
ሰሞኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ 2.5 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጣውን፤ በ4 ወራት ይጠናቀቃል የተባለውን እና 3 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ማዳበሪያ በዓመት ማምረት ይችላል ተብሎ የተነገረለትን የማዳበሪያ (የዩሪያ) ፋብሪካ ለመገንባት ከዳንጎቴ ግሩፕ ጋር ስምምነት ሲፈረም በሰጡት አጭር መግለጫ ፋብሪካው እንደ ዓባይ ግድብ እንደማይሆን ተናግረው ነበር።
ይህ ፕሮጀክት “በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የሚመራ ስራቴጂክ ፕሮጀክት ነው፤ በከፍተኛ ዲሲፒሊንና ቁጥጥር የሚደረግ ነው፤ እንደ ሕዳሴ ግድብ ሜጋ ፕሮጀክት ነው፤ ሕዳሴ ላይ የነበረው ስህተት እዚህ አይደገምም፤ በጥንቃቄና በጥናት የተጀመረ ፕሮጀክት ነው፤ በዕውቀትና በጥንቃቄ ብቻ ነው የሚመራው፤ ምክንያቱም አንድ ፕሮጀክት መጀመራችን ሳይሆን በጥንቃቄ ካልመራነው ተጨማሪ ኃብትና ጊዜ ስለሚያባክን እንደዚህ ዓይነት ስህተት እንዳይፈጠር በጥንቃቄ ነው የምንጀምረው፤ በጥንቃቄ ነው የምንጨርሰው፤ ዋናው ማረጋገጥ የምፈልገው ነገር በተባለው ጊዜ ይህንን ፕሮጀክት እንጨርሰዋለን” ብለዋል።
መለስ ዜናዊ ስሙ በውል ያልታወቀውን ግድብ ሲያስጀምር፤
- መጀመሪያ ላይ የሚሊኒየም ግድብ ተባለ
- በኋላ ታላቁ ሕዳሴ ተባለ
- ግድቡን መገንባት የተጀመረው መጋቢት 24/2003 ዓ.ም.
- በአምስት ዓመታት ውስጥ ግንባታው ይጠናቀቃል ተብሎ ነበር
- ወጪው አራት ቢሊዮን ዶላር ወይም እስከ 4.7 ቢሊዮን ዶላር ይደርሳል ነበር የተባለው።
ይህ ያለ ዕውቀትና ያለ ዕቅድ መለስ ዜናዊ እንዳያልቅ አድርጎ ያስጀመረው ግድብ ለቀድሞውና አሁን ሕገወጥ ለሆነው ትህነግ ተሰጥቶ ሲሚንቶ ከኤፈርት (መሶበ)፤ ሥራው ደግሞ መርከብ በጠራራ ፀሐይ ሲሸጥ ለነበረውና ክንፈ ዳኘው ይመራው ለነበረው ሜቴክ ለተባለ ድርጅት ነበር የተሰጠው።
ከለውጡ በኋላ ሥራው ቆሞ የነበረውን የዓባይ ግድብ እንደገና ለማስጀመር ጥረት ሲደረግ በወቅቱ ከአራት ኪሎ የተባረረው ትህነግ የፈጸመው ግፍና በደል ይፋ መሆን ጀመረ። ምሥጢሩ እንዳይጋለጥበት የፈለገው ትህነግ፤ በገዳይ ስኳዶቹ ሰዎችን ማስወገድ፣ ሰነድ ማጥፋት፣ መረጃ መሰወር ጀመረ።
ሌላው ይፋ የሆነ ነገር ሥራውን እንደገና ለማስጀመር ኮንትራክተሩ ሳሊኒ በቢሊዮን ብር የሚቆጠር ያልተከፈለኝ ውዝፍ ዕዳ አለና ይከፈለኝ የማለቱ ዱብዕዳ ነበር። በመጨረሻም በተደረገ ድርድር 450 ሚሊዮን ዩሮ ወይም ወደ 28 ቢሊዮን ብር ተከፍሎት ሥራው እንደገና ተጀመረ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ልዩ ክትትል እየተደረገለትና በኮንስትራክሽን ሥራው ላይ በርካታ ለውጦች ተደርጎ አሁን ለምረቃ ደርሷል።
በዕውቀትና በጥንቃቄ ሳይመራ ቀርቶ ግድቡ ተጨማሪ ወደ 10 የሚጠጋ ዓመታትን አስጨምሯል፤ በመቶ ሚሊዮን የሚቆጠር ብር ተጨማሪ ወጪ አስወጥቷል፤ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ያገራችንን ዜጎች 10 ዓመት ሙሉ በጨለማ እንዲቆዩ አድርጓል፤ ለጎረቤት አገራት ተሽጦ የሚገባውን በቢሊዮን የሚቆጠር ገቢ አሳጥቷል።
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል መሥሪያ ቤት እንዳወጣው መረጃ ከዓባይ ግድብ ኃይል ሽያጭ፤ ባለፈው ዓመት 140 ሚሊዮን ዶላር፤ በዚህ ዓመት ደግሞ 300 ሚሊዮን ዶላር፤ ግድቡ ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቅ ደግሞ በዓመት አንድ ቢሊዮን ዶላር እንደሚያገኝ ተናግሯል።
ግምቱን በግማሽ ብናሳንሰውና ዓባይ ግድብ በዓመት 500 ሚሊዮን ዶላር ከኃይል ሽያጭ ያስገባል ብንል፤ በተባለበት ጊዜ ተጠናቅቆ ቢሆን ኖሮ ባለፉት 10 ዓመታት በትንሹ አምስት ቢሊዮን ዶላር ገቢ ከኃይል ሽያጭ ማድረግ ይቻል ነበረ። በሌላ አነጋገር ግድቡ ወጪውን ሸፍኖ ነበር ማለት ነው።
ያለ ዕቅድ፣ ያለ ዕውቀት የሚጀመር ሥራ ዕዳው ብዙ፤ ጉዳቱ የማይገመት ነው።
ከሚዲያው ሰፈር ደግሞ አንድ ጉዳይ እንጥቀስ። የዓባይ ግድብ ሥራ እንደማይቀጥል ብዙ ከተወራ በኋላ፤ የታሰበው አልሳካ ሲልና ግንባታው እንደገና ሲጀምር “ዐቢይ ሸጦታል”፣ “ዐቢይ ከግብፅ ጋር ተስማምቶ የኃይል ማመንጨት ዓቅሙ እንዲቀንስ ተደርጓል”፤ ወዘተ እየተባለ ሲነገር ቆየ። ይህም አልሳካ ብሎ ግንባታው እየተፋፋመ ሲሄድ ባንዳነትን ጌጥ ያደረጉና ለዶላር የተሸጡ በሌላ ሰበር ዜና መጡ።
የዛሬ አምስት ዓመት ከስድስት ወር ላይ ዋዜማ ሬዲዮ “ኢትዮጵያን ቋሚ ባለዕዳ የሚያደርገው የህዳሴ ግድብ ስምምነት ላይ መንግስት የመፈረም ፍላጎት እያሳየ ነው፤ ዋዜማ ራዲዮ የስምምነት ረቂቅ ሰነዱን አግኝታለች” ብለው በሰበር ኢትዮጵያን ሊሰባብሩ ሞከሩ። ጎልጉል በነጻ የሕዝብ አስተያየት ዓምዱ ጥያቄ አቀረበ፤ ዋዜማዎች በድፍረት ለጻፉት በስውር መልስ ሰጡ። መልሳችንን አታትሙብን ስላሉን አክብረን ዝም አልን፤ እነሱ ግን እስካሁን አግኝተነዋል ያሉትን “የስምምነት ረቂቅ ሰነድ” አላወጡም። ይቅርታም አልጠየቁም።
በወቅቱ ዋዜማ ከጻፈው ውስጥ አንድ አንቀጽ ብቻ ሕዝብ እንዲታዘብ ከዚህ በታች አቅርበነዋል፤
“ዋዜማ ራዲዮ ያገኘችው ኢትዮጵያ ግብጽና ሱዳን በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ አሞላልና ድርቅ ቢከሰት ማካካስ እንዲቻል በሚል እንዲፈርሙበት የተዘጋጀው ረቂቅ የስምምነት ሰነድ፣ ኢትዮጵያን ቋሚ የውሀ ባለ እዳ የሚያደርግ መሆኑን መረዳት ችለናል። በዚህ ረቂቅ ስምምነት ላይ ሁለት የኢትዮጵያን ጥቅም አደጋ ውስጥ የሚጥሉ ይዘቶች እንዳሉ ዋዜማ ራዲዮ ሰነዱ ላይ ከባለሙያዎች ማብራሪያን አግኝታለች። ሁለቱም አደጋዎች ያሉት ድርቅ፣ ተከታታይ ድርቅና ረጅም ዝናብ አጠር አመታት ቢከሰቱ የሚደረገው ማካካሻን የተመለከተው የሰነዱ አካል ላይ ነው።”
የዓባይ ግድብ 13 ተርባይኖች የሚኖሩት ሲሆን አጠቃላይ ኤሌክትሪክ የማመንጨት አቅሙ 5 ሺህ 150 ሜጋ ዋት እንደሚደርስ ተገልጿል። ይህም በአፍሪካ ትልቁ የሃይድሮ ኤሌክትሪክ አመንጪ ያደርገዋል።
ግድቡ 145 ሜትር ከፍታና ወደ ጎን ደግሞ 1,780 ሜትር ርዝመት ያለው ሲሆን፣ 74 ቢሊየን ሜትር ኪዩብ ውሃ ሙሉ በሙሉ ሲይዝም ውሃው የሚተኛበት ስፍራ ርዝመት 246 ኪሎ ሜትር (ከአዲስ አበባ ሻሸመኔ) እንደሚደርስ ከሰባ በላይ ደሴቶች እንዳሉት ተገልጿል።
የዓባይ ግድብ ያለ ዕቅድና ያለ ዕውቀት ቢጀመርም በዕቅድና በዕውቀት ተመርቶ ተጠናቋል። የዓባይ ግድብ የውኃ ጠብታ ጥርቅም ብቻ አይደለም የደም፣ የላብ፣ የዕንባ ጠብታም ነው።
ከዚህ በኋላ ኢትዮጵያ የውኃ ኒውክሊየር የታጠቀች፤ ማንም የማይደፍራት፤ ለሌሎች አፍሪካ ሀገራትና ለመላው የጥቁር ሕዝብ እንደ ዓድዋ የኩራት ተምሳሌት ሆናለች።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
ይህ ርዕሰ አንቀጽ የ“ጎልጉል: የድረገጽ ጋዜጣ™” አቋም ነው።





Leave a Reply