
የፕሬዚዳንት ባይደን የቅርብ ወዳጅ የሆኑት ሴናተር ክሪስቶፈር ኩንስ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድን ለማነጋግር አዲስ አበባ መጥተው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንንን አነጋግረዋል።
የኋይት ሐውስ የፕሬዚዳንቱ የብሔራዊ ጸጥታ አማካሪ የሆኑት ጄክ ሱለቫን ባወጡት አጭር መግለጫ እንዳሰፈሩት በትግራይ አለ በሚባለው የሰብዓዊ መብት ገረጣና ሰብዓዊ ቀውስ ባይደን ያላቸውን ትልቅ ጭንቀት ሴናተር ኩንስ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ እንደሚያቀርቡ ነበር የጠቆሙት። በተጨማሪም ሁኔታው የአፍሪካ ቀንድን አለመረጋጋት ውስጥ ሊከተው የሚችል በመሆኑ ሴናተሩ ከአፍሪካ ኅብረት ጋር እንደሚመክሩበት አማካሪ በመግለጫቸው አመልክተው እንደነበር ይታወሳል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ በተገኙበት አቶ ደመቀ ተቀብለው አስፈላጊው ማብራሪያ እንደተሰጣቸው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሲያስታውቅ ባይደን እንደፈለጉትና በኋይት ሃውስ መግለጫ መሰረት ሴናተሩ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን ስለማግኘታቸው የተባለ ነገር የለም።

አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ውይይቱን አስመልክቶ መግለጫ ሲሰጡ የችግሩ መነሻና መድረሻ አስመልክቶ ያለውን ውዥንብር በሚያጠራመልኩ አቶ ደመቀ ለመልክተኛው እንዳስረዱ አመልክተዋል። አያይዘውም ኢትዮጵያ ደጋግማ እንዳስታወቀችው ሚሊሻን የውጭ ሃይል አድርጎ መመልከት አግባብ እንዳልሆነና በአንድ አገር የውስጥ ጉዳይ መግባት እንደሆነ አቶ ደመቀ በቂ ግንዛቤ እንዳስያዙዋቸው አመልክተዋል።
ኢትዮ 12 የተሰኘ ድረገጽ መረጃ አቀባዮቹን ጠቅሶ ሴናተሩ ትህነግ የፈጸመውን ዘግናኝ የምስል መረጃ፣ የራሱን ሰዎች ሲሞቱ ማንነታቸው እንዳይታወቅ አንገታቸውን እንደሚቆርጥ፣ አብዛኛው መቃብሮች የተደመሰሰበትን ሃይል በጅምላ የቀበረበት እንደሆነ የሚያሳይ፣ ሌሎችም ለሕዝብ ይፋ ያልሆኑ መረጃዎችና ማስረጃዎች ለሴናተሩ እንደሚቀርብላቸው አስቀድሞ ዘግቦ ነበር።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ለሴናተሩ ማብራሪያ ሲሰጡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ወንጪ የገበታ ለአገር ፕሮጀክትን እያስጀመሩ፣ በጊንጪ የኤለኤክትሪክ ማሰራጫ ጣቢያ እያስመረቁ ነበር።



ጆ ባይደን የትግራይን ቀውስ አስመልክቶ በቀጥታ ጉዳዩ ከሚመለከታት ኢትዮጵያ መረጃ ማግኘት ሲችሉ ከኬንያ መሪ ጋር በትግራይ ጉዳይ መወያየታቸው፣ ለአንድ ራሷ አሸባሪ ብላ ፈርጃ ላስቀመጠችው የትህነግ ሽፍታ ቡድን በሚያደላ መልኩ ኢትዮጵያ ተገዳ ለህልውናዋ ስትል ያካሄደችውን ዘመቻ ፍትሃዊነት ሌላ መልክ ለማስያዝ መሞከሩ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን ቅር አሰኝቷል። አካሄዱም አግባብ ባለመሆኑ ሴናትሩን እንዳላገኟቸው ግምታቸውን የሰጡ በርካቶች ናቸው።
ጆ ባይደን የላኳዋቸው ሴናተር በበኩላቸው ኢትዮጵያ ስትራቴጂዊ አጋር መሆኗን፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚከሰቱ ማናቸውም ጉዳዮች አሜሪካን እንደሚያሳስባትና ሁልጊዜም ቢሆን አብራ ለመስራት ቁርጠኛ መሆናቸውን እንዳስታወቁ የመንግስት መገናኛዎች ተናግረዋል። ከመጋረጃው ጀርባ ምን እንደተባባሉ የተጠቆመ ነገር የለም።
የሴናተሩ ጉብኝት ዋና ዓላማ የህወሃትን ርዝራዥ እየመሩ ነበሩ በሚባሉትና በቅርቡ መሞታቸው እየተነገረ ያለውን ጌታቸው አሰፋ እና ጻድቃን ወልደ ትንሳኤ መሞት ለማረጋገጥ ሊሆን ይችላል የሚል ግምታዊ አስተያየት ከሰውየው መምጣት ጋር አብሮ ተሰምቷል።
ለምዕራብ አገራት የቀድሞ ጦር ኃላፊዎች የሚመሩት ብረት ያነገበ ትግል ከምንም በላይ የሚያሳስባቸው ነው። ለአፍሪካ ቀንድ አለመረጋጋትም ከፍተኛ አሉታዊ ተጽዕኖ እንደሚያመጣም እሙን ነው። ከዚህም ሲያልፍ ለአሸባሪነት በር ከመክፈት በተጨማሪ ለመካከለኛው ምስራቅ ችግሩ የሚተርፍ ይሆናል። ህወሃትም ይህንኑ ለማሳየት ይመስላል አሉኝ ያለውን ኮሎኔሎችና ጄኔራሎች ወደ ተከዜ በረሃ እንዲገቡ ያደረገው። ህወሃት ከሥልጣን ቢወገድ የአፍሪካ ቀንድ ለቀውስ ይዳረጋል በሚለው ትርክት የምዕራቡን ዓለም እጅ ማስጠምዘዝ ይቻላል በማለት ህወሃቶች ሲያምኑበት የኖሩበት የማጭበርበሪያ ሥልት ነበር።
የሤራ፣ የግፍ፣ የተንኮል ማምረቻ የነበረው መለስ ዜናዊ ወደማይመለስበት ከተሸኘ በኋላ ህወሃት አቅጣጫውን እንደሳተ ባቡር በፍጥነት ወደ ሞቱ በረረ። በመጨረሻም በሕዝብ ትግል ከሥልጣን ከተወገደ በኋላ መቀሌ መሽጎ ምሥራቅ አፍሪካን ማናወጥ የሚችል ኃይል እንደሆነ በመደስኮር “ባሕላዊ ጨዋታችን ነው” በማለት ስለሚመጻደቅበት ጦርነት ሲያቅራራ ለሁለት ዓመት ተኩል ያህል ቆየ።
ራሱ ህወሃት በሰሜን ዕዝ የመከላከያ ሠራዊት ላይ “መብረቃዊ ጥቃት” ማድረሱን በራሱ ሚዲያ ለዓለም በመለፈፍ የመከላከያ ሠራዊት አባላትን በማረድ በቅጡ እንዳይቀበሩ ግፍ ፈጸመባቸው። ይህንን ተከትሎ ከመከላከያ የተከፈተበት ዘመቻ በሁለት ሳምንት መቀሌን ለቅቆ እንዲወጣ አደረገው። በወቅቱም የመጨረሻውን ዘመቻ ለማከናወን ወደ ተምቤንና ተከዜ ሲፈረጥጥ በአምስት ቡድን በመክፈል ከተለያየ አቅጣጫ የደፈጣ ውጊያ ለማድረግና ለምዕራቡ ዓለም ኃይሉን ለማሳየት ነበር።
የስዩም መስፍን፣ የአባይ ጸሃዬና የሌሎቹ መደምሰስ፤ የነስብሃት ከጉድጓድና ድጋያማ ተራራ በቃሬዛ ተመዝዞ ወጥቶ ለውርደትና ለእስር መዳረግ ህወሃትን ማገገም እንደማይችል ሆኖ ለሁለት ወገቡ የተቀነጠሰበት መራራ ሽንፈት ነበር። ሆኖም እንደ አሜባ ለአምስት ከተከፈለው ቡድን ቀሪው ሁለት ቡድን የመልሶ ማጥቃት ዘመቻ ሲከፍት ከውጪ ደግሞ “በሽተኛ ነኝ” ብሎ ካገር የወጣው ብርሃነ ገብረክርስቶስ የሚመራው ቡድን በዓለምአቀፉ ማኅበረሰብ ላይ በሚዲያ የሃሰት ፕሮፓጋንዳ መርጨቱን ጀመረ። በጎንዮሽ በዓለምአቀፉ ማኅበረሰብ ላይ በሰብዓዊ ዕርዳታ ስም የፖለቲካ ጫና ማሳደሩን ተያያዘው።







የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በስግብግቡ ጁንታ የተሰነዘረበትን የዲፕሎማሲ ዘመቻ በብቃት ለመመከት አፍቃሪ ህወሃት የሆኑትንና በብቃት ሳይሆን በኮታ አምባሳደር የሆኑትን መጠቀም ባለመቻሉ ኢትዮጵያ ብዙ ዋጋ ከፈለች። ከሥልጣን ስወገድ እንዲረዱኝ ብሎ “ከመርህ ውጪ” አስቀድሞ ያዘጋጃቸውን የሚዲያና የዓለምአቀፍ መስተጋብሮችን በገንዘብ በመደለል ጁንታው በኢትዮጵያ ላይ ጫና ቢያሳድርም አገር ወዳድ ኢትዮያውያን በራሳቸው አነሳሽነት የምዕራቡን ዓለም ከተሞች በተቃውሞ ትዕይንተ ሕዝብ አጥለቀለቁት። በኢትዮጵያ ላይ ሲደለቅ የነበረው ከበሮና ሲረጭ የነበረው ፈንዲሻ በተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክርቤት አዳራሽ ለቡና ቁርስ ሳይበቃ የቁሻሻ ቅርጫት ሲሳይ ሆነ።
በአገር ውስጥ የኢኮኖሚ አሻጥር፤ ከምዕራቡ ዓለም የዲፕሎማሲና የሚዲያ ዘመቻ እንዲሁም ከምስራቅ አፍሪካ በአባይ ግድብ ሰበብ ሌላ ቀውስ ውስጥ ገብታ በተለያየ አቅጣጫ ስትንገላታ የነበረችውን ኢትዮጵያን ለማትረፍ መንግሥት በጁንታው ርዝራዦች ላይ ሁለተኛውን ዘመቻ ከፈተ። የዚህ ዘመቻ በዋንኛነት ትኩረት ያደረገው የህወሃትን የመደራደር ዓቅም ማምከን የሚል ነበር።
በመሆኑም በቆላ ተምቤን በነበረውና በህወሃት ኮሎኔሎችና ጄኔራሎች ይመራ በነበረው ቡድን ላይ መከላከያ በምድርና በአየር ከባድ ጥቃት ሰነዘረ። በዚህም ምክንያት የጁንታው ኃይል ከዚያ በመሸሽ ሙሉ በሙሉ ተጠራርጎ በራያና ዲላ በሚባሉ ወረዳዎች መሸገ። እዚያም የመከላከያ ሠራዊት ዘመናዊና በስልት የተደረገ ጥቃት ቀጥሎ ጻድቃን ገብረትንሳኤ የሚመራውና ደብረጽዮንም አለበት በሚባለው ቡድን ላይ የመጨረሻውን ጥቃት ሰነዘረ።
ከአምስት ቀን በላይ በወሰደው ዘመቻ በሽሽት ላይ እያለ ለሁለት ተከፍሎ በተለያየ ቦታ ካለውና በፃድቃን ገብረትንሣኤ ከሚመራው የጁንታው ቡድን በርካታ ጄኔራሎች፣ ኮሎኔሎችና ሌሎች ባለማዕረጎች ተደመሰሱ። በአንዳንዶች ግምት ጻድቃንም ከሞቱት ጄኔራሎች አንዱ ነው ተብሎ ይታመናል።
ኢሣት የመከላከያ ምንጮቹን ጠቅሶ እንደዘገበው 16 አንገት የሌላቸውና መለየት ያልተቻለ የህወሓት ባለስልጣንና የጦር መሪዎች መገኘቱ ሲረጋገጥ 26 በስም የሚታወቁ ኮሎኔሎችና 6 ጄኔራሎች ሙሉ በሙሉ መደምሰሳቸው ታውቋል።
የህወሓት ጁንታ ባለስልጣናትና የጦር መሪዎች ሲያዋጓቸው የነበሩ ቁጥራቸው 2700 የህወሓት ልዩ ኃይልና ሚሊሻ በአየር ድብደባ ሙሉ በሙሉ ሲደመሰሱ 1,500 የሚሆኑት እጅግ በጣም ተንገላተው ግማሹ በረሀብ መራመድ አቅቷቸው በየመንገዱ እየተኙ እጃቸውን ለመከላክያ ኃይል ሰጥተዋል።
ኢሣት በዚሁ ዘገባው እንደገለጸው ጁንታው በቁጥር 5,000 ሺህ የሚሆኑ ልዩ ኃይልና ሚሊሻን አደራጅቶ በተከዜ በኩል ለመሸሽና ሱዳን አለ ከተባለው 1,500 የማይ ካድራው (ሳምሪ) የተባለው ነፍሰ ገዳይ የህወሓት ወጣቶች ጋር ሊገናኝ የነበረው ጥረት ሙሉ በሙሉ መክሸፉ ታውቋል።
አሁን ባለው መረጃ መሠረት ቀሪው ከ500 የማይበልጥ የጁንታው ታጣቂ በሽሽት ላይ የሚገኝ ሲሆን ይህ በፍርጠጣ ላይ የሚገኝ ርዝራዥ ቡድን በሰላም እጅ እንዲሰጥ አንድ ሳምንት ጊዜ ተሰጥቶታል። ይህንን የሳምንት ጊዜ ይፋ ያደረገው የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት መግለጫ እንደተናገረው ቡድኑ በሰላም እጅ የማይሰጥ ከሆነ ባለበት ይደመሰሳል። የት እንዳለ ደግሞ ከበቂ በላይ መረጃ እንዳለ ታውቋል።
ሴናተር ኩንስም ይህንኑ ተመልክተውና ህወሃት ከእንግዲህ ወዲህ ሥጋት እንደማይሆን ተረድተው፤ በማስረጃ ተረጋግጦላቸው የሚሄዱት ሁኔታ አስቀድሞ የተጠናቀቀ ነው። ከሁሉ በላይ ደግሞ ህወሃት እንኳስ የምሥራቅ አፍሪካ የተምቤን አካባቢ ሥጋት እንደማይሆን ወደ አሜሪካ ሲመለሱ ከፕሬዚዳንቱ ጀምሮ እስከነ ሱዛን ራይስና ወደታችም ለነብርሃን ክርስቶስ የሚያበሥሩት “ዜና” ይኖራቸዋል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ የትጥቅ ትግል ከውጪ በሪሞት መቆጣጠሪያ ጦርነት መምራት እንደማይቻል ምዕራባውያን ጠንቅቀው የሚያውቁት ነው። በእነዚህ ምክንያቶች ድምር ውጤት አኳያ ሲታይ ነው ጉብኝታቸው “ለቅሶ ከመድረስ” ያለፈ እንደማይሆን የተነገረው።

ጉዳዩ ያለቀለት መሆኑን የተገነዘቡት እነ ብርሃነ ገብረክርስቶስም አስቀድመው የነጌታቸው አሰፋን መሞት በመረዳታቸው ሰሞኑን የዕርቅ ዜማ መጫወት ጀምረዋል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ ዕርቅ ካልተደረገ ህወሃት አሁንም የምሥራቅ አፍሪካ ሥጋት ሊሆን ይችላል እያስባሉ በነጭ ወያኔ የሚዲያ ወኪሎቻቸው አቅጣጫ የማስቀየሪያ ዘመቻ ተያይዘውታል። ወደ አዲስ አበባ የመጣው የሴናተር ኩንስ ቡድን ለነዚህም ሆነ ለሌሎቹ ዕርማቸውን የሚያወጡበትን መርዶ ያረዷቸዋል የሚል አስተያየትም እየተሰጠ ይገኛል። ይልቁንም እነ ብርሃነ ገብረክርስቶስ እና ሌሎች ከአሜሪካ ሆነው ሁከትና ብጥብጥ የሚነዙ በወንጀለኝነት ለኢትዮጵያ ተላለፈው የሚሰጡበት ሁኔታን መጀመር ከውጪ የሚነዛውን ለማስቆምና ሁኔታውን ለማረጋጋት አሜሪካንን ሊጠቅማት ይችላል የሚል ሃሳብ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አካባቢ ለሴናተሩ እንደሚሠነዘርላቸው ይጠበቃል።
ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ®ንብረት ናቸው። ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (https://www.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን።
Nice info.