
በኢትዮጵያ እና በኢትዮጵያውያን ላይ የተነሳው የሽብር ቡድን በሕዝብ ላይ አያሌ በደሎችን አድርሷል። ከእኩይ ቡድን አቅራቢያ የሚገኙ የአማራና የአፋር ክልል ነዋሪዎች ደግሞ የሽብር ቡድኑ ግፍና ወረራ ገፈት ቀማሾች ናቸው። ለሦስተኛ ጊዜ ጦርነት ያነሳው የትህነግ የሽብር ቡድን የትግራይ ተወላጆችን ከሕፃናት እስከ አዛውንት ድረስ እየመለመለ ለጦርነት እየላካቸው ነው።
የሽብር ቡድኑ በአማራና አፋር ክልል በወረራ በያዛቸው አካባቢዎች ንፁሐንን በጅምላ ረሽኗል፣ ሃብትና ንብፈታቸውን ዘረፏል አውድሟል። የሽብር ቡድኑ የሚልካቸው ታጣቂዎች ሀገሩን እየተከላከለ በሚገኘው ጥምር ጦር እየተመቱ ብዙዎች ይረግፋሉ። እድል የቀናቸው እጃቸውን ሰጥተው ሕይወታቸውን ያተርፋሉ።
የሽብር ቡድኑ ታጣቂዎች በወልቃት ጠገዴ ሰቲት ሑመራ ዞን ለሚገኘው ጀግናው የሀገር መከላከያ በርካቶች እጃቸውን እየሰጡ ነው። እጃቸውን ከሰጡት መካከከል የሽሬው ተወላጅ አብርሃም በሪሁ ይገኝበታል። የትህነግን የሽብር ቡድን ከመቀላቀሉ አስቀድሞ የፌዴራል ፖሊስ አባል የነበረው አብርሃም የሰሜን ዕዝ በተካደ ጊዜ በትግራይ ልዩ ኃይል በቁጥጥር ሥር ዋልኩ ይላል። ከዚያ በኋላ የሽብር ቡድኑን እንዲቀላቀል ይጠይቁታል። እርሱም እምቢ እንዳላቸው ይናገራል። ከዚያ በኋላ ግን በግዳጅ የሽብር ቡድኑን ተቀላቅያለሁ ነው የሚለው። አብርሃም አለቆቹ “የብልጽግናን ወታደር እንደመስሰዋለን፣ ደምስሰን እኛ እራሳችን እንመራቸዋለን” እንደሚሏቸው ተናግረዋል።
የብልጽግና ወታደር መከላከያ፣ ልዩ ኃይልና ፋኖ ሊወጋችሁ መጥቷል እንደሚባሉም ገልጿል። የመከላከያን ምት አልችል ሲል እጁን እንደሰጠ የሚናገረው አብርሃም ያን ሁሉ ግፍ ያሳለፈ መከላከያ እንደዚህ ይቀበለናል ብዬ አላሰብኩም ነበር ብሏል። ላደረጉልኝ ሁሉ ምስጋና ይገባቸዋል፣ በጣም ተንከባክበውናል ነው ያለው።
ከሰባት ዓመት በላይ ያለ ሰው እንዳይቀመጥ ከመጡ ያርዷችኋል ይሉናል። “ይገድሏችኋል፣ ያርዷችኋል፣ ቤት ውስጥ ቁጭ ብላችሁ ከምትሞቱ ገድላችሁ ብትሞቱ ይሻላችኋል፣ ከሰባት ዓመት በላይ ያለን ሰው ይገድላችኋል፣ ከሞት ላትተርፉ ነገር ዝም ብላችሁ ወደ ውጊያ ብትገቡ ይሻላችኋል” ይሉናልም ብሏል።
ለግዳጅ እምቢ ያለ ልጅ እናት አባቱ ይታሠራሉ፣ እናት አባት ሲታሠሩ የግድ ወደ ውጊያ እንገባለን ነው ያሉት። የሽብር ቡድኑ ታጣቂዎች እጃቸውን ሰጥተው በታላቋ ኢትዮጵያ በሰላም እንዲኖሩም ጥሪ አቅርቧል።
በትግራይ ለእርዳታ የሚገባው እህል ለባለሀብቶች እና ለባለስልጣናቱ እንደሚከፋፈል የተናገረው አብርሃም የማመላለሻ ነዳጅ የለም በሚል ሰበብ ደሃው ማኅበረሰብ እርዳታ እንደማይደርሰውም ተናግሯል። የተራቡ ድሃዎች እያሉ የሽብር ቡድኑ ታጣቂዎች የእርዳታ ምግብ እየተመገቡ እንደሚዋጉም አረጋግጧል። “ስንቅ ከሕዝባችን፣ ትጥቅ ከጠላታችን” እየተባለ አብዛኛው ታጣቂ ማርከን እናስታጥቃችኋለን እየተባለ በባዶ እጁ ነው የሚገባው ነው ያለው።
“ውረሩ፣ ያገኛችሁትን ግደሉ” እየተባልን ነው የምንመጣውም ብሏል።
የ55 ዓመቱ ገብረ ሰንበት ገበረ ኪዳን ደግሞ ነባር ታጋዮች ተብለን አዲስ ክፍለ ጦር ተመስርቶልን ወደ አፋር ተላክን ነው ያሉት። ከአፋር በኋላ ወደ ትግራይ ተመልሰው በወልቃይት በኩል መምጣታቸውንም ገልፀዋል። በተደጋጋሚ እየከዳሁ በተደጋጋሚ በግዴታ ተመልሼያለሁ ነው ያሉት። ለመከላከያ ሠራዊት እጃቸውን ከሰጡ በኋላ በጥሩ እንክብካቤ ላይ እንዳሉም ተናግረዋል።
የአክሱም ተወላጇና የአክሱም ዩኒቨርሲቲ የሁለተኛ ዓመት ተማሪዋ ሮዛ ሙሉጌታ ከቤቱ እኔ ነኝ ታላቋ፣ ከቤት አንድ ሰው መውጣት ደግሞ ግዴታ ነው፣ ብዙ ጊዜ ተደበቅሁ፣ ነገር ግን ቤተሰብ ይታሠራሉ፣ ቤተሰብ ከሚታሰሩና ከሚንገላቱ እኔ ብሞት ይሻለኛል ብዬ መጣሁ ነው ያለችው። በሽብር ቡድኑ ውስጥ ለሁለት ወራት እንደቆየች የተናገረችው ሮዛ ያለ መሣሪያ ውጊያ እንዳስገቧትና እጇን መስጠቷን ነው የተናገረችው።
ትግራይን ታላቅ ማድረግ አለብን ይሉናልም ብላናለች። የትህነግ የሽብር ቡድን መሪዎች የሚፈልጉት እንዲፈፀምላቸው እንጂ ሕዝቡ የሚፈልገውን አንዳችም ነገር እንደማያዳምጡና እንደማይቀበሉም ገልፃለች። የትግራይ ሕዝብ የሕወሃት ጠብ አጫሪነት እና እንግልት እንደሰለቸውም ሮዛ ተናግራለች። የሕወሃት መሪዎች ለስልጣናቸው ሲሉ የማያደርጉት ነገር እንደሌለም አስታውቃለች።
እርዳታ ስጡን ስንል፣ የእርዳታ እህል አይገባም፣ እህል የለም ይሉናል፣ ነገር ግን ስልጠና ከገባሁ ጀምሮ የምመገበው የእርዳታውን ስንዴ ነው፣ የገባኝ አሁን ነው እርዳታውን ታጣቂው እንደሚበላው ነው ያለችው።
“የትግራይ ልጆች ለማይሆን ነገር ዋጋ አትክፈሉ፣ እጃችሁን ስጡ፤ እኔ እጅ የሰጠኹባቸው ሰብዓዊነት የሚሰማቸው እና እውነተኛ ኢትዮጵያውያን ናቸው፣ እናንተም እጃችሁን ስጡ፣ ኢትዮጵያን አንድ ለማድረግ እጃችሁን በመስጠት ተባበሩ” ነው ያለችው ሮዛ።
ውረሩ የሚባሉት ሕዝብ በሚናገራቸው ልክ ሳይሆን ደግና ከትግራይ ሕዝብ ጋር መቼም ቢሆን እንደማይለያይም ገልጸዋል ታጣቂዎቹ። (ታርቆ ክንዴ፤ አሚኮ)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
የኢትዮጵያን መሪዎች ዛሬ ነቅተዋል እንጂ የ ወያኔ ልብ እንደፈለጉት ነው የሚዘውረው የነበረው። ሰላም እያለ፡ ስንቅና መድሃኒት መግብ ዚያገባ ጦርነት ይጀምራል። የኣብይን ርህራሄ እንደ ጅልነት ቆጥሮ ለሰወስተኛ ግዜ ጦርነት መክፈቱ ለጥፋቱ መሆኑ ወያነ ረስቶትስል።