
“ጫካ ስንገባ ምክንያታዊ ነበርን አሁንም የሰላምን አማራጭ ተቀብለን ስንመጣ በምክንያት ነው” – ኮሎኔል ፈንታው ሙሀባ
“በሰላማዊ መንገድ የአማራን ህዝብ ጥያቄ እናስመልሳለን” – ረ/ፕ እያሱ አባተ
ከዚህ ቀደም በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት እና በአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋሕድ) መካከል የዘላቂ ሰላም ስምምነት መፈረሙ ይታወሳል።
ሐሙስ ዕለት ደግሞ ስምምነቱን ውጤታማ ለማድረግ የማስፈፀሚያ ስምምነት ተፈርሟል።
ስምምነቱን የአማራ ክልል የሰላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ እሸቱ የሱፍ (ዶ/ር) እና የአፋሕድ ወታደራዊ አስተዳደር መምሪያ ኃላፊ ረዳት ፕሮፌሰር ኢያሱ አባተ ነው የተፈራረሙት።
በስምምነት ፊርማ ስነስርዓቱ ላይ የሰላም ሚኒስትር አቶ መሐመድ ኢድሪስን ጨምሮ ፣ የመከላከያ አመራሮች፣ የአማራ ክልል አመራሮች የሰላም ጥሪ ተቀብለው የገቡ አካላት ተገኝተው ነበር።
በቅርብ ወደ ሰላም አማራጭ የገቡት የአፋሕድ ከፍተኛ አመራር ኮለኔል ፈንታው ሙሀባ እንዲሁም ረ/ፕ እያሱ አባተ ተገኝተው ነበር።
ምን ተባለ?
የሰላም ሚኒስትር አቶ መሐመድ ኢድሪስ፦
“ይህ ዘመን ያለንን አቅም በጋራ አዳምረን አንዱ ለአንዱ ድጋፍ ሆኖ ሰርቶ ከድህነት ለመውጣት የምንተጋበትና የምንሰራበት እንጂ ኋላቀር በሆነ መንገድ አንዱ ሌላኛውን ገድሎ የሚፎክርበት ዘመን አይደለም።
“በመግደል እና በመሞት የሚሟላ ወይም የሚሳካ የፖለቲካ ፍላጎት የለም። አሸናፊ መሆን ከፈለግን ዓለም ስልጡኖች በደረሱበት ሰላማዊ የፖለቲካ ትግል ውስጥ መግባት ህዝባችንን ማልማት ለህዝባችን ለትውልዳችን የሚበጀውን መስራት እንጂ ለቀጣዩ ትውልድ መማሪያ የሆኑትን አቅም የሚሆኑትን መሰረተ ልማት ማጥፋት፣ እድሎችን ማጨናገፍ አይገባም።
“ህብረታችን ፣ መደመራችን ለልማት መሆን መቻል አለበት። አንዳንዴ የኢትዮጵያን እድገት በማይፈልጉ አካላት ፣ ማደጋችን አብሮነታችን፣ ጥንካሬያችን ስጋት ለሆኑባቸው አካላት እራሳቸው እንኳን ኃይላቸውን ሰብስበው ምንም ማድረግ ከማይችሉ ትናንሽ አካላት አጀንዳ ተቀብሎ ኢትዮጵያን ለማጥፋት ፣ ህዝቦቿን ለመጉዳት መንቀሳቀስ በታሪክም በትውልድም ተጠያቂ ያደርገናል።
“ይህ የሰላም መንገድ ሌሎችም በጫካ ውስጥ ያሉ ወገኖች ሊከተሉት የሚገባው አትራፊ መንገድ ነው።”
አቶ መሐመድ ፤ አሁን ላይ ሀሳብን ወደ መድረክ ይዞ መጥቶ መነጋገር እና በሀሳብ ማሸነፍ እየተሻለ ኋላቀር በሆነ መንገድ መሳሪያ አንግቦ የህዝብን እንቅስቃሴ መግታ፣ ህዝብ በየዕለቱ ከኑሮው ጋር የሚያደርገውን ትግል እየገቱ መፈተን የሞራልም በህግም ፣ በታሪክም ያስጠይቃል ሲሉ አሳስበዋል።

ረዳት ፕሮፌሰር እያሱ አባተ፦
“እኛ ወደጫካ ስንወጣ የተቆጠሩ ጥያቄዎች ይዘን፣ ህይወታችንን ለመስጠት ፣ ለህዝባችን ዋጋ ለመክፈል ነው የወጣነው። ከዚያ በላይ ዋጋ ከፍለን ከመንግሥት ጋር የሰላም ስምምነት ፈጽመናል።
“በብዙ መንገድ እንደ ሀገር ፣ እንደ ህዝብ የተነሱ ጥያቄዎችን መንግሥት ማዳመጥ ካልቻለ ነፍጥ አንስተን መዋጋት አለብን ብለን ስንወጣ ጥያቄዎቻችንን ቆጥረን ይዘን መንግሥት ደግሞ ጥያቄያችሁ ምንድነው ? እንከሚልበት ጊዜ ድረስ ነው ውጊያ የሚያስፈልገው። ይሄን ጉዞ ለሶስት አመት ያህል ሄደናል።
“አሁንም የቀጠናውን ሁኔታ ፣ የዓለምን ሁኔታ ተንትነን ሚሻለው መንገድ የትኛው ነው የሚለውን ረጅም ጊዜ ተወያይተን እኛም በፋኖ በኩል፣ መንግሥትም እንደ መንግሥት የገመገመው ያየው ነገር ኖሮ ነው ይሄን የሰላም ስምምነት ለመፈራረም የማስፈጸሚያ ሰነዱንም ለመፈራረም የበቃነው” ብለዋል።
ረ/ፕ እያሱ ፥ ጥያቄዎቻችን ቆጥረን አስቀምጠናል አፈጻጸሙን በተመለከተ መንግሥትም ካለፈው ሂደት ተምሮ ሁሉንም ነገር ይፈጽማል ብለን እናምናለን ለዛም ነው የፈረምነው ሲሉ ገልጸዋል።
ቆጥረን ካስገባነው ውጭ ሌላ ጥያቄ የለም ስለዚህ ሌሎችም ወደዚሁ የሰላም መስመር ቢመጡ የተሻለ ነው ሲሉ አክለዋል።
እነሱ (መንግሥትን የሚታገሉ) “ከሰይጣንም ጋር ቢሆን አብረን እንሰራለን” ይላሉ እኛ የአማራን ርስት ለማስጠበቅ፣ ብሔራዊ ጥቅማችንን ለማስከበር ፣ የአማራን ህዝብ ጥያቄ ለማስመለስ ከመንግሥት ጋር በሰላም እንሰራለን ማለታችን ከባድ ውሳኔ ነበር ግን ወስነነዋል ሲሉ ገልጸዋል።
“እኛ አሁንም ከትግል አልወጣንም። የትግል ጥያቄዎቻችን የሚያርፉበት ምዕራፍና ቀጣይ ምንሄድበት መንገድ ምንድነው? የሚለውን ነው ያስቀመጥነው። በሰላማዊ መንገድ የአማራን ህዝብ ጥያቄዎች ሁሉ እናስመልሳለን። ልንሞት ነው የወጣነው ከእግዚአብሔር ውጭ ማንም ዋስትና አልነበረንም። እስከፍጻሜያችን ድረስ በአማራ ህዝብ ጥቅም ጥያቄ ላይ አንደራደርም። በሀገራችን ሉዓላዊነትና ጥቅምም ላይ አንደራደርም” ብለዋል።
ኮሎኔል ፈንታው ሙሀባ ምን አሉ ?
“ለሶስት ዓመት ያህል በጫካ ቆይተናል። ወደ ትግል/ጫካ ስንገባ ምክንያታዊ ነበርን አሁንም የሰላምን አማራጭ ተቀብለን ስንመጣ በምክንያት ነው።
“ይሄ ውይይት ዛሬ የተጀመረ አይደለም። የሰላማዊ መንገዱ የተፈለገበት ምክንያት አለ የሰላም ውይይቱ ለአንድ አመት ያህል የተካሄደ ነው።
“የዛሬ አመት ጥር ወር ላይ ዳውንት ላይ የአፍሪካ ህብረት፣ ኢጋድም መጥተው እኔም ባለሁበት ጠቅላላ ውይይት አድርገናል። በዛ ውይይት በጥሩ መንፈስ በጥሩ መግባባት ነው የተለያየነው። በግብታዊነት የተደረገ ነገር የለም።
“ውይይቱ አንድ አመት የተደረገ፣ ምክንያታዊ፣ ህጋዊነትን የተከተለ እንጂ ሰዎች እንደሚሉ በክህደት ወይም እጅ በመስጠት አይደለም” ብለዋል።
ኮለኔል ፈንታው በአማራ ክልል ያለው ትግል “ተጠልፏል” ያሉ ሲሆን ጠላፊዎቹ ህወሓት፣ ሻዕቢያ፣ ግብፅ ናቸው ሲሉ ገልጸዋል።
“ከነዚህ ሰዎች ጋር ሆኖ እንዴት የአማራን ጥያቄ ማስመለስ ይቻላል ? እንደ ሀገር የኢትዮጵያን እና ህዝቧን ጥያቄ ማስመለስ ይቻላል ? ካልን በምንም ተአምር አይቻልም ” ብለዋል።
” ይህች ሀገር ዛሬ የምትተራመሰው ህዝባችንም መረጋጋት ያቃተው ህወሓት እና ሻዕቢያ ባፀደቁት ህገመንግስት ነው ” ሲሉ ተናግረዋል።
” ኢትዮጵያን እያተራመሱ ያሉት አሁንም ህወሓት ፣ ሻዕቢያ እና ግብፅ ናቸው ” ሲሉ ከሰዋል። ” ብር ይመድባሉ፣ መሳሪያ ይሰጣሉ ፣ ተተኳሽ ይሰጣሉ፣ አሁንም ሀገሪቱ እንዳትረጋጋ እንዲያውም ጦርነቱ አማራ ክልል እንዲካሄድና ትርምሱ እዛው እንዲቆም ይፈልጋሉ ፤ ትንኮሳው ወደነሱ እንዳይመጣ በሩቅ ጦርነቱ ትርምሱ አማራ ክልል እንዲሆን ይፈልጋሉ ፤ እኛ አንቀበልም ” ብለዋል።
የአማራ ክልል ምክትል ርእሰ መሥተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) በበኩላቸው ፤ “ሌሎች በትግል ውስጥ ያሉ ኃይሎች የክልላቸውን እና ሀገራቸውን ቁመናና ወርድ ተገንዝበው ለክብራቸው ሲሉ ወደ ሰላም አማራጭ እንዲመጡ በድጋሚ የሰላም ጥሪ አቅርበናል ” ብለዋል። (@tikvahethiopia)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ


Leave a Reply