• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ፕሮፍ ተሸኙ!

October 6, 2020 11:14 pm by Editor 3 Comments

የጂኦግራፊ ሊቅ የሰብዓዊ መብት ተሟጋችና ደራሲ መስፍን ወልደ ማርያም (ፕሮፌሰር) (1922-2013)

“አንድ ትውልድ ይወለዳል፣ በጊዜው እንደጊዜው ያድጋል፣ ያልፋል፣ በሌላ ትውልድ ይተካል። አዲሱም ትውልድ የተረከበውን ቅርስ ይዞ ይነሳና በራሱ ጥረት አዳዲስ ሥራዎችን ሠርቶ ይጨምርበትና ያድጋል፣ አዲስ ነገርን ትቶ ያልፋል። የቀደመው ትውልድ ተፈጥሮና ኑሮው ከሚያስገድደው በላይ ለሚቀጥለው ትውልድ መስዋዕት መሆን አይችልም፣ አይጠበቅበትምም። በምፅዋትና በሞግዚት አስተዳደር የሚኖር ትውልድ ለሚቀጥለው ትውልድ የሚያስተላልፈው ዕዳ ብቻ ነው፣ ዕዳን በውርስ ተሸክሞ የሚፈጠር ትውልድ ያለምርኩዝ መንቀሳቀስ አይችልም፣ ምርኩዝ ሊሆኑት የሚችሉት እነዚያው የዕዳው ባለቤቶች ናቸው። ስለዚህም ከዕዳና ከምፅዋት አዙሪት አይወጣም።”

ይህን ጠሊቅ ዕይታ የትውልድ ቅብብሎሽ አንፃራዊ ገጽታና ትችት በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ላይ “ትውልዶች” በሚል ርዕስ መስከረም 7 ቀን 2013 ዓ.ም. ዜና  ዕረፍታቸው ከመሰማቱ ከአሥር አምስት ቀናት በፊት የከተቡት ሊቁ መስፍን ወልደ ማርያም (ፕሮፌሰር) ናቸው።

በኢትዮጵያ ዘርፈ ብዙ ጉዳዮች ላይ ሐሳባቸውን ለማንፀባረቅ ችላ የማይሉ፣ ዕውቀታቸውንና ምልከታቸውን በአደባባይ ለማስተጋባት የሚተጉ ነበሩ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም።  “ነፃ ሐሳብ ለነፃ ሕዝብ” የሚል አስተምህሮ የነበራቸው ያንንም ለመተግበር ዕውንም ለማድረግ ወደ ኋላ ማለት ማፈግፈግን ዞር በል የሚሉ ናቸው ይሏቸዋል። ለሰብዓዊ መብቶች መከበር ከሦስት አሠርታት ወዲህ ኢሰመጉን በመመሥረት ያሳዩት ተላሚነት ይበልታን አስገኝቶላቸዋል።

ከዘውዳዊው ሥርዓት እስከ ወታደራዊው የደርግ መንግሥት፣ ከሕዝባዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊኩ እስከ አሁን ዘመኑ ፌዴራላዊ ሪፐብሊክ መንግሥታት  ድረስ የሽግግር ዘመኑንም ጨምሮ በገሀድ በመሔስ የሚሰማቸውን በመጣጥፍና በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን በመግለጽ ከቀዳሚነት ይጠቀሳሉ። በተለይ ደርግ ወድቆ ኢሕአዴግ መንበረ ሥልጣኑን ሲጨብጥ በሽግግሩ ዘመን በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ከወቅቱ የሽግግር መንግሥቱ ፕሬዚዳንት አቶ መለስ ዜናዊ ጋር ክርክር የገጠሙበት መንገድም (ሌሎች ምሁራን ጨምሮ) በብዙዎች ዘንድ ይታወሳል።

በ1950ዎቹና በ1960ዎቹ በሰሜን ኢትዮጵያ የደረሰውን ድርቅና ረሃብ ተከትሎ የተፈጠረውን ቀውስ ይፋ በማድረግ የሚጠቀሱት በስሚ ስሚ ያገኙትን ሳይሆን በተለያዩ አካባቢዎች በመገኘት ያዩትን የተመለከቱትን በፎቶግራፍ ጭምር በማስደገፍ ከባልደረቦቻቸው ጋር መጣራቸው ይወሳላቸዋል። በርሳቸው አገላለጽ ‹‹ጠኔ›› የሚባለውን ረሃብ አስመልክቶ መፍትሔ ማሳያ መጽሐፍም እስከ ማዘጋጀት መድረሳቸው ገጸ ታሪካቸው ያሳያል።

 ከባህር ማዶ የቅድመና ድኅረ ምረቃ ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ የሥራውን ገበታ የተቀላቀሉት የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ  ዩኒቨርሲቲን ነው። በዘመኑ  ጥቂት ምሁራን ብቻ የሚያደርጉትን ለሚያስተምሩት ትምህርት የመማርያ መጽሐፍ በማዘጋጀት ረገድም ዓይነተኛ ተጠቃሽ ናቸው።

በአካዴሚያ ሕይወታቸው ለፕሮፌሰርነት የበቁበት የጂኦግራፊያ መምህርነታቸው የኢትዮጵያን መልክዓ ምድር በጥልቀት የሚያሳይ መጽሐፍን አበርክተዋል። የትምህርት  ክፍሉንም እስከ መምራት ደርሰዋል።

ፕሮፌሰር መስፍን በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በነበሩበትና ጡረታ ከወጡም በኋላ ጥናታዊ ጽሑፎችንና መጻሕፍትን አሳትመዋል። የኢትዮጵያ ጥናት ዓለም አቀፍ ጉባዔን ጨምሮ በተለያዩ ዓለም አቀፍ መድረኮች ጥናቶቻቸውን አቅርበዋል። የአደባባይ ምሁር ካሰኛቸው አንዱ የተለያዩ ጽሑፎችን በማዘጋጀት በጋዜጦች፣ በመጽሔቶችና በማኅበራዊ ትስስር መድረኮች ያለመታከት ሲያካፍሉ መቆየታቸው ነበር።

በገጣሚነትም የሚታወቁት ፕሮፌሰር መስፍን በመስከረም 1967 ዓ.ም. ያሳተሟት “እንጉርጉሮ” የግጥም መድበል የኅብረተሰቡን እንጉርጉሮ  ያንፀባረቀች ናት።  ከ38 ዓመት በኋላም የአገሬው እንጉርጉሮ  ፈውስ  ባለማግኘቱም የ2005  ዓ.ም. “ዛሬም እንጉርጉሮ” በማለት አሳትመዋል።

ካዘጋጇቸውና የኅትመት ብርሃን ካገኙት መካከል “ኢትዮጵያ ከየት ወዴት፣ አደጋ ያንዣበበበት የአፍሪካ ቀንድ፣ ሥልጣን ባሕልና አገዛዝ፣ ፖሊቲካና ምርጫ፣ የክህደት ቁልቁለት፣ አገቱኒ፣ መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ፣ አድማጭ ያጣ ጩኸት፣ እንዘጭ! እምቦጭ! የኢትዮጵያ ጉዞ፣ አዳፍኔ፣ ፍርሃትና መክሸፍ፣ ዛሬም እንደ ትናንትና” ተጠቃሽ ናቸው።

በዘውዳዊ ሥርዓት የተጀመረው ፖለቲካዊ ትግላቸው ወደ ፓርቲ ሕይወት የተሸጋገረው በ1997 ዓ.ም. በተደረገው አገራዊ ምርጫ ዋዜማ ከትግል አጋሮቻቸው ጋር ባቋቋሙት ቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ ፓርቲ አማካይነት ነው። ምርጫውን ተከትሎ በተፈጠረው ቀውስም ‹‹የሕገ መንግሥቱን ሥርዓት አደጋ ላይ በመጣል›› በሚል ከሌሎች ጓዶቻቸው ጋር እንዲታሰሩ ተፈርዶባቸው በይቅርታ መለቀቃቸው ይታወሳል።

ከአባታቸው አቶ ወልደ ማርያም እንዳለና ከእናታቸው ወ/ሮ ይመኙሻል ዘውዴ ሚያዝያ 15 ቀን 1922 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ከተማ የተወለዱት ፕሮፌሰር መስፍን፣ በልጅነታቸው ዘመን በ1937 ዓ.ም. ለድቁና ያበቃቸውን የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን መሠረታዊ ትምህርት ተከታትለዋል። በተፈሪ መኰንን ትምህርት ቤትም የአንደኛና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ ወደ ህንድ አገር በማቅናት የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ከፑንጃብ ዩኒቨርሲቲ ሁለተኛ ዲግሪያቸውን በአሜሪካ ከሚገኘው ክላርክ ዩኒቨርሲቲ አግኝተዋል። ትምህርታቸውን አጠናቅቀው ከተመለሱ በኋላ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ማገልገላቸው ከመጀመራቸው በፊት በካርታና ጂኦግራፊ ኢንስቲትዩት ውስጥ ሠርተዋል።

ባደረባቸው ሕመም ሳቢያ ሕክምናቸውን ሲከታተሉ የቆዩት ፕሮፌሰር መስፍን ማክሰኞ መስከረም 19 ቀን 2013 ዓ.ም. ለረቡዕ አጥቢያ በ90 ዓመታቸው አርፈዋል። ሥርዓተ ቀብራቸውም ከሰኞ በኋላ እንደሚፈጸም የቀብሩ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ለመገናኛ ብዙኃን መግለጻቸው ታውቋል።

ዜና ዕረፍታቸውን ተከትሎ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) በሐዘን መግለጫቸው፣ “የሐሳብ ልዕልና ምልክት፣ የሰላማዊ ትግል አርአያ፣ ላመኑበት ነገር እስከ መጨረሻቸው ሞጋች፣ ላመኑበት እውነት ብቻ የሚቆሙት ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም በማረፋቸው ጥልቅ ሐዘን ተሰምቶኛል፤” ብለዋል።

ከአርባ ስድስት ዓመታት በፊት በወርኃ መስከረም ካሳተሟት “እንጉርጉሮ” የግጥም መድበል ውስጥ የሞትን ምንነት ከገለጹበት ውስጥ የሚከተለው አንጓ ይገኝበታል።

ሞት ማለት:-
ሞት አለመስጋት ነው የግዴለሽ ዓለም፣
ድንጋይ ተሸክሞ በውኃ ላይ መቆም፣
ጤንነት የለበት፣ አያጠቃው ሕመም፣
ትዝታ የለበት፣ አይታይበት ሕልም፣
ቡቃያው አያሸት፣ ፍሬው አይለመልም።
ዝናብ አይዘንብበት ድርቀት ነው ዘላለም።
ማንም አይጎዳ ማንም አይጠቀም።

የሦስት ልጆች አባት የነበሩት ፕሮፌሰር መስፍን፣ በኅልፈታቸው ዋዜማ በ13ኛዋ ወር ጳጉሜን “መልካም ምኞት ለአዲስ ዓመት” በሚል ርዕስ በፌስቡክ ገጻቸው እንዲህ ተመኝተው ነበር።

“2012 ዓ.ም. ቆሻሻውን አራግፎብናል። ነገር ግን እግዚአብሔር ክረምቱን ከባድ አድርጎታል፣ እግዚአብሔር ክረምቱን ያከበደው በውስጣችንም ሆነ በላያችን የተሸከምነውን ቆሻሻ ለማጠብ እንድንችል ይሆናል። እግዚአብሔር ልባችንን በፍቅር፣ አዕምሮአችንን በዕውቀት ይሙላልን”። (ሪፖርተር)

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሽኝት ፕሮግራም ሲካሄድ

ጉዞ ወደ ቅድስት ሥላሴ
ቅድስት ሥላሴ
ሽኝት
የትውልድ ፈርጦች፤ የኢትዮጵያ አንጸባራቂ ዕንቁዎች – ፕሮፌሰር መስፍን እና ፕሮፌሰር አስራት (ማኅበራዊ ሚዲያ)

(በተለይ ካልተጠቀሰ ፎቶዎቹ በሙሉ የተወሰዱት ከኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ የማኅበራዊ ገጽ ነው)

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Middle Column, News, Politics, Social Tagged With: mesfin, prof mesfin

Reader Interactions

Comments

  1. ታዛቢ says

    October 13, 2020 09:11 pm at 9:11 pm

    ለጎልጉል ምስጋናዬ ልክ የለውም!
    የኝህ ታላቅ ሰው ታሪክ እንዲህ ባጭሩ ቅልብጭ ብሎ: ግና ለትውልድ በሚተላለፍ መልክ በመዘከሩ ኮርቼባችኋለሁ!!

    Reply
  2. Mulugeta Andargie says

    October 18, 2020 07:32 am at 7:32 am

    Mulugeta Andargie

    በፕሮፍ ላይ የሰጠሃቸው ጸያፍ አስተያየትና በግጥም የላከው አስተያየት፤ ሁለቱም ተሰርዘዋል።

    አስተያየት ልኬ አላተማችሁልኝም ብለህ እንደ ሁልጊዜው እንዳታላዝን ነው ይህንን የነገርንህ።

    አርታኢ

    Reply
  3. Mulugeta Andargie says

    November 1, 2020 03:09 am at 3:09 am

    ጎልጉሌች ስለ ዘረኝነት ትዋጋላችሁ? እስቲ ፊታችሁን በመስታወት ተመልከቱት። ሞኝ የለም!! ስትፎክት ትኖራለህ እንጂ፤ ነጻ ህዝብ መሆናችንን ኣረጋግጠናል። እኔ እንደ እናንተ ኣላዝንንም።ህዝባችን ነጻ ነው። ሰርቶ፥ ለፍቶ፥ ጥሮ ግሮ ያድራል። የሃይለስላሴ መንግስት፥ የደርግ መንግስት ያሰቃየው ነበር። ያ ይመለሳል ብላችሁ የምታስቡ ከሆነ ህልም ነው። ቀሺሞች።

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • “አስደንጋጭ”! 1 ሚሊዮን ከሚጠጋ ተፈታኝ ተማሪ ወደ ዩኒቨርሲቲ የሚገባው 30 ሺህ (3.3%) ብቻ ነው  January 27, 2023 09:11 am
  • የማይዘነጋዉ የኢትዮጵያዊያኖች የጀግንነት ተጋድሎ ታሪክ፡- ኮሎኔል ባጫ ሁንዴ (ታጠቅ) January 27, 2023 06:12 am
  • ጎርጎራ – የመጻዒው ዘመን ሙሽራ! የዉበት ፈርጥ! January 17, 2023 04:18 pm
  • ሁለተኛው መስቀል አደባባይ January 17, 2023 04:13 pm
  • በአቡዳቢ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን January 17, 2023 04:08 pm
  • በንፋስ ስልክ ላፍቶ ስምንት የመሬት ሌቦች ተያዙ January 16, 2023 11:36 am
  • ሺሻ ሲያስጨሱ በተገኙ ሆቴሎችና የምሽት ጭፈራ ቤቶች ላይ እርምጃ ተወሰደ January 16, 2023 08:50 am
  • በሐሰተኛ መታወቂያ የደኅንነት አባል ነን ብለው ሲያጭበረብሩ የነበሩ ተያዙ January 13, 2023 02:03 pm
  • ተሽከርካሪ ወንበር ለትግራይ – “ናይ ኣካል ጉዱኣት ተሽከርካሪ ዘለዎ ወንበር” January 12, 2023 07:17 pm
  • የአማራው ኩራት፣ የኢትዮጵያ ዘብ፣ የትህነግን ቅስም ሰባሪ! January 12, 2023 04:00 pm
  • በኢትዮጵያ ላይ የተጣሉ ማዕቀብ እና ሌሎች አስገዳጅ ሕጎች ሙሉ ለሙሉ ተሰረዙ January 12, 2023 01:52 pm
  • የቻይና ዕዳ ስረዛ “Payday Loan Diplomacy” ወይስ ኢትዮጵያን ያዳነ ተግባር? January 12, 2023 11:00 am
  • የአዲስ አበባ አስተዳደር ከቋንቋ ጋር በተያያዘ ውሳኔ አስተላለፈ January 12, 2023 10:46 am
  • “አምባሳደሩ” የቀድሞ ጌቶቻቸውን እንዲያቋቁሙ ተሾሙ January 11, 2023 03:47 pm
  • መከላከያ ሸኔን የሚዋጉ ሚሊሻዎችን አሠልጥኖ አስመረቀ January 10, 2023 05:37 pm
  • በሰባት ተጠርጣሪዎች ላይ ከባድ የሙስና ወንጀል ክስ ተመሰረተ January 10, 2023 03:36 pm
  • የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አቅጣጫ January 6, 2023 03:26 pm
  • “ከዕብሪቱ አስተንፍሰነዋል” – ኢሳያስ January 2, 2023 07:29 pm
  • [ኢትዮጵያን] “አስታክኮ ኤርትራን መውጋት ለሚፈልግ ኃይል አንተባበርም” January 2, 2023 07:11 pm
  • የ፰ ወር ሕጻንና ጨቅላ ወንዶች የሚደፈሩባት ትግራይ December 14, 2022 02:49 pm
  • “ሰውን ለመርዳት ሰው መሆን ብቻ በቂ ነው” የደጎች አውራ የመቄዶኒያው ቢንያም በለጠ December 14, 2022 09:59 am
  • “የሀብት ምዝገባ መረጃው ለሕዝብ ክፍት ይደረግ “ December 13, 2022 10:30 am
  • የኢትዮጵያ ዓለምአቀፋዊ የሌብነት ደረጃ December 13, 2022 09:42 am
  • ለብረት አቅላጮች ለመሸጥ በኤሌክትሪክ የብረት ማማዎች ስርቆት የ100 ሚሊዮን ብር ኪሳራ December 13, 2022 09:26 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2023 · Goolgule