
* “እኛ የገባነው ልናፈርሰው ነው” ሕዝቅኤል ገቢሣ
በሰላማዊ ትግል መንግሥት ለመጣል ማቀዱን አስታውቆ ሃያ አንድ ቦርድ አባላትን ሰይሞ የሰነበተው የ-አብሮነት ማኅበር ሰባት ሥራ አስፈጻሚዎችን መምረጡ ታወቀ። ማኅበሩ “ለቦርድ አባላት” በሚል ባሰራጨው የ“እንኳን ደስ አላችሁ” መልዕክት አቶ ልደቱ፣ ከአማራ የማኅበሩ ፕሬዚዳንትና ሊቀመንበር ሆነዋል። መቅደስ አዳነ ከወላይታ (ምክትል)፣ አሸናፊ አብርሃም ከደቡብ (ጸሐፊ)፣ ሙሉጌታ ዘለቀ ከአማራ (ገንዘብ ያዥ)፣ የሕዝብ ግንኙነት ኦፊሰር ሕዝቅኤል ገቢሣ /በተለይ እንግሊዘኛና ትግርኛ ጠንቀቀው ስለሚያውቁ/ ከኦሮሞ፣ የድርጅት አስተባባሪ እስማኤል ጎርሴ ከሶማሌ፣ የውጭ ግንኙነት ኦፊሰር መስፍን አየነው ከትግራይ መመረጣቸው ይፋ አድርጓል።
ቀደም ሲል ምርጫው ከመደረጉ በፊት የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው አባላቶች ሕቡዕ እንደሚሆኑ ተመልክቶ እንደነበር የስብሰባው ተሳታፊዎችን ጠቅሰን መዘገባችን አይዘነጋም። ያለፈው ሳምንት ባለመግባባት ምርጫው ሳይካሄድ ከቀር በኋላ ሃሳብ ተቀይሮ ሕቡዕ እንዲሆኑ ተወስኖ የነበረው የሥራ አስፈጻሚዎች ዝርዝር ታውቋል።
በተከታታይ ለዲሲ የአዲስ ሪፖርተር ተባባሪ መረጃ የሚሰጡት ወገኖች እንዳሉት ከሆነ ሰኞ ዕለት በተካሄደው ምርጫ ቀደም ሲል አቶ ልደቱ በግል እንዳይመረጥ ቅስቀሳ ያደረጉበት የርዕዮት ሚዲያ ባለቤት ቴዎድሮስ ጸጋዬ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ሳይሆን ቀርቷል።
ቴዎድሮስ ባለፈው ሳምንት ባለመግባባት ምርጫ ማድረግ ሳይቻል በተበተነው ስብሰባ ላይ እጁን ሳያወጣ በተደጋጋሚ በመናገር ስብሰባውን በመበጥበጡ፣ ከሁሉም በላይ ግን ከሻዕቢያ ጋር ግንኙነት ያላቸውን አጥብቆ ስለሚቃወም፣ በተቃራኒው ሻዕቢያን የሚቃወሙትን ስለሚደግፍ ነበር አቶ ልደቱ በግል ስልክ እየደወሉ ምርጫ ውስጥ እንዳይገባ የቀሰቀሱበት።
ያለፈው ስብሰባ ከተበተነ በኋላ ቴዎድሮስ ሥራ አስፈጻሚ ውስጥ እንዳይመረጥ አቶ ልደቱ ካነጋገሯቸው መካከል ሁለቱ ለአዲስ ሪፖርተር እንዳሉት “ቴዎድሮስ ከሰማ የሚዲያ ዘመቻ ስለሚከፍትብን ምሥጢር ይሁን” ሲሉ አቶ ልደቱ መናገራቸውን አመልክተዋል። አቶ ልደቱን በግል ስልካቸው በማግኘት ለማነጋገር ተባባሪያችን ያደረገው ሙከራ አልተሳካም።
ፕሮፌሰር ሕዝቅኤል ገቢሣ ምርጫው እየተደረገ ሳለ “diversity (ብዘሃነትን) አትከተሉም” በማለት አስቀድመው ተቃውሞ አሰምተው እንደነበር የተናገሩት የመረጃው ባለቤቶች፣ ስብሰባው ካለቀ በኋላ እንደሰሙት ከሆነ መመረጣቸው ከተነገራቸው መካከል መልቀቂያ ያስገቡም አሉ። (የሕዝቅኤል ተቃውሞ ሰባት አባላት ባሉበት ቡድን ሁለት አማራ እንዴት ይሆናል ከሚል የመነጨ ነው በሚልም ተወስዷል)
ከአቶ ስብሃት ነጋና ከሻዕቢያ ሰዎች ጋር አብረው እንደሚሠሩ፣ በምስራቅ ኢትዮጵያ አቅጣጫ የተጀመሩ ሰፋፊ ፕሮጀክቶችን ለማስተጓጎልና ጦርነቱን ለማስፋት በግብጽ መሾማቸው የተሰማባቸው ሕዝቅኤል፣ ከሚቀርቧቸው ሰዎች ጋር ሆነው የ-አብሮነት እንደሚፈርስ ስብሰባ በተደረገ በአንድ ቀን ውስጥ መናገራቸው ተሰምቷል።
“እኔና መስፍን አየነው የገባነው ስብስቡን ለማፍረስ ነው” በማለት ፕሮፌሰሩ መናገራቸውን የሰሙት እነ አቶ ስብሃት ነጋ የሚመሩትን ቡድን የሚቃወሙ ሌላኛው የትግራይ ቡድን ደጋፊዎች ሲሆኑ፣ ሕዝቅኤል “አዲስ የተቋቋመ አደረጃጀት አለ። ከአብሮነት ውስጥ የሚፈለጉትን ወደዚያ እንወስዳለን። የ-አብሮነት ነገር አይታመንም። የሌሎችን መብትና ስብጥር አያከብርም” ማለታቸው ታውቋል። እሳቸውንም በግል ስልካቸው ለማግኘት በተደጋጋሚ የተደረገው ሙከራ አልተሳካም።
እነዚሁ የትግራይ ተወላጅ የሆኑ የመረጃ ምንጮች ለተባባሪያችን እንዳሉት ሕዝቅኤል አዲስ እየተመሠረተ ነው ያሉት አደረጃጀት እሳቸው ያሉበት ፕሮፌሰር ኤፍሬም ይስሐቅ ያደራጁትና እነ አቶ ስብሃት ነጋ፣ አምባሳደር ብርሃነ ገብረ ክርስቶስ ከኋላ የሚመሩት ነው።
ከሃያ አንዱ የቦርድ አባላት መካከል አንዱ የሆኑት አቶ ታምራት ላይኔ፣ አስቀድመው የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ለመሆን ፈቃደኛ ሆነው የነበሩ ቢሆንም፣ በሰላማዊና የትጥቅ ትግል ስልት ላይ ክርከር ከተካሄደ በኋላ በሰኞው ዕለት ምርጫ ርሳቸውን ከሥራ አስፈጻሚነት ተወዳዳሪነት ማግለላቸውን በስብሰባው የተካፈሉ አስታወቀዋል።
የ-አብሮነትን አብረው አጅበው የነበሩት እነ ጃዋር መሐመድ፣ አቶ በቀለ ገርባ፣ ኢተና ወዘተ የመሳሰሉት ሙሉ በሙሉ ራሳቸውን ማግለላቸውን ጠቅሰን መዘገባችን አይዘነጋም። ይህም የሆነው በአገር ውስጥ የኦሮሞ ተወላጆች በሰነዘሩባቸው ተቃውሞ መሆኑ አይዘነጋም።
ቡድኑ ሥራ ሲጀምር በአገር ውስጥ የሕቡዕ አደረጃጀት በማስፋፋት የተቃውሞና ዓድማ እንደሚያደራጅ አቶ ልደቱ በተደጋጋሚ መናገራቸው አይዘነጋም። የ-አብሮነት ከአገር ውስጥ አብሮ ካሉ የተወሰኑ ድርጅቶች ጋር እንደሚሠራ፣ አንዳንዶቹም በጅምሩ ወቅት በይፋ በዙም (Zoom) ስብሰባ ይካፈሉ እንደነበር የሚታወስ ነው። (አዲስ ሪፖርተር)
ጎልጉል፤ የድረገጽ ጋዜጣ




Leave a Reply