቋትና ጥቁር ጠል የሆነው ትራምፕ ስለ ግድቡ ይህን ተናገረ ብለው ሰዎች ሲቀባጥሩ መስማት ያሳዝናል። ትራፕ የማይገባበት የዓለም ጉዳይ የለም። ግን ከእውቀትና ከመረዳት ሳይሆን እንዲሁ በነሲብ ከማውራት ነው። በዚህ ሰው ዙሪያ ገና ብዙ ነገር እናያለን። ግን እርሱ ያለውን እንደ ገደል ማሚቶ እየተቀበሉ ማስተጋባት ወይም በተናገረው ምክንያት እንቅልፍ ማጣት ጭራሽ አያስፈልግም። የውድቀት መጀመሪያ ትዕቢት ነው። ዝም ብሎ ለጠበቀ ብዙ ነገር እናያለን እንሰማለን። አሜሪካ የተማታባት ሃገር ሆናለችና!
    ታዲያ የትግራይ ታጣቂዎች ለሁለት ተሰንጥቀው አንድ ሌላውን ናና ግጠመኝ ማለቱ የሚያሳዝን እንጂ እሰየው የሚያሰኝ ጉዳይ አይደለም። ትላንት ያለቁት የትግራይ ልጆች ተረስተው እንደገና ጦርነትን ለመጫር በዚህም ሆነ በዚያ በኩል ሃተፍተፍ ማለት የህዝባችን ሰቆቃ ጣራ ለማውጣት የሚደረግ እብደት ነው። አማራም ታጣቂ/ኦሮሞውም ታጣቂ/ሌላውም እንዳሻው በሆነባት በዚህች የሃበሻ ምድር ላይ ቀኑ መቸ ነው ሰላም ሰፍኖ ህዝቡ አንገቱን ቀና አርጎ ሰርቶ የሚኖረው? የመቀሌው ወያኔ ከሻቢያ መጠጋቱ የጨነቀው እርጉዝ ያገባል እንዲሉ እንጂ ሁለቱ ነቀዞች በበረሃም ይሁን በገጠር ተስማምተው አያውቅም። ግን ያው የሞት ድግስ ለመደገስ ሁሌም ይግባባሉ። ስናሳዝን። ያለ ጦርነት ሙያ የሌለን ጅሎች። ወንድምና እህታችን ገድለን በአስከሬናቸው ላይ እያጨበጨብን የምንዘፍን የቁም ሙቶች። እኔ ባደኩበት ባህል ጎረቤት እንኳን ሃዘን ላይ ከሆነ ሬዲዪ አይከፈትም ነበር። እነዚህ አውሬዎች ከበቀሉ በህዋላ ሰው በሰውነቱ መለካቱ ቀርቶ ብሄርና ቋንቋው መለያው ሆነ። የእንስሳት ዓለም ይሉሃል ይሄ ነው።
    ጥቁሩ ዓለም ቡጢ ጨብጦ ኑና ላሳያችሁ ከማለት ይልቅ ራሱን ፈትሾ ለሰላም እጥፍ መንገድ ሂዶ ለሃገርና ለወገን ሲባል ነገርን በይቅርታ ለውጦ ቢራመድ የት በደረሰ ነበር። ግን ያ አልሆነም። ጊዜው የሚፎከርበት ጊዜ ሳይሆን የምናፍርበት ጊዜ ነው። ህዝባችን በቀን አንዴ እንኳን በልቶ ማደር ያቃተው ጊዜ ላይ ነን። ስለሆነም በሃራ ምድር ያሉት ታጣቂዎችም ሆኑ የደብረጽዪን ቡችሎች ባይናከሱ ይመረጣል። ግን ወያኔ ያለ ጦርነት መኖር አይችልም። ከባህር እንደ ወጣ አሳ መተንፈስ የሚሳነው ወያኔ ሰላም ሲኖር ነው። ጦርነት ጠማቂው ወያኔ ለትግራይ ህዝብ መከራ አዝናቢና ለሃገር በሽታ ነው። ይሁን በዚህም በዚያም ፎክሩ/አፋክሩ ተፋለሙ/ተገዳደሉ/ትርፉ ባዶ ነው የሚሆነው። ሰው በሃገሩ ላይ ተቀምጦ ሃራ መሬትና የጠላት ይዞታ እያለ ሲያወራ አያሳዝንም። ነው ወይስ ጣሊያን ለ3ኛ ጊዜ ወረረን? የቁም ሙቶች እኛ ነን። የሞቱት ይህን ጉድ አያዪምና ህያዋን ናቸው። በመጨረሻም መፋተግ/መገዳደል እንደማይረባ አንድ ነገር ላካፍላችሁና ይብቃኝ።
    እነርሱም ይላሉ ከተኮስን አንስትም። እኛም እንላለን ቃታ አናስከፍትም
    ይሄን ብለን ብለን የተገናኘን ቀን አሞራ ተሰብሰብ ትበላለህ ድለት!

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የተንጋደደው የገዱ መልስ February 6, 2026 03:05 pm
  • ሻዕቢያ “አክሱም ገብቶ ወጣቶች በጅምላ ሲረሽን ጸብ ተፋፍሟል …” February 4, 2026 01:15 pm
  • አደራ ጠባቂው የኢሉአባቦር ሕዝብ February 4, 2026 12:14 pm
  • የአውሬው ሪፖርተር ቀላቢዎች፡ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን January 28, 2026 09:56 am
  • በአሜሪካ ጥምር ዜግነት እንዲቀር ጥያቄ ቀረበ January 27, 2026 03:05 pm
  • “ከህወሓት፣ ከሻዕቢያ፣ ከግብፅ ሰዎች ጋር ሆኖ እንዴት የአማራን ጥያቄ ማስመለስ ይቻላል?” ኮሎኔል ፈንታው January 25, 2026 04:23 am
  • የኢትዮጵያ አየር ኃይል: ለአፍሪካ ሀገራት የመጀመሪያዎቹን የአየር ኃይል አብራሪዎች ያሰለጠነ ተቋም January 25, 2026 03:50 am
  • የአማረ ሪፖርተር እያደረሰ ያለው የብሔራዊ ደኅንነት አደጋ January 22, 2026 01:56 am
  • የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የማርያምን ማዕረግ ዝቅ አደረገች December 12, 2025 09:27 pm
  • ኢህአፓ: ከነጭ ሽብር ወደ “አዲስ አበባ ትናገር” የጎዳና ሽብር? December 12, 2025 09:11 pm
  • EOC Bans Haile Gebrselassie Over Are­qie Comments Linked to Doping November 21, 2025 07:47 pm
  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2026 · Goolgule