
በ116ኛው የሠራዊት ቀን ሲከበር ንግግር ያደረጉት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ “ዐጼ ምኒልክ የጦር ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት ያቋቋሙበትን ቀን የሀገር መከላከያ ሠራዊት ቀን ኾኖ እንዲከበር ተደርጓል” በማለት ቀኑ ለምን እንደተመረጠ ይፋ አደረጉ።
ከዚህ ሌላ ፊልድ ማርሻሉ በንግግራቸው፤
ሉዓላዊነቷ ተጠብቆ ከጀግኖች የተረከብናትን ኢትዮጵያ እንደተከበረች እና ማንነቷ እንደተጠበቀ ለማስቀጠል ወታደራዊ ዝግጁነታችንን አሳድገንና ቁመናችንን አዘምነን ማንኛውንም ተልዕኮ በላቀ ብቃት ለመፈጸም ሠራዊቱ ዝግጁ መሆኑን አሣውቀዋል።
የሠራዊቱ አባላት የተሠጣቸውን ታላቅ አደራ በድል ለመወጣት የመፈጸም ብቃታቸውን በማሣደግ በዓላማ ጽናታቸው እንዲቀጥሉ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ አሳስበዋል፡፡
ሠራዊቱ ሀገሩን እና ህገ መንግስታዊ ሥርዓቱን በመጠበቅ ረገድ ሄላፊነቱን በብቃት እየተወጣ መሆኑን የገለፁት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ የታጠቁ ኃይሎችን እና ኢ- መደበኛ አደረጃጀቶችን ወደ ሕጋዊ መስመር ለማስገባት እየተሠራ ያለው በሱዳን የተከሰተው ችግር በኢትዮጵያም እንዳይደገም በማሰብ መሆኑንም አስገንዝበዋል፡፡
የምድር ሃይል፣ የአየር ሃይል ፣ የባሕር ሃይል እና የሳይበር ኃይሎቻችንንም ዘመኑን እና ኢትዮጵያን በሚመጥኑ መልኩ እየገነባን የተሻለ አስተማማኝ ደረጃ ላይ ማድረስ ችለናልም ብለዋል።
የካቲት 7 ቀን 1987 ዓ.ም የሠራዊት ቀን ሆኖ እንዲከበር መወሰኑ ወገንተኝነት የፈጠረው አንዱ ታሪካዊ ስህተት መሆኑንም አንስተዋል።
ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ የተሳሳተውን ውሳኔ በማሥተካከል የኢትዮጵያ ዘመናዊ ሠራዊት እንደ ተቋም የተመሠረተበት ቀን ጥቅምት 15 እንዲሆን መወሠኑን ተናግረዋል። በመሆኑም “ዐጼ ምኒልክ የጦር ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት ያቋቋሙበትን ቀን የሀገር መከላከያ ሠራዊት ቀን ኾኖ እንዲከበር ተደርጓል” ብለዋል ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ።
ጥቅምት 15 ቀን 1900 ዓ.ም ዳግማዊ አጼ ምኒልክ ፊታውራሪ ሀብተጊዮርጊስ ዲነግዴን (አባ መላን) የመጀመሪያው የጦር ሚኒስትር አድርገው የሾሙበት እና ሠራዊቱ ዘመን ተሻጋሪ እንዲሆን መሠረት የጣሉበት መሆኑን የጠቆሙት ፊልድ ማርሻሉ፣ ፊታውራሪ ሀብተጊዮርጊስ ዲነግዴ ሠራዊቱ ዘመን ተሻጋሪ ሆኖ እንዲቀረፅ በሳል አመራርነት ሰጥተዋል ብለዋል።
116ኛው የሠራዊት ቀን ለሀገራቸው በየዘመናቱ መስዋዕት የከፈሉ ጀግኖችን የምንዘክርበት ቃላችንን የምናድስበት እና ይበልጥ ለማንኛውም ተልዕኮ የምንነሳሳበት ዕለት ነው። (የመከላከያ ሠራዊት ቴሌግራም)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
መቸውንም ቢሆን ያለፈ ነገርን እየናድ ሃገር መገንባት አይቻልም። ማርሻሉ አጼውን ማውሳታቸው መልካም ነገር ነው። የሃገራችን የያኔም ሆነ የአሁን ችግር የዘረኝነት በሽታ ነው። ሰው ዛሬን እንጂ ነገን አለማየት። እርግጥ ነው ወያኔና ሻቢያ የከተማ አለቆች ከሆኑ ጀምሮ ነገሮች ሁሉ ከፍተዋል። ዛሬም በትግራይ ውስጥ ወያኔ የሚሰራው ክፋት ማቆሚያ የለውም። የሚገርመው ግን አሜሪካም ከወራታት በህዋላ ዛሬም ወያኔን አይዞህ ለማለት ወደ መቀሌ መመላለሳቸው ነው። የወያኔን የፕሮፓጋንዳ ሚዲያ ላዳመጠ ሰውን ሃዘን አስቀምጦ ሌላ ጦርነት ቀስቃሽ ፕሮፓጋንዳ እንደሚነዙ በግልጽ ያሳያል። እብደታችን መቼ ይሆን የሚቆመው? በየስብሰባውና በየጎዳነው የትግራይ (ወያኔ) ባንዲራን እያውለበለቡ ሃገር ነን ማለታቸውን ዛሬም አልተውም። የሃገሬ ሰው እንደሚለው ” ሲኖሩ ልጥቅ ሲለዪ ምንጥቅ ነው” ዝም ብሎ ሲደላ ኢትዮጵያዊ ነን ሲከፋ ትግራይን ሃገር እናረጋለን እያሉ ሰውን ማወናበድ አስፈላጊ አይደለም።
በወያኔ ጊዜ የነበረው የኢትዮጵያ ሰራዊትና አሁን ላይ ከተዋቀረው የሰራዊት አሰራርና ጥንካሬ የተለየ አይደለም የሚሉን ተጨፈኑና ላሞኛችሁ የሚሉ የፓለቲካ ስልቦች ናቸው። ለውጥ አለ። ለውጡ ግን ገና ብዙ ሥራ ይቀረዋል። ምድሪቱ በዘርና በቋንቋ የተሰመረውን የአፓርታይድ የክልል ፓለቲካ ህገ መንግስቱን በማሻሻል እስካልተቀረፈ ድረስ መገዳደላችን ይቀጥላል። አሁን በፋኖና በመከላከያ መካከል የሚደረገው ፍልሚያ ጭራሽ መሆን የማይገባው የእብደት ሥራ ነው። መቆም አለበት። የብልጽግናው መንግስትም የጊዜው የኑሮና የፓለቲካ ጫና ያስነጠሰውን ሁሉ መንግስቴን ልትንድ ነው በማለት ማስርና ማሰቃየቱን ማቆም አለበት። ለመገዳደልና ጥይት ለማጮህ የምንቸኩለውን ያህል ለሥራ ለሰላም ብንተጋ ዛሬ ሃገሪቱ የት በደረሰች። ግን በዚህች ምድር ላይ ለሚኖረን አጭር ጊዜ ስንቶችን አስለቅሰን፤ ቀምተንና አሳዝነን ሁሉም ወደማይቀርበት ዓለም እንሻገራለን። በእኔ እምነት ብሄርተኞች የቁም ጅሎች ናቸው። በሌላው ደምና እንባ የሚነግድ። እስቲ የፍልስጤሙ ሃማስ አሁዶችን በማጥቃቱ ያተረፈው ምንድን ነው? ሰቆቃና ዋይታ! በዚህ ግጭት የተነሳ ገና ብዙ ጉድ ይፈጠራል። የሱዳንን የእርስ በእርስ ጦርነት ከቅርብና ከሩቅ ሆነው ነዳጅ የሚያርከፈክፉበት አረቦችና ነጮች ስለ ሱዳን ህዝብ አይገዳቸውም። አንዲት ምላስ የምታክል ምድር ግን ስትወረር ዓለም ሁሉ አብሮ ያለቅሳል? ግን ለጥቁር ህዝብ አረቡና ነጩ አይገደው? ገጣሚው እንዳለው
ብርሃንን ፍለጋ እልፎች ሲሯሯጡ
ሰላም ሰላም ብለው ጦርን እየጫሩ
ዞረው ተመልሰው አዛኝ አንጓች ሆነው
አፍርሰው ገንብተው ደግመው እየናድ
የኋሊት አስኬድን ቀን እየቆጠሩ
እኛም የጅል ጅሎች አብረን እየዶለትን
ቤታችን ፈረሰ ሰላም ሰላም እያልን።
የአሁኑ የኢትዮጵያ መከላከያ ካለፉት ወታደራዊ ውድቀቶችና መመናመን ትምህርት ሊቀስም ይገባል። በተለይም ወያኔ በዘሩና በቋንቋው ላ ዕላይና ታህታይ መዋቅሩን ሁሉ በወታደራዊ መስኩና በኢኮኖሚውም መያዙ ከመፈንገል እንዳላስጣለው ሁሉ የብልጽግናው መንግስትም ከዚያ ውድቀት ተምሮ ኢትዪጵያ |2| የሚሸት ለሃገሩና ለወገኑ የሚዋደቅ ሰራዊት መገንባት አለበት። በሃይማኖትና በቋንቋ እንዲሁም በክልልና በብሄር የተደራጀ ሃይል መፈራረሱ አይቀሬ ነውና ከታሪክ እየተማሩ በመራመድ ነገሮችን ማሳመር ከአሁኑ የኢትዮጵያ ሰራዊት የሚጠበቅ ነው።፡