
የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ግድያ በፈጸሙ ጥፋተኞች ላይ ተጠያቂነት እንዲረጋግጥ አሳስቧል
የመከላከያ ሠራዊት የምዕራብ ዕዝ በአካባቢው ግድያና ጥቃት በፈጸሙ ማንነታቸው በግልጽ ያልተነገረ ታጣቂዎችን የመደምሰስ ዕርምጃ መውሰድ መጀመሩን ያስታወቀ ሲሆን፣ ጥቃት በተሰነዘረባቸው አካባቢዎች ላይም 150 ኪሎ ሜትር የሸፈነ ስምሪት ማድረጉንም ገልጿል።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ዞን ከዚህ ቀደም ለተደጋጋሚ ጊዜ እንዲሁም ሰሞኑን በነዋሪዎች ላይ በተቃጣው ግድያና ጥቃት ሥጋት ውስጥ የወደቁ የአካባቢው ነዋሪዎች መንግሥት ደኅንነታቸውን በዘላቂነት እንዲያስጠብቅላቸው ጠየቁ።
ነዋሪዎቹ ጥያቄያቸውን ያቀረቡት የሰሞኑን ግድያና ጥቃት ተከትሎ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኰንን የተመራ የፌዴራልና የክልል መንግሥት ከፍተኛ ባለሥልጣናት ቡድን ባለፈው ዓርብ መስከረም 8 ቀን 2013 ዓ.ም. አካባቢውን ጎብኝቶ ነዋሪዎቹን ባነጋገረበት ወቅት ነው።
በአካባቢው ጉብኝት በማድረግ ከነዋሪዎች ጋር የተወያዩት የመንግሥት ባለሥልጣናት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ደመቀ መኮንን፣ የሰላም ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል፣ የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻዲሊ ሀሰን፣ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ተመስገን ጥሩነህ፣ የብልፅግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ብናልፍ አንዷለምና ሌሎች የሁለቱ ክልሎችና የፌዴራል ከፍተኛ አመራሮች እንዲሁም የፀጥታ አመራሮች ናቸው።
ከነዋሪዎቹ ጋር የተወያዩት ባለሥልጣናት በአካባቢው ዘላቂ ሰላምን የማስፈንና በአጥፊዎች ላይ አስፈላጊው ዕርምጃ የመውሰድ ተግባር እየተከናወነ መሆኑን አስታውቀዋል።
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች እየታዩ ያሉ የፀጥታ መደፍረሶችንና በሰለማዊ ነዋሪዎች ላይ እያጋጠሙ ያሉ ጥቃቶችን አስመልክቶ ባወጣው መግለጫ መንግሥት በአካባቢው የነዋሪዎችን ደኅንነት ማረጋገጥ እንዳለበት አሳስቧል።
በተጠቀሰው አካባቢ ከዚህ ቀደምም ተመሳሳይ ጥቃቶች በተደጋጋሚ ማጋጠማቸውን የገለጸው ኮሚሽኑ፣ መንግሥት እየደረሰ ያለውን ተደጋጋሚ ጥቃት ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው አካላት ገለልተኛ፣ ፈጣንና ውጤታማ ምርመራዎችን በማካሄድ ጥቃትና ግድያውን በፈጸሙ ጥፋተኞች ላይ ተጠያቂነት እንዲያረጋግጥ አሳስቧል።
ኮሚሽኑ በአካባቢው ከሚገኝ አንድ መንግሥታዊ ምንጭ አገኘሁት ባለው መረጃ ቢያንስ በሁለት ዙር በደረሱ ጥቃቶች ባልታጠቁ ሲቪሎች ላይ ግድያዎች መፈፀማቸውን እንዲሁም በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች መፈናቀላቸውን ማረጋገጥ እንደቻለ ገልጿል፡፡
ከክልሉ መንግሥት ባገኘው መረጃ በርካታ ነዋሪዎች በጥቃቱ ምክንያት መፈናቀላቸውንና ከጥቃቱ በኋላ ከተፈናቃዮቹ መካከል 300 ያህሉ ወደ ቀያቸው እንዲመለሱ መደረጉን እንዳረጋገጠ፣ የአገር መከላከያ ሠራዊትና የፌደራል ፖሊስ ከክልሉ የፀጥታ ኃይሎች ጋር በመተባበር አካባቢውን ለማረጋጋት እየሠሩ ስለመሆኑ መረጃ ማግኘቱንም አስታውቋል።
ኮሚሽኑ ሁሉም የፖለቲካ ቡድኖችና ባለድርሻ አካላት ገንቢ ውይይት እንዲያደርጉና ከማንኛውም ዓይነት የሁከት ድርጊቶች እንዲታቀቡ ጥሪውን ያቀረበ ሲሆን፣ ሁሉም አካላት ሕገ መንግሥቱንና ኢትዮጵያ ፈርማ የተቀበለቻቸውን ሌሎች አግባብነት ያላቸውን የሰብዓዊ መብት ድንጋጌዎች ውስጥ የተቀመጡ መብቶችንና ግዴታዎችን እንዲያከብሩ ኮሚሽኑ ጠይቋል። በቀጣይም ጉዳዩን በንቃት እንደሚከታተለው ገልጿል። (ዮሐንስ አንበርብር፤ ሪፖርተር)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply