
የሪፖርተርን እና የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የ“በሬ ካራጁ” አዋዋል በአንድ ታሪክ እናብራራው … አንድ አውራ ዶሮ የነበረው አንድ ሰነፍ ገበሬ ነበር፤ ገበሬው ይህንን አውራ ዶሮ ከገዛበት ቀን ጀምሮ ዶሮውን ለመብላት የሚመኝ አንድ ኮሳሳ ቀበሮ በገበሬው ቤት ሁልጊዜ ያንዣብባል፤ በሰፈሩ እየዞረም “ዶሮው ታምሟል፤ ጠዋት ይሞታል” እያለ ቀበሮው ለሰፈረተኛው በሙሉ ያወራል፤ የሚወራበትን ያልሰማው ወይም ጆሮ ዳባ ያለው ሰነፍ ገበሬም ጉዳዩን ከመጠየቅና ከማጣራት ይልቅ “ቀበሮው መዞር ከጀመረ አንድ ቀን ሆነው፤ አንድ ሳምንት ሆነው፤ 15 ቀን ሆነው፤ … መቼም ቢርበው ነው” እያለ ያገኘውን ሥጋ ሲመግበውና የዙረቱን “በዓል” ሲያከብርለት ከሰነበተ በኋላ ቀበሮው በደንብ ሲጠበድል ዶሮውንም ያበላውን ገበሬም ሰለቀጣቸው።
በኢትዮጵያ በነጻ ሚዲያ ስም በነጻነት እየተንቀሳቀሰ የሚገኘው ሪፖርተር ሚዲያ የተመሠረተበትን 30ኛ ዓመት እያከበረ ይገኛል። ለ30 ዓመት በሕይወት ለመኖር መቀለብ የግድ ነውና ለሦስት ዐስርተ ዓመታት ሲቆይ በርካታ ቀላቢዎች አፍርቷል።
ከአበበ ባልቻ ጋር 25ሺህ ብር በነፍስ ወከፍ አዋጥተን በ50ሺህ ብር ሪፖርተርን መሠረትን የሚለው አማረ አረጋዊ በዘመነ ትህነግ ቀላቢዎቹ የራሱ የትህነግ ድርጅቶችና የመንግሥት ማሽነሪው (state machinery) ነበር (አበበ ባልቻ ከአማረ ጋር ሪፖርተርን መመሥረቱ እንደ ክብር ማውራቱ በሌላ ጊዜ የምናየው ይሆናል)። ምክንያቱም ሪፖርተር የተቋቋመው የትህነግን ዓላማ የትህነግ ተቃዋሚ በመምሰል ለማስፈጸም ነው – በሌላ አነጋገር አውሬው ሪፖርተር በኢትዮጵያ ማሊያ ለትህነግ የሚጫወት ነበር፣ አሁንም ነው።
ባለፈው ስለ ሪፖርተር ባቀረብነው ሰፋ ያለ መረጃ ላይ ሪፖርተር በአዲስ አበባ የተቀመጠ የትህነግ ጉዳይ ፈጻሚ መሆኑን መጥቀሳችን ይታወሳል። ከዚህ በላይ በዋነኝነት ለማሳየት የሞከርነው የሪፖርተርን የአጀንዳ ተካይነት ሚና የተለያዩ ማስረጃዎችን በማጣቀስ ነበር።
ሪፖርተር ይህንን ሥራ ለመከወን ደግሞ በደንብ መቀለብ አለበት፤ በመረጃ ብቻ ሳይሆን በፋይናንስም። በሟቹ የደኅንነት ሰው ክንፈ ገብረመድኅን መረጃ ሲቀለብ የነበረው ሪፖርተር ከክንፈ ሞት በኋላ የትህነግ አጀንዳ ተካይነት ሚናው ቀጥሎ ቀላቢ ሳይቸገር ኖሯል። አሁን ላይ ደግሞ በቀዳሚነት ቀላቢዎቹ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ሲሆኑ ባልተለመደ መልኩ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ሌላው ቀላቢ ሆኗል።
በ2014ዓም አጋማሽ አካባቢ የተቋቋው ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ብዙ የተለፋበት ታላቅ ተቋም ነው። ኮሚሽኑ እጅግ ሥር የሰደዱ የኢትዮጵያን ችግሮች በተለይም በዘመነ ትህነግ የተተከሉትን የሠንደቅ ዓላማ፣ የብሔራዊ ሕዝብ መዝሙር፣ የክልል አወቃቀርና አወሳሰን፣ በቋንቋ ላይ የተመሠረተ ፖለቲካ፣ … በተለይ ባለፉት 30 ዓመታት በሀገራችን የፖለቲካ ሥርዓት ውስጥ ትህነግ የተከለውን አፍራሽ አጀንዳ ሕዝብን አወያይቶ ዘላቂ መፍትሔ የሚያመጣ፣ መርዝ የሚያረክስ፣ ሰንኮፍ የሚነቅል ነው። በሌላ አነጋገር የምክክር ኮሚሽኑ አጥፊ አጀንዳዎችን ይነቅላል፤ ጠቃሚዎቹን ይተክላል።
ስለዚህ የኮሚሽኑ መቋቋም በመጀመሪያ የሚጎዳው ፖሊሲዎቹን እንዳይነቀሉ አድርጎ የተከለው ትህነግ እና የርዕዮቱ አራማጆችን ነው። በመሆኑም ትህነግም ሆነ ትህነጋውያን ኮሚሽኑን ፈጽሞ አይወዱትም። ግጭት ባለበት የአማራ ክልል ጨምሮ በሁሉም የኢትዮጵያ ክፍል ኮሚሽኑ አጀንዳ ሲያሰባስብ፤ በትግራይ አጀንዳ እንዳያሰባስብ እስካሁን ድረስ በትጋት እየሠሩ ነው።
የአውሬው ሪፖርተር ባለቤት አማረ አረጋዊም ኮሚሽኑን ፈጽሞ አይፈልገውም። ስለዚህ ምን አደረገ? ልክ እንደ ቀበሮው ገና ኮሚሽኑ እንደተቋቋመ “ዶሮው ታምሟል፤ ነገ ይሞታል” እያለ ማስወራት ጀመረ።
ፌብሩዋሪ 23 ቀን 2022ዓም “መንግሥት ጣልቃ የሚገባ ከሆነ ከኃላፊነታቸው እንደሚለቁ የምክክር ኮሚሽኑ ሰብሳቢ አሳሰቡ” በሚል ርዕስ የፕሮፌሰር መስፍንን የተጨነቀ ወይም ለመልቀቅ ያገረገረ የሚመስል ፎቶ አክሎ ሪፖርተር አንድ ዜና አስነብቦ ነበር። ሌላው በ“ውጪ ሚዲያ” ስም ከሪፖርተር ጋር እየተናበበ የትህነግን አጀንዳ የሚተክለው ቢቢሲም በተመሳሳይ ርዕስ ዜና አውጥቶ ነበር።


ኮሚሽኑ ሥራውን ሲጀምር ሁሉንም ኮሚሽነሮች ያቀፈ የትውውቅ ፕሮግራም ከሕዝብ ተወካዮች ምክርቤት ኃላፊዎች አድርጎ ነበር።
የካቲት 16 ቀን 2014ዓም በተወካዮች ምክርቤት በተካሄደው ፕሮግራም ላይ ዋናው ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ በዋነኛነት የተናገሩት ኃላፊነቱ ከባድ እንደሆነ፣ ግን ደግሞ ለመሥራት ፈቃደኛና ቁርጠኛ መሆናቸውን፣ ያለ መንግሥት ጣልቃ ገብነት በገለልተኝነት እንደሚሠሩና ይህም የመንግሥት አቋም እንደሆነ ቃል እንደተገባላቸው ነበር። ይህ ካልሆነ ግን ሥራቸውን ለመልቀቅ እንደሚገደዱም ተናግረዋል። ይህም ተገማችና ተጠባቂ ነው።
በተወካዮች ምክርቤት በተደረገው ስብሰባ ላይ ያልተገኘው፤ ጋዜጠኛ ያልላከው ወይም ያልተጋበዘው ሪፖርተር (ቢቢሲም እንዲሁ) ከምክር ቤቱ ድረገጽ ላይ ያገኘውን ዜና በራሱ የምኞትና የአጀንዳ ተካይ አቅጣጫ በመሥፈር ገና ኮሚሽኑ ቢሮ፣ ጠረጴዛ፣ ወንበር፣ ወረቀት፣ እስክሪብቶ፣ ላጲስ፣ መቅረጫ፣ … ሳይኖረው “ዶሮው ታምሟል፤ ነገ ጠዋት ይሞታል” በማለት ዘገበለት። “መንግሥት ጣልቃ የሚገባ ከሆነ ከኃላፊነታቸው እንደሚለቁ የምክክር ኮሚሽኑ ሰብሳቢ አሳሰቡ” ነበር የሪፖርተር ምኞታዊ ዜና።
ሪፖርተር “30ኛ ዓመቴን እያከበርሁ (ሠላሳ ዓመት እየዞርሁ) ነውና ስፖንሰር አድርጉኝ” በማለት የፕላቲኒየም፣ የወርቅ፣ የብር ስፖንሰሮችን መልምሎ “ቀልቡኝ” ማለቱን የሰሙ ሀገር አፍራሹን አውሬ ጥሩ አድርገው በሀገር ሃብት እየቀለቡ ነው። ከእነዚህ ቀላቢዎች መካከል የብር ስፖንሰሩ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ነው።
በቀጣይ ሌላኛውን ቀበሮ ቀላቢ ሰነፍ ገበሬ እናቀርባለን።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ



Leave a Reply