50 ሚሊዮን ሕዝብ የሚኖርበት የአማራ ክልል ዓመታዊ በጀት ሰማኒያ ቢሊዮን ነው
በትግራይ ክልል ለአምስት ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ሕዝብ ሰብዓዊ ድጋፍ እየተሰጠ መሆኑን የኢትዮጵያ አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አስታወቀ። እስካሁን ወደ ትግራይ የሰብዓዊ ዕርዳታ አቅርቦት ይዘው ከሄዱ አንድ ሺህ 626 ከባድ ተሽከርካሪዎች የተመለሱት ተሽከርካሪዎች 596 ብቻ እንደሆኑ አመልክተዋል። ክልሉን የሚያስተዳድረው ትህነግ በበኩሉ የሚገባው እርዳታ ከሚፈለገው አንጻር በቂ እንዳልሆነ ገልጿል። ዕርዳታ ጭነው የሚገቡትን ከባድ ተሽከረካሪዎች ለምን እንደሚያግታቸው ምክንያት አላቀረበም።
የኢትዮጵያ አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ደበበ ዘውዴን ጠቅሶ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እንዳስታወቀው፤ ምግብ፣ ምግብ ነክ ያልሆኑና መድኃኒት እንዲሁም የትራንስፖርትና የጥሬ ገንዘብ ዝውውርን ጨምሮ ለአምስት ነጥብ ሁለት ሚሊዮን የትግራይ ሕዝብ ሰብዓዊ ድጋፍ እየተሰጠ መሆኑንን ገልጸዋል።
በትግራይ ክልል ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ወገኖች በተለያዩ ድርጅቶች አማካኝነት እንዲደርሳቸው በማድረግ በኩል ሥራው የተሠራና ተፈቅዶ እንዲሄድ እየተደረገ ያለው በኢትዮጵያ መንግሥት እንደሆነ አቶ ደበበ ገልጸዋል። በዚህም በአሁን ወቅት በክልሉ ድጋፍ ለሚሹ አምስት ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ሕዝብ ሰብዓዊ ድጋፍ እየተሰጠ ይገኛል ብለዋል።
ሰብዓዊ ድጋፉ በርካታ ምግብና ምግብ ነክ ያልሆኑ ድጋፎችን ያካተተ እንደሆነ፤ በዚህም በርካታ የዓለም አቀፍ ሰብዓዊ ድጋፍ ላይ የተሰለፉ አጋር አካላት ምግብን ጨምሮ መድኃኒትና ሌሎች ድጋፎችን ለክልሉ ዜጎች በመስጠት ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል።
አቶ ደበበ እንዳሉት፤ እስከ ግንቦት 1 ቀን 2014 ዓ.ም ድረስ በጥሬ ገንዘብ ለአስተዳደርና ለፕሮግራም ማስፈጸሚያ የሚሆን አንድ ነጥብ 76 ቢሊዮን ብር ወደ ክልሉ እንዲላክ ተደርጓል። ይሄንንም የሚያስፈጽሙት በአካባቢው የሚንቀሳቀሱ አጋር ድርጅቶች ናቸው።
202 ሺህ 79 ኪሎ ግራም የተለያዩ መድኃኒቶች በተለያዩ አጋር ድርጅቶች ሰብዓዊ ድጋፍ በአየር ትራንስፖርት ወደ ክልሉ መጓጓዙንም አቶ ደበበ ገልጸዋል።
ከዚህም ባሻገር በተለያዩ ድርጅቶች የሰብዓዊ ድጋፍ አቅርቦት 406ሺህ 403 ኪሎ ግራም የተመጣጠነ ምግብ እና 91ሺህ 558 ኪሎ ግራም ምግብ ነክ ያልሆኑ የተለያዩ ቁሳቁሶች በአየር ትራንስፖርት እንደተጓጓዘ ተናግረዋል።
እንደ አቶ ደበበ ገለጻ፤ በሚያዚያ ወር 2014 ዓ.ም 401 ሺህ 29 ሊትር ነዳጅም ተጓጉዟል። እስካሁን ይህንን በመጓጓዝ ደረጃ በየብስ ላይ መቀሌ የደረሱ ከባድ ተሽከርካሪዎች አንድ ሺህ 626 ናቸው። ከዚህ ውስጥ የተመለሱት ተሽከርካሪዎች 596 ብቻ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።
አቶ ደበበ፤ እስካሁን ለሰብዓዊ አገልግሎት 221 የአየር በረራ መከናወኑን ጠቅሰው፤ ሌሎች ክልሎች እየተላከ ካለው በበለጠ 83 ድርጅቶች በትግራይ ሰብዓዊ ዕርዳታ አቅርቦት እየተረባረቡ እንደሚገኙ ነው የገለጹት።
ከሐምሌ 2013 ጀምሮ 50 ሺህ 921 ሜትሪክ ቶን ምግብ፤ እንደ ውሃ፣ መጠለያ፣ ቁሳቁስ፣ ንጽህና መጠበቂያ የመሳሰሉ ዘጠኝ ሺህ 563 ሜትሪክ ቶን ተጨማሪ ቁሳቁሶች በተለያዩ አጋር ድርጅቶች ሰብዓዊ ድጋፍ አቅርቦት አማካኝነት በየብስ ትራንስፖርት ለክልሉ ዜጎች መጓጓዙን አስታውቀዋል።
ስለ ኢትዮጵያ ሕዝብ የመናገርና አጠቃላይ መረጃ መስጠት የሚቻለው በኢትዮጵያ መንግሥት ብቻ ነው። በተለይ በሚዲያዎች በኩል ከግለሰብ ጀምሮ የሚሰሙ ነገሮችን ተመርኩዞ መናገር አስቸጋሪ ነገር ነው ሲሉም አቶ ደበበ ተናግረዋል።
ወደ ትግራይ ክልል እየገባ ያለው የዕርዳታ አቅርቦት ከሚያስፈልገው አንጻር እጅግ አነስተኛ መሆኑን እና በዚህም ምክንያት ሞትና ረሃብ እየተስፋፋ እንደሚገኝ የትግራይ ክልል የግብርና እና ገጠር ልማት ቢሮ ኃላፊ መሆናቸውን የገለጹት ዶ/ር አትንኩት መዝገቡ፣ በቅርቡ ለቪኦኤ ተናግረዋል፡፡
ወደ ክልሉ ለሚደረገው የዕርዳታ አቅርቦት ማነስ የትግራይ ክልል አመራሮች እና አንዳንድ የረድኤት ድርጅቶች መንግሥትን ተጠያቂ አድርገዋል። ሃላፊው መንግስት በቁጥር፣ በቀን፣ በመለክያና በስም ለይቶ አንድ በአንድ ወደ ትግራይ የገባውን እርዳታ፣ እንዲሁም 76 ቢልዮን ብር አስመልክቶ ቪኦኤ ቃል በቃል ጥያቄ አላቀረበም። የቪኦኤ የትግራይ ዘጋቢ በደፈናው ሃላፊው መንግስትን እንደወነጀሉ ነው ያስታወቀው። መንግስት ውንጀላውን እንደይቀበለውም አመልክቷል።
76 ቢሊዮን ብርና እርዳታ የሚላክለት የትግራይ ክልል አስተዳዳሪ ትህነግ በስሌት ደረጃ በአገሪቱ ካሉ ክልሎች በላይ ሃብት እየተላከለት መሆኑንን መረጃው ያሳያል። እስከ ግንቦት አንድ ቀን 2014 ድረስ ለማስፈጸሚያ ወደ ትግራይ የተላከው 76 ቢልዮን ብር ከአማራ ክልል ዓመታዊ በጀት ጋር ሲነጻጸር በአራት ቢሊዮን ብቻ ነው የሚያንሰው። 50 ሚሊዮን የሚጠጋ ህዝብ ያለው አማራ ክልል በጀቱ ሰማኒያ ቢሊዮን መሆኑ ይታወቃል። በጀቱ ተጨማሪውን ሳያካትት ሲሆን ለማሳያነት ለመጠቀም እንጂ ሌላ ዓላማ የለውም። (ኢትዮ 12)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply