• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ይቅርታ ያደረገን ሕዝብ ማታለል አይገባም

December 1, 2022 01:22 pm by Editor Leave a Comment

ተሃድሶ ጥሩና መጥፎ ጎኖች አሉት። በተለይ ሥርነቀል አቢዮት በተለመደባት አገራችን ተሃድሶ ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች አሉት። ያንን መዘርዘር ግን አሁን አስፈላጊ አይደለም። የዚህ ርዕሰ አንቀጽ ዓላማ በተሃድሶ ምክንያት እየደረሰ ያለውና መረን የለቀቀ ተግባር እርምጃ እንዲወሰድበት ለመጠቆም ነው።

ትህነግ ያላሰበውን ሥልጣን ተቆጣጦሮ አዲስ አበባ ሲገባና ካድሬዎቹ የዲዛይነር ልብስ መልበስ ሲጀምሩ የተበላሸው ጭንቅላታቸው ያው በበረሃው እሳቤ ነበር የቀጠለው። ከዓመታት በኋላ የድርጅቱን መበስበስ እንደማያውቅ ሆኖ ያስደነቀው ሊቀጳጳስ መለስ ዜናዊ “እስከ እንጥላችን ገምተናል” ነበር ያለው። የዘራውን እንደሚያጭድ አለማሰቡ ዕውቀት ጸዴ በረኸኛ መሆኑን በራሱ አስመስክሮበታል።

ያገኙትን ሁሉ መዝረፍ ሙያቸው አድርገው የተካኑት ትህነጋውያንና ኢህአዴጋውያን ሊቀ ደናቁርት ካድሬዎች በለውጥ ስም ልክ እንደ ማብሪያና ማጥፊያ ተገለበጡና ተደመሩ። አሰሱም ገሠሱም “ግሙም” ሁሉም አብሮ ተደመረ፣ ተደማመረ፣ ተቀየጠ። ሕዝብም ይሁን ይቅር ብለናል፤ ከተሻሻላችሁ ላገራችን ስንል እንቀበላለን ብሎ ማራቸው።

ሆድ እንጂ ጭንቅላት የሌለው ካድሬ ምንም ይሉኝታና ምህረት አያውቅም። ዘረፋው፣ ሌብነቱ፣ ዘረኝነቱ፣ ቅሚያው፣ ቀጠለ። ከንቲባ አዳነች በቅርቡ እንደተናገሩት በተዘረፈ መሬት ላይ ሕንጻ የሚሠሩ ገና መሠረት ሳይጥሉ እንዳይታገዱ አስቀድመው የፍርድቤት ማዘዣ ያወጣሉ። ከዚህ በኋላ እኔ ነኝ ያለ ወንድ ግንባታውን አያስቆማቸውም።

በአገራችን ላይ መረን የለቀቀው ሌብነት፣ ምዝበራና ንቅዘት አሁን በይቅርታ ዝም ተብለው ከኢህአዴግነት ወደ ብልጽግና የተገላበጡ ካድሬዎችና አዲስ በተደመሩ የለውጥ ተረኛ ዘራፊዎች የተቀናጀ ተግባር ነው። እነዚህ ካድሬዎች የሚያውቁትና ዋነኛ የነበረው ሥራቸው ዝርፊያ ነው። ዘርፈው የፓርቲያቸውን ኅልውና እስካስቀጠሉና ወጥተው እስከለፈለፉ እይነኬ ናቸው። ኢህአዴግም እስከ ዕንጥሉ በስብሶ ይዟቸው ቆየ። ያለ እነሱ ኅልውናው አደጋ ላይ የሚወድቅ እንዲመስለው ራሳቸው ካድሬዎቹ አሳምነውታልና። 

ኃይለማርያም ደሳለኝ የአስፈጻሚውን ሥልጣን ሲቆጣጠሩ የመልካም አስተዳደር ችግር ነው በአገሪቷ የተንሰራፋው ብለው ካቢኔያቸውን በዶክተሮችና ፕሮፌሰሮች ሞሉት። በአሮጌ አቁማዳ አዲስ ወይን እንደመጨመር ሆነና ኢህአዴግ በለውጡ ተበላ። ከለውጥ ይልቅ ሥር ነቀል አቢዮት ቢደረገ ኖሮ ከነጻ እርምጃ እስከ እስር ይገባቸው የነበሩ ብዙዎቹ ተደምረው አመለጡ። አንዳንዶቹም እጅግ ዘግናኝና ሊታሰብ በማይችል ሁኔታ በአደባባይ የሚወገዱ ነበሩ። ካድሬ ግን ውለታ አያውቅም።

ባለንበት ወቅት ትህነግ የጫረው ጦርነት፣ የሸኔ ግፍ፣ የሲሚንቶ ዋጋ ያለ ምክንያት መናር፣ ከመጠን በላይ የደረሰው የኑሮ መወደድ፣ ጽንፈኝነት፣ ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል ዓይነት ተረኝነት፣ የረቀቀ ሌብነት፣ ወዘተ የተነጣጠሉና ምንም ግንኙነት የሌላቸው ናቸው ብሎ የሚያስብ ወይ ራሱ ሌባ ካድሬ ነው፤ አለበለዚያ ገዳም የራቀው ንጹህ የእግዜር ሰው ነው።

“በስብሰናል፣ ገምተናል” እያለ እንደ ደህና ነገር በሚዲያ ሲያወራ የነበረው ትህነግ/ኢህአዴግ የተገረሰሰው በግፍ ብዛት ነው። በመልካም አስተዳደር ዕጦት ነው። ብልጽግናም ይህ የኅልውና አደጋ ፊትለፊቱ ተጋርጧል። “ኅብረተሰቡ ሙሰኞችን ያጋልጥ፣ ኅብረተሰቡ ይተባበር፣” ወዘተ የምትለው የካድሬ አዝማች እየተነሳ ያለውን ቁጣ የማያበርድበት ደረጃ ላይ ደርሷል።

መንግሥት ከአናቱ ጀምሮ በየጉያው ሥር የተሸጎጡ ዘራፊዎችና ሌቦች እነማን እንደሆኑ ጠንቅቆ በማስረጃ ያውቃል። እዚህ እና እዚያ ጥቃቅንና አነስተኛ ጉቦ ተቀባዮችን እጅ ከፍንጅ ያዝኩ ብሎ ግዳይ እንደ ጣለ ጀግና በብሔራዊ ሚዲያ መለፈፍ የትም አያደርስም። ዓሣ መሸተት የሚጀምረው ካናቱ ነው እንዲባል ሌብነት የዕዝ ሠንሠለት አለው። ተዋረዱን ጠብቆ ካናት ነው እየተንቆረቆረ የሚወርደው፤ ስለዚህ ካናት መጀመር ነው አዋጪው።

ስለዚህ

  • መንግሥት በሥሩ የተሰገሰጉትን እና “ብልጽግናችን” እያሉ ቀን ተሌት ሕዝቡን የሚያደነቁሩትን ካድሬዎች ያሰናብት፤
  • በዘመነ ትህነግ በየሚዲያው ሲለፈልፉ ስናያቸው የነበሩ ደናቁርትን በጡረታም ይሁን በፈለገው መንገድ ከሥልጣን ያስወግድ፤
  • በሚኒስትር ማዕረግ እያሉ ጠቅላይ ሚ/ር ጽሕፈት ቤት ማጎር ሳይሆን ሌቦችን ከሲስተሙ ጠራርጎ ያጽዳ፣
  • በሌብነት ላይ የሚደረገው ዘመቻ መቀጣጫና ማስፈራሪያ እንዲሆን በካቢኔ ደረጃ ካሉ ታዋቂ ሌቦች ይጀመር፤
  • የካድሬ አሠራርና ሹመት በሜሪት ይቀየር፤ እነዚህ ጥቂቶቹ ናቸው።

ብልጽግና ለራስህ ስትል ስማ። ይህንን ካላስተካከልህ እንደ ትህነግ ሩብ ክፍለ ዘመን ሳይሆን የምትቆየው “ሕዝብን ላገለግል ተመርጫለሁ” ለምትልበት የአምስት ዓመት ሩብ መድረስህን ቀልብህ ይንገርህ።

ትህነግ ሲያሾረው የነበረው ኢህአዴግ የተገረሰሰው በመልካም አስተዳደር ዕጦት ነው። ኮሮና ነው፣ ጦርነቱ ነው፣ ዓለም አቀፍ የኑሮ ውድነት ነው፣ የነዳጅ መወደድ ነው፣ ይሄ ነው፣ ያ ነው እያሉ በምክንያት መኖር ለትህነግም አልበጀውም። ያንተም መጻዒ ዕድል ከዚህ አይለይም። ነግረናል ቤት ይቃጠላል ብለናል ብላለች ሴትየዋ።        

መደምደሚያ፤ ይህ ርዕሰ አንቀጽ ዋናው ሐሳቡ ኢህአዴግን ከተሃድሶው እንቅስቃሴ ጋር በማነጻጸር “ኢህአዴግ ማረኝ” ለማለት አይደለም። ትህነግንም ሆነ ኢህአዴግን የሚያስናፍቅ ምንም ነገር የለም። እንዲያውም ትውልድ የሚሻገር ውድመት በማምጣቱ መጪው ትውልድ ጠንቅቆ እንዲማርበትና ትህነጋዊ አስተሳሰብ ገና ሲያቆጠቁጥ እንዲቀጨው በየትምህርት ቤቱ በመጽሐፍ፣ በየቦታው በሐውልትና በየጊዜው በሚዲያ መነገር ያለበት ነው።

አሁን መከራ ለሆነብን ተቋማዊ ዝርፊያ ዓይን ያወጣ ሌብነት ዋናው ተጠያቂ ማን ሆነና ነው በንጽጽር “ትህነግ ማረኝ” የምንለው? ከዚህ ይልቅ አሁን በአመራር ላይ ያለው ኃይል የትህነግ/ኢህአዴግ ውላጅ በመሆኑ የሠራውን ግፍ ይቅር ብሎ ቀጥል ያለውንና ምሕረት ያደረገን ሕዝብ እየበደለ መሆኑ ዓይናችሁን ጨፍኑ ላሞኛችሁ ዓይነት ነው። ሕዝብ ምሕረት ያደረገው የተሠራውን ስላላወቀ ሳይሆን ብልሕ ሆኖ ነው። ይቅርታ ያደረገን ሕዝብ ደግሞ ማታለልና ደግሞ ግፍ መሥራት የትም አያደርስም። ይቅርታ የተደረገበት ፋይል አልተቃጠለም፤ ይቅርታውን ለሚንቅ የበደሉን መዝገብ መምዘዝ ብዙ የሚከብድ አይደለም።

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ


ይህ ርዕሰ አንቀጽ የ“ጎልጉል: የድረገጽ ጋዜጣ™” አቋም ነው።

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Editorial, Middle Column Tagged With: corruption, ethiopian terrorists, operation dismantle tplf, tplf terrorist

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ዘርፍ ባለሙያው ጃዋር ሌላ ጥሪ አቀረበ November 17, 2025 09:25 am
  • የ-አብሮነት ማኅበር የመረጠው ሕቡዕ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ይፋ ሆነ November 5, 2025 12:06 pm
  • “የኢሳያስ አፈወርቂ ውድቀት አይቀሬ ነው … “ፅምዶ” ራዕይ ዓልባ” ነው – ሼትል ትሮንቮል October 26, 2025 10:15 pm
  • አሜሪካ ስላልተቀበለችው ነው “የሽሽግር መንግሥት” ስብሰባው በአምስተርዳም ተካሄደው October 25, 2025 11:09 pm
  • በዓባይ ግድብ ምረቃ፡ የሕዝብ ደስታ፣ የቴድሮስ ካሳሁን ዝምታ September 14, 2025 04:27 am
  • ኢትዮጵያ የውኃ ኑክሊየር ማብላያዋን ልታስመርቅ ነው  August 29, 2025 11:46 pm
  • መከላከያ በፋኖ አመራሮች ላይ እርምጃ ወሰደ፤ ዘመነ በ“አንድ ማንኪያ ቅንነት” አንድ እንሁን አለ August 23, 2025 12:35 am
  • ፋኖን በፋይናንስና በሎጂስቲክስ የሚደግፉ የጎጃም ባለሃብቶች ከስደት ሊመለሱ ነው August 14, 2025 12:42 am
  • የበቀለ ገርባ የአሜሪካ ጥገኝነት ማመልከቻ ውድቅ ተደረገ August 13, 2025 12:16 pm
  • ሞዐ ተዋሕዶ “ነጻ አውጪ ግምባር” – ሞነግ August 13, 2025 12:58 am
  • የሃይማኖትና የመንግሥት ጥምረት በረከት ወይስ መርገም?  August 5, 2025 09:18 pm
  • የባከነ የስደት ሕይወት ከደባርቅ እስከ ኖርዌይ July 29, 2025 05:44 pm
  • “በዚህ ዓመት መጨረሻ ትግራይን እንቆጣጠራለን”፤ ቲፒኤፍ July 22, 2025 01:28 am
  • Rusted screws, metal spikes and plastic rubbish: the horrific sexual violence used against Tigray’s women July 4, 2025 01:48 am
  • በሞርሞን ቤ/ክ ዕርዳታ የኪዳነምህረት ኦርቶዶክስ ቤ/ክ ማምለኪያ ሥፍራ አገኘች July 2, 2025 01:28 pm
  • የበረከት ስምዖን “አየር ላይ ትዕይንት” አየር ላይ ተበተነ July 2, 2025 01:24 am
  • “ዐቢይ ይውረድ፣ እኛ እንውጣ፣ በተራችን እንግዛ” ስልቴዎች (ስብሃት፣ ልደቱ፤ ቴዎድሮስ) June 11, 2025 01:56 am
  • ኤሊያስ መሠረት የሚሠራው ለማነው? ለብጽልግና? ወይስ …? June 3, 2025 01:27 am
  • በግንቦት 20 – የሁለት መሪዎች ወግ May 28, 2025 02:01 am
  • በፈቃዳቸው የተመለመሉ ወጣቶች ሁርሶ ሥልጠና ጀመሩ May 22, 2025 09:11 am
  • ድብቁ ሤራ ሲጋለጥ – “ሦስትን ወደ አራት” May 21, 2025 01:01 am
  • ከትግራይ ሾልኮ የወጣው ምሥጢራዊው ሰነድ ምንድነው? May 20, 2025 09:18 am
  • በደቡብ ጎንደር በጸዳሉ ደሴ የተመሩት 72 ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጡ May 19, 2025 02:24 pm
  • የተመሠረተው የፋኖ አደረጃጀት ዋነኛ ዓላማው ድርድር መሆኑ ተነገረ May 14, 2025 11:07 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2025 · Goolgule