
ለዓመታት በአገር ውስጥ የሙዚቃ ድግስ (ኮንሰርት) እንዳያሳይ የታገደው ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) አስመራ ላይ የሙዚቃ ድግስ ለማቅረብ ተስፋ እንደሚያደርግ ተናገረ። ችግሮቻችንን አራግፈን ወደፊት መጓዝ አለብን ብሏል።
ዴይሊ ሜይል አዣንስ ፍራንስ ፕሬስን ጠቅሶ እንደዘገበው በእርሱ ላይ እየደረሰ ያለው ነገር እንዳለ ሆኖ ቴዲ “በኢትዮጵያ ሰላምና አንድነት ላይ” ትኩረት ማድረግ መቀጠሉን ከአዲስ አበባ ወጣ ብሎ በሚገኘው ቤቱ ዘና ባለ ሁኔታ መናገሩን ዘገባው ጠቅሷል።
የልጅነት ዘመኑን በማስታወስ ቴዲ ሲናገር፤ “ልጅ ሆኜ እንደ አንድ አገር ስንኖር አስታውሳለሁ፤ አንድ የምናውቃት አገር ኢትዮጵያ የምትባል ነበረች፤ አሁን በዚህ ዘመን ግን የምንታወቀው በዘራችን ነው፤ ይህ ደግሞ እጅግ አደገኛ እየሆነ መጥቷል” ብሏል።
ህወሓት በቴዲ የጥበብ ሥራዎች ላይ ማዕቀብ በመጣሉ በተለይ ተደናቂነትን ያገኘው “ኢትዮጵያ” የተሰኘው አዲሱ አልበሙም ሆነ ቀደምት ሥራዎቹ እንደሌሎቹ ባለሙያዎች ህወሓት በተቆጣጠረው ሚዲያ ላይ አይሰሙም። አንዳንዶች ይህንን አስመልክተው ሲናገሩ፤ የቴዲ 17 መርፌ ሙዚቃም ይሁን እቴጌ ወይም ባልደራሱ ወይም ማር እስከ ጧፍ ሁሉም ህወሓትን ያስበረግጉታል።
“ጥቁር ሰው” የተሰኘው አልበሙ ህወሓት ከፈጠረው የዘር ፖለቲካ ጋር ተያይዞ በኦሮሞ ብሔረተኞች ዘንድ ስሙ እንዲጠለሽ ብዙ ተሠርቶበታል። እነ ጃዋር መሐመድ ያደረጉት የበቀል እርምጃ ከህወሓት እኩይ ተግባር ባልተናነሰ መልኩ የቴዲ ሥራ ለሕዝብ እንዳይቀርብ ብዙ እንቅፋትን ፈጥረው አልፈዋል። የቴዲ ኮንሰርት ስፖንሰር አድራጊ የነበረው ሃይኒከን ቢራ በዚህ ዘመቻ ምክንያት ራሱን ማግለሉ የሚታወስ ነው። (ይህንን አስመልክቶ ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ አትሞት የነበረውን ዘገባ ለማንበብ እዚህ ላይ ይጫኑ)።
ቤቱ ግድግዳ ላይ በተሰቀለ የምኒልክ ጎራዴ አጠገብ ተቀምጦ ቴዲ ስለተካሄደበት ይህን መሰሉ ህገወጥ ዘመቻ ይህንን ይላል፤ “ስለ ኢትዮጵያ ታሪክና ቀደምት ነገሥታት አሉታዊ አመለካከት ያላቸው ቡድኖች ሊኖሩ ይችላሉ። አመለካከታቸውን ባከብርም የኔን አመለካከት መውደዳቸውም ወይም አለመውደዳቸው እውነቱን አይለውጠውም።”
በሙስሊምና ክርስቲያን መካከል ሰላምና ፍቅር፣ መግባባት እንዲኖር የሚያዜመው ቴዲ ከህወሓት ሌላ በርካታ ነቃፊና ስም አጥፊዎችም በዘመኑ አላጣም። በአድናቂዎቹ ሴቶች ጡት ላይ ይፈርማል በማለት ስለ እርሱ ሲናገሩ ለነበሩ የሰጠው ምላሽ በኢትዮጵያ በውጭ አድናቆትን እንዳተረፈለት ዴይሊ ሜይል ዘግቧል። እንደ ኢትዮጵያዊ ይህንን ዓይነት ነገር ፈጽሞ ሊያደርገው እንደማይችል ነው ቴዲ የተናገረው። ይህንን በመደገፍ ይመስላል የአፍሮ ኤፍ ኤም ፕሮግራም ኃላፊ የሆነው ኢዮኤል ሰሎሞን “(ቴዲ) የሚሰብከው የሚኖረውን ነው፤ እኛ እንወደዋለን፤ ኢትዮጵያውያን ይወዱታል” በማለት አስተያየቱን ሰጥቷል።
“ኢትዮጵያ” አልበሙ የምረቃ ፕሮግራም የተቋረጠበት ቴዲ አፍሮ፤ ለአዲሱ ዓመት (2010) ያቀደው ኮንሰርትም ተከልክሏል። አሁንም ግን ተስፋ ሳይቆርጥ ለገና ኮንሰርት ለማቅረብ ያቀረበው ጥያቄ እንዲፀድቅለት እየጠበቀ ነው። ይህ ሁሉ ሆኖ በሙያውና በሙዚቃው ስለ ኢትዮጵያ ከመሥራት ምንም እንደማያዳክመው ተናግሯል።
የቴዲ ምኞት እና ተስፋ ግን በዚህ ብቻ የተገታ አይደለም፤ እስከ አስመራ የዘለቀ ነው። እዚያ የሙዚቃ ድግስ ለማቅረብ ተስፋ ያደርጋል። “የሚያስፈልገን የፍቅር፣ የሰላም፣ የይቅርባይነት መንፈስ ነው። ምክንያቱም አሁን ያሉት ችግሮች የታሪክ ቅሬታዎች ያመጧቸው ውጤቶች ናቸው። ልናራግፋቸው፤ ወደኋላ ትተናቸው ልንሄድ ይገባል” ይላል ቴዲ አፍሮ።
ዘገባው ከነፎቶው የተጠናቀረው ከዴይሊሜይል ድረገጽ ነው።
ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ™ ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ™ ንብረት ናቸው። ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (https://www.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን።
ሰዎች!! ቴዲ አፍሮ ስለ ኢትዮጵያዊነት ያትታል፣ ይዘፍናል፣ እኩልነትን አክሎበት ያውቃል?? ቴዲ ስለ ሀገሩ ለመስበክ ብዙ ይቀረዋል። ከመጠምጠም ትምህርት ይቅደም!!
ሙሉጌታ!! አንድ መሆን ከእኩልነት የሚልቅ ይመስለኛል። አንድ መሆን በውስጡ እኩልነትንም ይጨምራል። እንደሚገባኝ የቴዲም ሃሳብ ይኸው ነው፣ አንድ እንሁን። እኩልነት የሌለበት “ትክክለኛ አንድነት“ ሊኖር አይችልም። እኩልነት ከሌለ አንድነት የተባለው ነገር ውሸት ወይም ስም ብቻ ይሆናል። ቴዲ የአባትህ ስም እንደሚገባው ይሰማኛል። አንዳርጌ!(አንድ አድርጌ፣ አንድ የሚያደርግ)። እንግዲህ መሰለኝና ተናገርኩ ጎልጉል Speak your mind ስላለ።