
የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጪ ግምባር (ትህነግ)ን ማንነት የማያውቅ አንድም በሟቾች ይሸቅጣል፤ በደማቸው የፖለቲካ ትርፍ ለማግኘት ይጣጣራል፤ ወይም ያወቀ መስሎት ይለፈልፋል፣ ይዘልፋል፣ ይዘፍናል።
ትህነግ ከአፈጣጠሩ ጀምሮ ምህረት የማያውቅ እንደሆነ “ነጻ አወጣሃለው” ባለው ሕዝብ ላይ ለዓመታት የፈጸመውን መመልከት በቂ ነበር። ስለምንረሳና እንደምረሳ ስለሚያውቅ ገድሎ ሙሾ አውራጅ ሆኖ ይመጣል። ጨፍጭፎን ስለ ሰላም ልደራደር ይላል።
በወለጋ የተከሰተውንና መቼም የማይረሳውን አረመኔያዊ ጭፍጨፋ በትህነግ ልክ ያለ አካል እና እርሱ አቡክቶ ጋግሮ የሠራው ኦነህ ሸኔ ካልሆነ ማንም ሊያደርገው እንደማይችል መገመት የማይችል ገና የኢትዮጵያ ፖለቲካ ያልገባው የፖለቲካ ሕጻን ነውና አርፎ ተቀምጦ ይማር። ሌሎች ግን አሉ አዛኝ መስለው አጀንዳ የሚፈጽሙ። ባደባባይ ከሰቆቃው ሰለባ በላይ ያለቅሳሉ፤ ከዚያ መልስ “አባላናቸው” እያሉ ከጣሪያ በላይ ይስቁብናል፣ በጅልነታችን ይሳለቁብናል።
እጅግ ልብ የሚሰብረውን የአቶ መሐመድን ሰቆቃ አል-ዐይን አስነብቦናል፤ ለታሪክ እናሰቀምጠው።
አቶ መሀመድ የሱፍ ሙሄ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን ጊምቢ ወረዳ ነዋሪ ሲሆኑ ዕድሜያቸውን በትክክል እንደማያውቁት ይናገራሉ፡፡
የቶሌ ቀበሌ ነዋሪው አቶ መሐመድ 22 ቤተሰብ በአንድ ቀን እንደተገደለባቸው ለአል ዐይን አማርኛ ተናግረዋል፡፡ ከተገደሉባቸው ቤተሰቦቻቸው መካከል ከወለደች አራት ቀን የሆናት እመጫት ልጃቸው አንዷ መሆኗን ገልጸዋል፡፡

አቶ መሐመድ የሱፍ የአራት ቀን እመጫት ልጃቸው ከእነ ልጇ በጥይት መገደሏን ያነሱ ሲሆን፤ ገዳዮቹ ህጻኗን እንኳን አለመተዋቸው እጅግ እንዳሳዘናቸው ገልጸዋል፡፡
አቶ መሐመድ ልጆቻቸው ከነልጅ ልጆቻቸው መገደላቸውን የገለጹ ሲሆን የመጀመሪያና ሶስተኛ ልጆቻቸው እስከ ልጅ ልጆቻቸው አምስት፤ አምስት ሆነው መገደላቸውን ተናግረዋል፡፡
ሁለተኛዋ ልጃቸው ከሶስት ልጆቿ ጋር፤ እመጫቷ ልጃቸው ከሁለት ልጆቿ ጋር፤ ሌላኛዋ ልጃቸው ከአንድ ልጇ ጋር እንደተገደሉባቸው አቶ መሐመድ ለአል ዐይን አማርኛ በስልክ ተናግረዋል፡፡ በቅርቡ የተዳረችው የአቶ መሐመድ ልጅ እንዲሁም አንድ ወንድ ልጅም እንደተገደሉባቸው ነው የገለጹት፡፡
አቶ መሐመድ በአጠቃላይ ስድስት ልጆቻቸው እና 16 የልጅ ልጆቻቸው መገደላቸውን የገለጹ ሲሆን የቀበሯቸውም እራሳቸው እንደሆኑ ገልጸዋል፡፡ አሁን ላይ አዛውንቱ እናታቸውም አባታቸውም የተገደሉባቸውን ሰባት ልጆች ይዘው እዛው ቶሌ ቀበሌ መቀመጣቸውንና መሸሽ አለመቻላቸውን ገልጸዋል፡፡
አቶ መሐመድ በታጣቂዎች እንደተገደሉባቸው የጠቀሷቸውን ሁሉንም እራሳቸው እንደቀበሩ ገልጸዋል፡፡ ሃዘንተኛው አዛውንት የራሳቸውን ቤተሰቦችን ጨምሮ በአጠቃላይ 60 ሰዎችን መቅበራቸውን ይናገራሉ፡፡
“የእኔን ልጆችና የልጅ ልጆች የቀበርኩት እኔ ነኝ፤ በእኔ እጅ ነው የተቀበሩት ማንም አልቀበረልኝም፤ እኔ እራሴ ነኝ የቀበርኳቸው” ሲሉም ይናገራሉ አቶ መሐመድ፡፡ ከሟቾች ባለፈም የቆሰሉ ስድስት ልጆች እንዳሏቸው ገልጸዋል፡፡ አንደኛዋ ልጃቸው አዲስ አበባ ጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል እንደሄደች ገልጸዋል፡፡ አዲስ አበባ የሄደችው ልጃቸውእግሯ ይቆረጥ አይቆረጥ እየተባለ እንደሆነ ያነሱት አዛውንቱ የሟቾችን ስም ዝርዝር መናገር እንደሚችሉም ነው የገለጹት፡፡
የአቶ መሐመድ የሱፍ ሙሄ 22 የቤተሰብ አባላትን ካሳጣቸው ግድያ የተረፉት በቆሎ ማሳ ውስጥ ገብተው እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ እርሳቸው በቆሎ ማሳ ውስጥ ገብተው የተደበቁት ገዳዮቹ ሴት እና ልጅ “አይገድሉም” በሚል ግምት እንደሆነ ለአል ዐይን አማርኛ ገልጸዋል፡፡
የአቶ መሐመድ የሱፍ ሙሄ ጓደኛዬ መሐመድ አሊ በበኩላቸው የልጃቸው ሚስት ከነልጇ እንደተገደለች ያነሱ ሲሆን ጓደኛቸው አቶ መሐመድ የሱፍ ግን 22 ቤተሰቦቻቸውን ማጣታቸውን ለአል ዐይን አማርኛ ተናግረዋል፡፡
ጥቃት አድራሾቹን ያውቋቸው እንደሆነ የጠየቅናቸው አቶ መሐመድ ከግድያው በፊት ወደ ደምቢዶሎ በቶሌ ቀበሌ ማለፋቸውንና ምግብም ጠይቀው እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ጥቃቱ ሲፈጸም ወንዶች በብዛት ወደ ስራ ሄደው እንደነበርአቶ መሀመድ ገልጸዋል፡፡

አሁን ላይ እናታቸውና አባታቸው የተገደሉባቸውን ሰባትት ፤ አባታቸው የተገደለባቸው አምስት በድምሩ 12 የልጅ ልጆች ይዘው ግራ በመጋባት መቀመጣቸውን የገለጹት አቶ መሐመድ የፌዴራልም የክልል ባለስልጣናት መጥተው እንዳልጠየቋቸው ተናግረዋል፡፡
በምዕራብ ወለጋ ዞን ቶሌ ቀበሌ በተፈጸመ ጭፍጨፋ የሟቾች ቁጥር 2 ሺ እንደሚደርስ አቶ መሐመድ ገልጸዋል፡፡
በምዕራብ ወለጋው ግድያ ላይ አስተያየት እንዲሰጡን ለኦሮሚያ ክልል የመንግስት ኮሙኒኬሽን ቢሮ ተደጋጋሚ የስልክ ሙከራ ብናደርግም ማግኘት ባለመቻላችን ሃሳባቸውን ማካተት አልቻልንም፡፡
የፈዴራል መንግስት ግድያ በተደረገበት አካባቢ የሕግ ማስከበር ስራ እየሰራ መሆኑን የገለጸ ሲሆን የአማራ እና ኦሮሚያ ክልል ርዕሳነ መስተዳድሮች “አሸባሪዎችን ለማጥፋት በጋራ እንሠራለን” ብለዋል፡፡
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply