
አሁን ላይ ጃዋር የፖለቲካ ምሕዋሩን ስቶ የሚሄድበትን መንገድ የማያውቅ ሆኗል። በዚህ ኪሣራ ውስጥ ተስፋ ሰጪ ሆኖ ያገኘው የሥራ ማቆም አድማ መጥራት ነው። እስካሁን ያልተሳኩ የሥራ ማቆም አድማዎችን ጠርቷል፤ በሌሎችም ባልተጋበዘባቸው ጥሪዎችም ድንኳን ሰብሮ በመግባት ደጋሾቹን ድግሱን አምክኖባቸዋል። ግን አላረፈም፤ አሁንም ሌላ ጥሪ አድርጓል፤ ይኼኛውን ግን እሱ የሌለበት ለማስመሰል ምሥጢራዊ ለማድረግ እየሞከረ ነው። ልደቱ አያሌው የሽግግር መንግሥት የዘርፉ ባለሙያ በመሆን የክብር ዶክትሬት እንዲሰጠው ተግቶ እየሠራ እንዳለው ጃዋርም በሥራ ማቆም አድማ ጥሪ ብቸኛው የዘርፉ ባለሙያ እየሆነ መጥቷል።
አዲስ ሪፖርተር፤ ጃዋር [“ከመምህራን ማሕበር ጋር በታህሳስ ወር አመጽ ለማስነሳት ተስማምተናል” ማለቱን ማሕበሩ ነቀፈ፤] በሚል ርዕስ ያወጣው የዜና ዘገባ ይህንኑ የሚጠቁም ነው።
ጃዋር መሐመድ በታህሳስ ወር ከኢትዮጵያ መመህራን ማህበር ጋር በመተባበር አመጽ ለማስነሳት በሚስጢር ስምምነት ላይ መደረሱን አስመልክቶ ያሰራጨው መረጃና ይህንኑ ለማስፈጸም አስፈላጊ በጀት መዘጋጀቱን አስመልክቶ ማህበሩ ምንም ነገር እንደሌለ አስታወቀ። ይልቁኑም ማህበሩ ከመንግስት ጋር በበርካታ ጉዳዮች እየሰራ መሆኑን ነው ያመለከተው። ጃዋር ይህን ያለው በስሩ ላሉት ተልዕኮ አስፈጻሚዎቹ በሚስጢር እንዳሰራጨ ሪፖርት ባቀረበበት መድረክ ላይ ነው።
“ከመምህራን ማህበር ጋር ስምምነት መደረሱ ሌሎች አደረጃጀቶችን በተለይ የሰራተኛ ማህበራት ተወካዮችን ስለሚያነቃቃ መረጃው በሕዝቡ ውስጥ በስፋት በወሬ ደረጃ እንዲሰራጭ በተላለፈውና በተላከው በጀት መሰረት ስራ እየተሰራ ነው” በማለት ጃዋር ማህበሩን በመጥቀስ በታህሳስ ወር አድማ ለማስነሳት ስምምነት ላይ እንደተደረሰ ሪፖርት ባቅረበበት ስብሰባ ላይ የተገኙ ናቸው መረጃውን ለአዲስ ሪፖርተር የላኩት።
ከጉዳዩ ጋር በተገናኘ ለአዲስ ሪፖርተር ፤ምላሻቸውን የሰጡት የኢትዮጵያ መምህራን ማኅበር ፕሬዝዳንት ዶክተር ዮሐንስ በንቲ፣ “ጃዋር መሐመድ ስለተናገረው ንግግር ሆነ ዕቅድ የሰማነውም ፤ የምናውቀው ምንም ነገር የለም፤ በሌለ ነገር ምላሽ መስጠት አይቻልም” ሲሉ ዜናው እንዳስፈገጋቸው አመልክተዋል።
ማኅበሩ ከየትኛውም የፖለቲካ እንቅስቃሴ ወገንተኝነት ነፃ የሙያ ማህበር መሆኑን ያነሱት ዶ/ር ዮሐንስ፣ መረጃውን ከአዲስ ሪፖርተር መስማታቸውን በማመልከት የጃዋርን ምኞት አጣጥለዋል። አክለውም ማህበራቸው “ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅምና ልማት አጀንዳ ገለልተኛ ልንሆን አንችልም” ብለዋል።
የሀገር ሉዓላዊነትንና የቀይ ባሕር ጉዳይን እጀንዳቸው አድርገው እንደሚይዙ ያስታወቁት የኢትዮጵያ መመሕራን ማህበር ፕሬዚዳንት፣ ከመንግስት ጋር “በከፍተኛ ደረጃ” ባሉት አግባብ አብረው እየሰሩ መሆናቸውን አስታወቀዋል።
በደሞዝ፣ በጥቅማ ጥቅሞችና በመብት ዙሪያ ከመንግስት ጋር በትኩረት እየሰሩ እንደሆነ ያመለከቱት ዶ/ር ዮሐንስ፣ ልማትን የሚደግፉት እንደ ዜጋ የልማቱ ተጠቃሚ እንደሚሆኑ በአመክንዮ ስለሚረዱ እንደሆነ አመልክተዋል።
“ እኛ” አሉ ፕሬዚዳንቱ “ እኛ የሙያ ማህበር ነን፣ የማናስበውም እንደ ሙያ ማህበራችን በአመክንዮና በምክንያት ነው። በዚሁ አግባብ ሚናችንን ጠንቀቀን እናውቃለን”
ለሁለተኛ ጊዜ የዓለም መመህራን ማሕበር የስራ አስፈጻሚ አባል በመሆን አፍሪካን ወክለው የተመረጡት ዶክተር ዮሐንስ፣ ጠብመንጃ ያነሱ ኃይሎች ወደ ሰላማዊ ድርድር እንዲመጡ የሚመሩት ማሕበር እምነትና ፍላጎት ሲሆን በዚህ ረገድ አበክሮ እንደሚሰራም አመልክተዋል።
“በአገሪቱ የታጠቁ ኃይሎች ወደ ድርድር እንዲመጡ ከሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ጋር በቅርበት እየሰራን እንገኛለን” ብለዋል። አክለውም በየትኛውም ሁኔታ ግጭት እንደ አገር የሚመረጥ ባለመሆኑ ማህበራቸው በዚህ አግባብ ሰላም እንዲሰፍን እንደሚሰራ አመልክተዋል።
ቀይ ባህርን አስመልክቶ “አጀንዳው የመንግሥት ሳይሆን የሕዝብና የአገር ነው” ያሉት ዶክተር ዮሐንስ፣ “ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ጥቅም አንፃር ገለልተኛ መሆን አንችልም” ሲሉ በድጋሚ የማህበራቸውን አቋም አስታውቀዋል። ማኅበሩ የተቋቋመበት ዓላማም ፣የሚመራበት መንገድ ፣በሳይንሳዊ እና ሙያውን መሰረት ባደረገ መልኩ እንደሆነም አስገንዝበዋል።
ጃዋር የኢትዮጵያ መምህራን ማሕበር በህዳር ወር በኢትዮጵያ አመጽ ለማቀጣጠል አስፈላጊውን ውይይት በማድረግ መስማማቱን፣ ለዚሁም በቂ በጀት መመደቡን አለኝ በሚለው መዋቅር ማስተላለፉን፣ ይህም በስፋት እንዲወራ፣ በተዋረድ ጊዜው ሲደርስ ሚዲያዎች እንዲቀባበሉት እንደሚደረግ ገልጾ አጀንዳ ማሰራጨቱን አዲስ ሪፖርተር የሰማችው ይህንኑ መመሪያ ሰምተናል ካሉ ምልምሎቹ ነው።
የሕክምና ባለሙያዎችን አመጽ እንደሚመራ ሲያስታውቅ የነበረው ጃዋር በዓመቱ መጀመሪያ ትምህርት ቤት ሲከፈት ዓመጽ እንደሚጀመር በክረምቱ መገባደጃ ላይ አስታውቆ እንደነበር አይዘነጋም። (አዲስ ሪፖርተር)
ጎልጉል፤ የድረገጽ ጋዜጣ




የሃበሻ ጠላቱ ራሱ ነው። በቅርቡ ለአንድ ዓመት የከፍተኛ ት/ቤት ተማሪዎች እንዲያስተምሩ በማለት ያሳለፈውን ውሳኔ በመቃወም አንዳንድ ተማሪዎች ዳዎን ዳዎን እያሉ ማላዘናቸውን አንድ የድህረ ገጽ የሩቅ ዜና አቀባይ ሲዘግበው ” ህዝባዊ አመጽ በብልጽግና ላይ ተጀመረ” በማለት ነዳጅና ዘይት ተቀላቅሎ እንደጠጣ ተሽከርካሪ ሲንደቀደቅ መስማት ምን ያህል ወሬው ሁሉ የተዛባና የፈጠራ መሆኑን ያሳየናል። የተማሪ ተቃውሞ ሃገር አፈረሰ እንጂ ሃገር ሲገነባ አላየንም። የንጉሱን ከዙፋናቸው መውረድ ሌባ ሌባ በማለት ባልገባቸው ነገር የተሳደቡት እነዚያ የፓለቲካ ድውያን በ 17 ዓመቱ የደርግ እሣት ተለብልበው ገለባ ሆነው ቀርተዋል። ሲጀመር በሃበሻ ምድር የመንግስት ለውጥም ሆነ የፓለቲካን ጥያቄ በአመጽ ለማስፈጸም መሞከር ትንኝን በመዶሻ እንደመግደል ይቆጠራል። አይተነዋል፤፡ ኑረንበታል፤ ከአመጽና ከያዘው ጥለፈው ፓለቲካ የተረፈን የአመድ ክምር ብቻ ነው።
አሁን ላይ ያለ ቅጥ የተጣረሰው የፓለቲካ ስሪት ሰውን የሚያሰላው በቋንቋውና በክልሉ አልፎ ተርፎም በሃይማኖቱ በመሆኑ ለራስ ሲቆርሱ አያሳንሱ ሆነና ጦም አዳሪው በዛ። ግን እኮ ቅብጠትን፤ በህዝብ እንባ መሳቅን ያኔም አይተነዋል። ፍጻሜአቸው ግን የሮም አወዳደቅ ነው የሆነው። ሰው እንዴት ከዚያ አይማርም። ወያኔ ሀ ብሎ አመጽ የጀመረው አዲስ አበባ ዪንቨርስቲና በአዲስ አበባ አካባቢ ባሉ አንዳንድ ሻሂ ቤቶች ውስጥ አልነበረምን? የዛሬው የሻቢያ ጨካኝ መሪ የአዲስ አበባ ዪንቨርስቲ ተማሪ አልነበረም እንዴ? ግን ከኢትዮጵያ ጋር ሰላም ፈጥሮ ለሁለቱም ህዝቦች ጠቃሚ ነገር ከመስራት ይልቅ ከአረብ ጋር መጣመሩ ይመቸኛል ብሎ ተያይዞታል። ይህ መታመም አይደለም የሚሉ ሁሉ ራሳቸው የታመሙ ናቸው።
ጃዋር የፓለቲካል ሳይንስ መማሩን እንደ ታላቅ ነገር በመቁጠር የኦሮሞን ወጣቶች በሌላው ወገናቸው ላይ ቢለዋ ስለው እንዲነሱ የገፋፋ አሁን ደግሞ በብዙዎች አክ እንትፍ ተብሎ የተተፋ አኞ የፓለቲካ ሰው ነው። እንደ ጃዋር ያሉትን ሃገር ለማተራመስ እንደ ግብጽ፤ ሱዳን፤ ወያኔ፤ ኤርትራና ሌሎችም አይዞአችሁ በማለት በሃገራችን ውስጥ እሳት እንዲቆሰቁሱ የሚጠቀሙባቸው የፓለቲካ አሻንጉሊቶች ናቸው። እንደዚህ ያሉት ከፋፋዪችና ዘረኞች ፍጻሜአቸው አያምርም። አልጸጸትም የሚለውን መጽሃፉን በእርጋታ አንቦ ለተረዳ ልቡ የተደፈነ ያለፈውን ከአሁኑ ጋር አዛምዶ በዛሬው እውነት ላይ ለመኖር የተሳነው ሰው እንደሆነ ለመረዳት አይቸግርም። እነዚህ የብልጽግናን መንግስት አይንህ ላፈር የሚሉት የውጭና የውስጥ ቅጥረኛ ፓለቲከኞች በጭፍን ሁሉን ጥላሸት እየቀቡ፤ ተሰርቶ የቆመን ነገር እያጣጣሉ የሃገራችን ተስፋ ከሚያጨልሙት ጨለምተኞች ቀዳሚዎቹ ናቸው። በዓለም ላይ ሙሉ የሆነ መንግስት የለም። ሁሉም ከእነጉድለቱ ነው የሚንደፋደፈው። ብልጽግናም አያሌ ነገር የምነቅፍበት ጉዳይ ቢኖረኝም በዚህ 6 ዓመት ውስጥ የሠራቸውን ነገሮች አይን እያየ፤ ጀሮ እየሰማ አይኔን ግንባር ያርገው ማለት መጃጃል ነው። ብዙ ለውጦች ታይተዋል እየታዪም ነው። በአንድ እጅ መዶሻ በሌላ እጅ ጠበንጃ ተይዞ በሚሰራበት ምድር ላይ በ 27 ዓመት ያላየነውን ለውጥ በ 6 ዓመት ውስጥ አይተናል። ይህ የማይካድ ሃቅ ነው። ባንጻሩ የኑሮ መናር፤ የሰላም እጦት፤ የሰዎች መፈናቀልና መታፈን አልፎ ተርፎም መገደል አሳሳቢ መሆናቸው የታወቀ ነው። ሰርቶ ከመብላት ይልቅ መኪና አስቁሞ በመዝረፍ መኖር ለወሰነ የወንበዴ መንጋ ጊዜው ምቹ ነው። የገቢያ ግርግር ለሌባ ይመቻል እንዲሉ ከከተማ እስከ ገጠር የሰው አፈናና ዝርፊያው ጡፏል። ግን መንግስት ብቻውን ህዝብ ሳይጨመርበት የሚደረግ ነገር ዋጋ ቢስ በመሆኑ የህብረተሰብ አስተሳሰብ በጉዳዪ ላይ ችግር እየሆነ መቷል። እከሌን ገደልን፤ በዚህ ስፍራ አንድ ወታደራዊ ካምፕ አቃጠልን፤ ይህን ያህል ሰው ማረክን እንኳን ድርጊቱ ወሬው የማይሰለቻቸው ሙታኖች ባሉባት መሬት ላይ እንዴት ሰላምን ይኖራል? ዓላማ ያለው ታጣቂ የፓለቲካ ጥያቄውን ለዓለምና ለሃገሩ መንግስት አስታውቆ ከጦርነትና ግጭት ይልቅ ለሰላም ራሱን ያዘጋጃል። የሆነውና የሚሆነው ግን እንደዛ አይደለም። ወያኔ በትግራይ ሲጃፍት፤ ኦላ በኦሮሚያ ያዙኝ ልቀቁኝ ሲል የአማራው ፋኖ ደግሞ በዚህም በዚያም ጠሽ እያረገ ወንድምና እህቱን ገድሎ ለአማራ ህዝብ ነጻነት እየታገልን ነው ይለናል። ግን ይህ የብሄርተኞች መሳከር የጤና ነው የሚል የመንግስት አካልም ሆነ ተጻራሪ ሃይሎች ራሳቸው የታመሙ ናቸው። መንግስትም ይናዳል። የፓለቲካ ቡድንም እንደ ጉም ይተናል። ያን ሁሉ ያስበላውና ሁሉ አቀፍ የነበረው ኢህአፓ የታሪክ የግርጌ ማስታወሻ የሆነው ለምን ይሆን? በእውነት ሻቢያና ወያኔ እንዲሁም የኦሮሞ ጠባብ ቡድኖች ከኢህአፓ የተሻለ የፓለቲካ እይታ ኑሮአቸው ነው ዛሬ ላይ ላሉበት አቋም የደረሱት? መልሱን ላንባቢ እተዋለሁ።
በአለማችን ላይ ድንበር ዘልቆም ሆነ በሃገር ውስጥ ያልተላተመ ሃገር አይገኝም። ምዕራብና ምስራቅ አውሮፓ ላይ ያለው የአሁን ድንበር የሁለት የዓለም ጦርነት ውጤት ነው። ቀዝቃዛው ጦርነት ሲያበቃ ጀርመኖች አንድ ሲሆኑ ሌሎች ደግሞ ተፍረክርከዋል። አንዳንዶች ተራብተው 6 ሃገር ሆነዋል። ያተረፉት ግን እየየ ብቻ ነው! ይኸው እንሆ አሁን ደግሞ ራሺያ የጆርጂያን 20% መሬትና ሰፋ ያለውን የዪክሬንን መሬት በወረራ ይዛለች። ፍልሚያው ይቀጥላል! የአፍሪቃውም የሃገሮች ካርታ ሲሰፋና ሲጠብ እንደኖረ ቁሚ ይረዳል። የአረቡ ዓለም የሃገር ክልል የእንግሊዞች ወረራ ውጤት ነው። ታሪክን ወደ ኋላ ለተመለከተ ዛሬ ሃገር ነን የሚሉት ሁሉ ሃገር አልነበሩም። ኤርትራን ግብጾች/ቱርኮች/ጣሊያኖች/እንግሊዞች እየተፈራረቁ ገዝተዋታል። ይህን ያደረጉት ግን ህዝቡን አፍቅረው ሳይሆን ለራሳቸው ጥቅም ነው። ዛሬ ጅቡቲን እንደ ጉንዳን የወረሯት የውጭ ሃይሎች ለጅቡቲ ህዝብ የሚያደርጉለት አንድም ፋይዳ የለም። እኛ ግን ጥላችን ከራሳችን ጋር በመሆኑ በለው ኤርትራዊ ነው፤ በላት አማራ ናት፤ ያዘው ትግራይ ወዘተ እያልን ከአፍንጫችን ባላለፈ አስተሳሰብ ህዝባችን ለማያቋርጥ የመከራ ዶፍ ዳርገነዋል። ለዚህ ነው የእኛ ጠላት እኛው ቀዳሚ ስንሆን ሂድ አለንላችሁ ወንድምና እህቶቻችሁን ግደሉ በማለት እሳትና ንዋይ የሚያቀብሉን የውጭ ጠላቶቻችን ተጨማሪ ናቸው የምንለው። የሚበላው የሌለውን ህዝባችን ሥራ ማቆም አድማ ውስጥ መክተት ይባሱን ጠኔ እንዲገለውና የዓለም ህዝብ ዳግም ማላገጫ እንድንሆን ጠላቶቻችን ከሰነቁልን የጥፋት ጆኒያ የተወሰደ ክፋት ነው። ለማንም ለምንም አይጠቅምም። እናንተ የፓለቲካ ጉንዳኖች ደግሞ የሆነ ያልሆነውን ህዝባችን እየጋታችሁ ለመከራና ለመገዳደል ከማዘጋጀት ይልቅ ለተሻለ ገንቢ ሃሳብ ራሳችሁን አስገዝታችሁ ረዳት እጃችሁን ለተራበውና ለተጠማው ህዝባችን ብትዘረጉ የሚሻል ይመስለኛል።