
መረራ – ሲያልቅ እጅ ሰጡ!!
ኦነግን ይዞት በነበረው አቋም አማካይነት ፍጹም እንደማይነሳ አድርገው የቀጠቀጡት ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና ናቸው። “ኦሮሞ ግንድ እንጂ ቅርንጫፍ አይደለም ” ሲሉም የኦሮሞን አካታችነትና ታላቅ ሕዝብነት በማስረገጥ የጎጥ ፖለቲካ ረብ የለሽ መሆኑንን በጥናት አስደግፈው ኦነግን ያኮሰሱት መረራ፤ ኦነግ ውጤት እንደማያመጣም ተናግረው ነበር። ዛሬ ግን “ተመልሰው ለኦነግ እጅ ሰጡ” ሲሉ ወዳጆቻቸው ሳይቀሩ እየወቀሷቸው ነው።
የአምቦ ክፋይ በሆነችው ጊንጪ የተለኮሰው የኦሮሞ ትግል አድማሱን አስፍቶ ወደ ሌሎች ክልሎችም ተስፋፍቶ በጥምረት ለውጤት ሲበቃ፣ ላለፉት ሃምሳ ዓመታት ሲንከላወስ የነበረውና ተፈረካክሶ በየአቅጣጫው የተበተነው የኦነግ አመራሮች ወደ አገር ቤት “በጀግንነት” የመግባት ዕድል ተጎናጸፉ። እናም የድል አጥቢያ አርበኛ ሆነው የጠመንጃውንና የሰላማዊ ትግሉን አቀላቀለው ግልቢያውን አጦፉት።
ጃዋር መሐመድ ፈራ ተባ እያለ በቅርቡ የኦፌኮን ፓርቲ መቀላቀሉን ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ወዲያውኑ የተሰማው የመረራ እጅ መስጠትና የሸዋ ድምጽ ጉዳይ ነበር። በምርጫ ወረዳዎች ብዛትና በሕዝብ ቁጥር ሰፊ የሆነውን መካከለኛውን ኦሮሚያ ድምጽ ለመጠቅለል ታስቦ የተሰላው ስሌት “የመረራን ፓርቲ የተቀላቀልኩት የሸዋን ድምጽ ለመሰብሰብ ነው” ሲል ጃዋር ማረጋገጡን የዜና ሰዎቻችን ሰምተዋል።
ጃዋር ኦፌኮን ከተቀላቀለ በኋላ በእንግሊዝኛ ከሚታተመው አዲስ ስታንዳርድ ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ “አሁን ኦፌኮን ተቀላቅለሃል፤ ለምርጫ ትወዳደራለህ?” በሚል ለቀረበለት ጥያቄ ምንም ሳያቅማማ “ያለ ምንም ጥርጥር” በማለት መልሷል። ለጨፌ (ኦሮሚያ ምክርቤት) ይሁን ለፌዴራል ፓርላማ እንደሚወዳደር ለተጠየቀው በመለስ ዜናዊ ስልት “እሱን ፓርቲው ነው የሚወስነው” በማለት ምላሽ ሰጥቷል። የአሜሪካ ዜግነቱን ለመተውና ኢትዮጵያዊ ዜግነትን ለመቀበል በሒደት ላይ መሆኑን የተናገረው ጃዋር ኦፌኮ አዲስ የፓርቲ ፕሮግራም እንደሚያወጣና በዚያም ውስጥ እርሱ እጁ እንዳለበት ለተጠየቀው ከፓርቲው ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች እንዲሁም ከመሪው ፕሮፌሰር መረራ ጋር ላለፉት 16 ዓመታት ሲሠራ እንደቆየ ተናግሯል። ኦፌኮን በተራ አባልነት የተቀላቀለ መሆኑን በቃለ ምልልሱ የተናገረው ጃዋር ወደ ፓርቲው ከገባ ጥቂት ቀናት በኋላ የኦነግ ሸኔ ዳውድ ኢብሣ፣ የኦብፓ ከማል ገልቹ ከኦፌኮ መረራ ጉዲና ፓርቲ ጋር ጥምረት አደረጉ በተባለበት ወቅት ዋና አጣማሪና ከፍተኛ የፓርቲው ባለሥልጣን ሆኖ መቅረቡ ይታወቃል።

በቀጣይም የኦነግ ሸኔ መሪ ዳውድ ኢብሳ፣ ጃዋር መሃመድና ከማል ገልቹ አንድ ጠረጴዛ ላይ ሆነው ጥምረት መፍጠራቸው በጃዋር ሚዲያ ሰፊ ሽፋን ያገኘውም የሸዋን ድምጽ ለመሰብሰብ ከማሰብ መነሻ እንደሆነ ለመረዳት ተችሏል። ዜናው የጥምረቱን ታላቅነት አግንኖ በድጋፍ አስተያየት አጅቦ ቢያጮኸውም ጉምቱው ፖለቲከኛ ፕሮፌሰር መረራ አጣብቂኝ ውስጥ እንደሚገቡ ለጎልጉል ቅርብ የሆኑ አስታውቀዋል። በጥቅሉ ስምና አካባቢ ሳይጠሩ “እነሱን አናምናቸውም” ነው ያሉት። ሌላው ደግሞ ከትግራይ ህዝብ ነጻ አውጪ ግንባር (ትህነግ) ጋር የሚደረገው የጀርባ ጨዋታ በኦሮሞ ደም የመነገድ ያህል መሆኑ “አናምናቸውም” የሚሏቸውን ክፍሎች ማንነት ከወዲሁ በግልጽ የሚያሳይ ሆኗል ባይ ናቸው።
በቅርቡ አምቦ ስታዲየም ዳውድ ኢብሳን ለመቀበል በርካታ ሕዝብ ወጣ በሚል የትህነግ/ህወሃት ሚዲያ ማሰራጫዎች በስፋት የዘገቡት ዜና የችግሩ ማሳያ እንደሆነ አስተያየት ሰጪዎቹ ይናገራሉ። አምቦ አዲስ ከተማ እንደሚኖር የሚናገረው ጋዲሳ ወደ አምቦ ስታዲየም የሄደው ፕሮፌሰር መረራ እንደሚመጡ በቅስቀሳ ወቅት ተነግሮ ስለነበር ነው።
ቀደም ባሉት ጊዜያት በባዶ አዳራሽ ስብሰባ ሲያካሂዱ የነበሩት ዳውድ፣ አምቦ ያንን ያህል ሕዝብ በተሰበሰበት ጉባዔ መገኘታቸው እንዳስገረማቸው መናገራቸውን ያስታወሰው ጋዲሳ “መረራ የሉም ሲባል በርካቶች ተመልሰናል” ብሏል። ድራማው ግን አሁን ተደረገ ለተባለው ጥምረት ማመቻቻ መሆኑ ዛሬ ላይ ግልጽ እንደሆነለት ጠቁሟል። እሱ ብቻ ሳይሆን በበርካቶች ዘንድም የመወያያ ርዕስ ሆኗል።
ጃዋር መሃመድ ወደ ምርጫ እንደማይገባ ለጀርመን ሬዲዮ በተናገረ በአጭር ጊዜ ውስጥ ኦፌኮን በይፋ መቀላቀሉ “ለጠቅላይ ሚኒስትርነት እወዳደራለሁ” በሚል ንግሥናውን የሚያሳይ ፖስተር አሠርቶ ከፍተኛ ገንዘብ ከሰበሰበ በኋላ ዓቋሙን መቀየሩ በፈጠረበት የውስጥ ለውስጥ ተቃውሞ ሳቢያ መሆኑ ታውቋል። ይህንን ባያደርግ ሁሌም በሚታማበት ራስን የመቀያየር ችግር ክፉኛ የተዓማኒነት ችግር እንዳያጋጥመው ሰግቶ እንደሆነ በቅርብ የሚከታተሉት ይናገራሉ።

“የሸዋን ድምጽ ለማግኘት” በሚል ሂሳብ ኦፌኮን የተቀላቀለው ጃዋር በሸዋና በመካከለኛው ኦሮሚያ ይህ ስሌቱ እሱ እንዳሰበው ሊሄድ እንደማይችል ጋዲሳ ያስረዳል። ባያብራራም እነሱም እኛም የምናውቀው እውነት አለ ይላል።
በቡራዩ ገፈርሳ አካባቢ ነዋሪ የሆነው ታምሩ እንደሚለው እነ ዳውድን መምረጥ የማይታሰብ ነው ይላል። ሲያስረዳም “የዛሬ ሃምሳ ዓመት ገደማ ምዕራብ ሸዋ የተጀመረው የኦሮሞ ትግል በወለጋ የአንድ ቀበሌ ሰዎች ተጠልፎ ውጤት ሳያመጣ አርጅቶ ተፈረካክሷል። ይህ የአንድ ቀበሌ ልጆች የሚመሩት ትግል በጊንጪ ልጆች ትግል ወደ መደበኛው የትግሉ መነሻ ሰፈር ግብቶ በኅብረት ዛሬ ለተገኘው ድል በቅቷል። ይህንን ድል መልሶ ማስነጠቅ አይታሰብም” በማለት በቁርጠኝነት ይናገራል።
አባ ነጋ የሚመሩት ኦነግ ዩኒቲ (ኅብረት) ደጋፊ መሆኑንን የሚናገረው ሸንተማ ኅብረት መመሥረቱን ባይጠላም አካሄዱን “እስስታዊ” ሲል ይጠራዋል። የሸዋ ፖለቲከኞች አክራሪ ባለመሆናቸው ለኦነግ ዓላማ ስለማይመቹ፣ ኦሮሚያን በአክራሪዎች አመራር መዳፍ ስር ለማስገባት በሚል ኦፌኮ መጠለፉ ያሳዝነዋል። ኦፌኮ ውስጥ ያሉ አንዳንድ የበታች አመራሮች ከኦነግ ሸኔ ጋር ለመቀላቀል በጉባኤ ደረጃ የተወሰነም ሆነ የተደረገ ውይይት መኖሩን እንደማያውቁ መናገራቸውን አስታውሶ አሁን ተደረገ የተባለው ኅብረት ዕድሜ እንደማይኖረው ያምናል።
ሸንተማ እንደሚለው በአካባቢ ጠባብነት ስሜት የተነደፉ የኦፌኮ መሪዎች፣ በተለይም አቶ በቀለ ገርባ ኦፌኮን ወደ ወለጋ ሊጠቀልሉት እየሠሩ ነው። መረራም እጅ መስጠታቸው በስተመጨረሻ ሊረሳ የማይችል የጥፋት ታሪክ እንደሚመዘገብባቸው ያደርጋል።
“የእነ ታደሰ ብሩን ምስል ቢሮ በማስቀመጥ መቆመር ውሎ አድሮ ከምርጫ በፊት ይታወቃል” ያለው ሸንተማ እውነተኛዎቹ የቄሮ አመራሮች እነዳውድ ኢብሳ የአደረ አፋሽ ፖለቲካ ሲጫወቱ ዝም ብለው እንደማይመለከቱ ይናገራል።

መረራ በኦሮሞ ሕዝብ ዘንድም ሆነ በመላው የኢትዮጵያ ዜጎችና ፖለቲከኞች ትልቅ ክብር ያላቸው፣ በግልጽነታቸው የሚታወቁ፣ አክራሪ ኃይሎችን የሚያደባዩት፣ ጨዋና ደግ መሆናቸውን ለሚገነዘቡ ሁሉ ዛሬ የገቡበት ሰፈር ጉዳይ አስደንጋጭ ሆኗል። ሸንተማ ግን “ፕሮፌሰር መረራ የሸዋን ኦሮሞ የኃይል አሠላልፍ ጉዳይ እንደ አንድ ልምድ ያለው ፖለቲከኛ ረጋ ብለው እንዲያስቡ” ሲል ያሳስባል።
“መረራ ትህነግ/ህወሃት የኦሮሞን ልጆች፣ የትግል ባልደረቦቻቸውን፣ እሳቸውንና መላው የኢትዮጵያ ህዝብን እንዴት እንዳሰቃየ በአካል አይተዋል። በራሳቸው አንደበት መስክረዋል። እናም ዛሬ እሳቸው ጎን ሆነው በገሃድና በጀርባ ከትህነግ/ህወሃት ጋር ውል ለመፈጸም የሚሠሩ ኃይሎች አሸናፊ ሆነው እንዲወጡ ለማገዝ መተባበራቸውን ይወቁ። ይህም እሳቸውን ጨምሮ ነጻ ያወጣቸውን የኦሮሞ ደም ማሻቀጥ፣ በግልጽ በደሙ መቀለድ ነው” ሲል ሸንተመ አስተያየቱን ያጠቃልላል።
አዲስ አበባ ዙሪያ አስተያየት በማሰባሰብ የጎልጉል ዘጋቢ እንዳለው የሸዋን ድምጽ ወስዶ መንግሥት ለመመስረት እነ ጃዋር እያደረጉ ያለው ሙከራ በበቂ አደረጃጀት መላ ተበጅቶለታል። ውሎ አድሮ በገሃድ በሚታይ ደረጃ ጊንጪ የተለኮሰው የድል ችቦ ሃምሳ ዓመት ሙሉ ላይሳካላቸው እንዲደበዝዝ ወዳደረጉት ክፍሎች ሊሸጋገር ፈጽሞ እንደማይችል ቁርጠኝነቱ አለ።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ጃዋር መሃመድ የአሜሪካ ፓስፖርቱን በመመለሱን ጠቅሶ ምላሽ እየጠበቀ እንደሆነ አስታወቀ። ጃዋር በራሱ ኤል ቲቪ ከቀጠራት ሠራተኛው ጋር ካደረገው ውይይት ላይ ተቀንጥቦ በተሰማው የማስታወቂያ ምልልስ በቀናት ውስጥ ኢትዮጵያዊ እንደሚሆን ይፋ አድርጓል። ይሁን እንጂ ስለህግ መከበር ደጋገመው የሚሰብኩት መረራ ጉዲና የሚመሩት ፓርቲ ለጃዋር “ኢትዮጵያዊ” የሚል ዜግነት በማጎናጸፍ የመታወቂያ ወረቀት ሰጥቶታል። ይህ ሕገወጥ ድርጊት ሳይታወቅ በበታች አመራሮች ተደርጎ ከሆነም ፓርቲውን የሚመሩት ክፍሎች መልስ አልጡበትም። ጃዋር እንዳለው የአሜሪካ ዜግነት ይነሳልኝ ጥያቄ በቀናት የሚጠናቀቅ ሳይሆን በወራት የሚቆጠር ጊዜ የሚወስድ እንደሆነ ስለ አሠራሩ የሚያውቁ የሕግ ባለሙያዎች ይናገራሉ።
ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ™ ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ™ ንብረት ናቸው። ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (https://www.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን።
Leave a Reply