
ትላንት የትግራይ ክልል ጊዚያዊ አስተዳደር የቀድሞ ፕሬዜዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ “UMD” ለተባለ ሚድያ ዘለግ ያለ ቃለመጠይቅ ሰጥተዋል።
በርካታ ጉዳዮች ባነሱበት ቃለ-መጠይቃቸው “አሁንም ትግራይ መላ ቅጡ በማይታወቅ ሁኔታ ላይ ናት ፤ በርካታ የትግራይ ህዝብ በከፍተኛ ጭንቅና መከራ ውስጥ ይገኛል” ብለዋል።
ጥያቄ – በሁለት አመቱ የፕሬዚዳንትነት ቆይታህ ያልጠበቅከውና በጣም መጥፎ ነበር ብለህ የምትገልፀው አጋጣሚ አለ?
የጌታቸው ምላሽ – አዎ በጣም ያልጠበቅኩትና መጥፎ ነበር የምለው አለኝ። እኔን እስከማስወገድ ድረስ ፍላጎት እንደነበራቸው አላውቅም ነበር። መጨረሻ ላይ ግን ወደ አዲስ አበባ ለመሄድ ወደ ኤርፖርት ሳመራ እኔን አግቶ ለማስቀረት ሙከራ አደረጉ። ለማገት መሞከራቸው አይደለም እኔን ያበሳጨኝ። እኔ የተበሳጨሁት ሊገድሉኝ አቅደው እንደነበር ያወቅኩኝ ጊዜ ላይ ነው። ኋላ ላይ በደረሰኝ መረጃ መሠረት ሁለት የማከብራቸው ወታደራዊ አዛዦች “እንዴት አመለጠን ቀድመን ነበር እኮ ማስወገድ የነበረብን” ብለው በቁጭት እንዳወሩ አወቅኩኝ። ለነገሩ የሚታወቅ ባህሪ ነው። ኦሮሚያ ላይ ወይም ሌላ ቦታ ላይ ስታደርገው ከነበረ ትግራይ ወስጥም የማታደርግበት ምንም ምክንያት አይኖርህም።
ኬላ ጥሎ እኔን ለማገት ተልዕኮ ተሰጥቶት የነበረው አወጣኸኝ የተባለ የኮር አዛዥ ነው። እንደውም ኋላ ላይ ተልዕኮውን ባለመፈፀሙ አስረውታል። እኔን ለመግደል ዝርዝር ፕላን ያወጡትን ሰዎችን ሳይቀር አውቃቸዋለሁ። (ከአስፋው አብርሃ ቴሌግራም ገጽ የተወሰደ)
“በፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት መሰረት ጊዚያዊ አስተዳደሩ ሲመሰረት የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚንስትር ጦርነቱ በመምራት ከፍተኛ ሚና የነበረን 5 ስራ አስፈፃሚዎች ወደ ፕሬዜዳንት የኋላፊነት ቦታ እንዳንመጣ ፍላጎት ነበረቸው” በማለት ወደ ኋላ ተመልሰው አስታውሰዋል።
ይህን ሃሳብ እሳቸው ቢቀበሉትም የተቀሩት አራቱ ስራ አስፈፃሚዎች የጠቅላይ ሚንስትሩን ሃሳብ ውድቅ ማድረጋቸው ተናግረዋል።
“ጊዚያዊ አስተዳደሩ ለማቋቋም በአላስፈላጊ ክርክር አራት ወራት ፈጅተናል፤ በብዙ ውጣ ውረድ መጋቢት 21/2015 ዓ.ም ተቋቁሞ ፕሬዜዳንት ሆኜ መምራት ስጀምር በቀናት ውስጥ ‘ባንዳ’ የሚል ስያሜ ተለጠፈብኝ ” ሲሉ ተደምጠዋል።
አቶ ጌታቸው “በዚያው ዓመት ወርሃ ግንቦት የባሰውኑ ‘ከሃዲ’ ተባልኩኝ” በማለት ተናግረዋል።
“አራቱ የህወሓት ስራ አስፈፃሚዎች በየሦስት ወሩ ለማድረግ የሚፈቅደውን የድርጅቱ ውስጠ ደንብ በመጣስ በየሦስት ቀኑ ፍሬ በሌለው ስብሰባ በመጥመድ ከመንግስታዊ ስራ ውጭ እንድሆን አበክረው ሰርተዋል፤ በዚሁ ተማርሬ ኃላፊነቴ በራሴ ፍቃድ መልቀቅ ባለመቻሌ ተናደው እኔን ጨምሮ 16 የድርጅቱ ማእከላዊ ኮሚቴ አባላትን ‘ከሃዲዎች ከጂዎች’ ብለው በመፈረጅ አላሰራ አሉን” ብለዋል።
“የተቀረው የህወሓት የስራ አስፈፃሚ በፕሪቶሪያው የተኩስ ማቆም ስምምነት እንደ ሽንፈት የሚቆጥር፣ በተፈናቃዮች እጣ ፈንታ የሚቆምር፣ ጊዚያዊ አስተዳደሩ የተሰጡት ተልእኮዎች እንዳይፈፅም ከላይ እስከ ታች በእቅድ የሰራ አደናቃፊ” ብለውታል አቶ ጌታቸው።
አቶ ጌታቸው “ለውጥ የማይቀበሉ ፤ የተቸከሉ” ሲሉ የገለፁዋቸው የህወሓት 4ቱ ስራ አስፈፃሚዎች እሳቸው ወደ ጊዚያዊ አስተዳደሩ ፕሬዜዳንት በመጡበት ማግስት የሚሰራ በሌለበት 55 የድርጅቱ ሰዎች በምክትል የስራ ኃላፊ ደረጃ እንዲሾሙ ፕሮፓዛል እንዳቀረቡላቸው፤ ይህንን ያህል ቁጥር ያለው ስራ ሳይሰራ ደመወዝ የሚከፈለው አመራር ለመመደብ ቢቸገሩም ከክርክር በኋላ 35 በግድ መመደባቸው ገልጸዋል።
ድርጅታዊ ውስጥ ደንብ በመጣስ የ65 እና የ70 ዓመት ዕድሜ ያላቸው የማእከላይ ኮሚቴ አመራር እንዲሆኑ መመረጣቸው በርካታ ቁጥር ያለው አመራር ከሃላፊነት ምድብ ውጭ ሆኖም ቁጭ ብሎ በፊት የነበረው ደመወዝና ጥቅማ ጥቅም እንዲያገኝ የሚያደርግ እጅግ ዘግናኝ አሰራር ክልሉን ጠልፎ መጣሉ አቶ ጌታቸው ገልፀዋል።
“ጡረታ የማይፈቀድበት ክልል ቢኖር ትግራይ ነው” ያሉት አቶ ጌታቸው፤ ከጦርነቱ በፊት በ2012 ዓ.ም 800 ሚሊዮን ብር የነበረው የመንግስት ሰራተኞች ደመወዝ ጊዚያዊ አስተዳደሩ ተቋቁሞ ስራው በ2015 ዓ.ም ሲጀምር ከ1.2 ቢሊዮን ብር በላይ ማሻቀቡ በክልሉ ያለው ቅጥ ያጣ በልሹ አሰራር የሚያሳይ ነው ብለዋል።
“በትግራይ ያለው አሁናዊ ፓለቲካዊ ቀውስና ችግር ህወሓት ብቻውን ስልጣን እንዲቆጣጠር ያለው ያልተገራ ፍላጎት የፈጠረው ነው” ያሉት አቶ ጌታቸው “ይህንን ሁሉንም ነገር በብቸኝነት የመያዝ ያልተገራ የህወሓት ፍላጎት የማይሸከም በተግባር የተደገፈ ለውጥ በትግራይ መፈጠሩ ማሳያዎችን በመጥቀስ አስረድተዋል።
ከትናንት ወዲህ መጋቢት 26 ቀን 2017 ዓ.ም ከዱባይ ‘bird story agency’ ለተባለ ሚድያ በሰጡት ቃለመጠይቅ “በቅርቡ ወደ ኢትዮጵያ እመለሳሎህ ማለታቸው” ተከትሎ እሁድ ወደ አዲስ አበባ መመለሳቸው በአንዳንድ የማህበራዊ የትስስር ገፅ ተጠቃሚዎች ቢፃፍም ፤ ፕሬዜዳንቱ ለUMD ሚድያ በሰጡት ቃለ-መጠይቅ ስለዚሁ ጉዳይ ያሉት የለም።
NB. አቶ ጌታቸው ረዳ አራቱ ስራ አስፈጻሚዎች የጠቅላይ ሚኒስትሩን ሃሳብ ውድቅ እንዳደረጉ በገለጹበት አውድ ስም ባይጠቅሱም በይፋ የሚታወቁት ስራ አስፈጻሚዎች ፦
1. ደብረፅዮን (ዶ/ር)
2. ወ/ሮ ፈትለወርቅ
3. አቶ ኣለም ገብረዋህድ
4. አቶ ጌታቸው ኣሰፋ ናቸው። (ቲክቫህ)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply