የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን /ኢሰመኮ/ በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ወለጋ ዞን ግድያ እና መፈናቀል መኖሩን ከነዋሪዎች መረጃ የደረሰው መሆኑን አስታውቋል።
ኮሚሽኑ በምሥራቅ ወለጋ ዞን፣ ኪራሙ ወረዳ የሚገኙ ሲቪል ሰዎች ለደኅንነታቸው አስጊ ሁኔታ ላይ የሚገኙ መሆናቸው የሚያሳስብ መሆኑን ነው ብሏል።
በዚሁ ወረዳ፣ ቦቃ ቀበሌ መስከረም 7 እና 8 ቀን 2014 ዓ.ም በደረሱ ሦስት ተያያዥ ጥቃቶች በአጠቃላይ 18 ሲቪል ሰዎች መገደላቸውን፣ እንዲሁም መስከረም 8 ቀን 2014 ዓ.ም በውልማይ ቀበሌ በተፈጸመ ሌላ ጥቃት 11 ሰዎች መገደላቸውን ነዋሪዎች ለኮሚሽኑ አሳውቀዋል።
በኪራሙ ወረዳ ባለው አሳሳቢ የፀጥታ ሁኔታ ምክንያት ከተለያዩ የወረዳው አካባቢዎች ተፈናቅለው በኖሌ ቀበሌ፣ በሀሮ እና ኪራሙ ከተሞች ተጠልለው የሚገኙ ከ40 ሺህ በላይ የሚሆኑ ነዋሪዎች ለወራት አስቸኳይ ሰብአዊ ዕርዳታ እና ሌሎች ድጋፎችን ባለማግኘታቸው አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኙ ነዋሪዎች ለኮሚሽኑ ተናግረዋል።
በአሁኑ ወቅት ኪራሙ ወረዳን ከቡሬ እና ነቀምቴ ከተሞች ጋር የሚያገናኙ ዋና ዋና መንገዶች ለተሸከርካሪ እንቅስቃሴ ተዘግተው እንደሚገኙ ኮሚሽኑ አረጋግጡን ገልጿል።
የፌዴራል እና የክልሉ መንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በኪራሙ ወረዳ ላለው የፀጥታ ስጋት ዘላቂ መፍትሔ ለመስጠት እና በነዋሪዎች ላይ በተደጋጋሚ ጥቃት የሚያደርሱ ኃይሎችን ከሕግ ፊት ለማቅረብ ተጨባጭ እርምጃዎችን እንዲወስዱ ኢሰመኮ አሳስቧል። (ኢብኮ)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Ashebir Shiferaw says
የሰባዊ መብት ኮምኒሺኑ ሰዎቹ የሚፈናቀሉበትን መሰረታዊ ምክንያት ለማወቅ ሞክሯል? ወይስ አልፈለገም? ምክንያቱን ቢያውቅ የመፍትሄ ሃሳብ ለመጠቆምም ሆነ ተፈናቃዮቹም ምን ማድረግ እንደሚግባቸው አቅጣጫ ለማሳየት ይመቸው ነበር።