• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

በአውቶቡሶቹ ግዢ ቢያንስ 1 ቢሊዮን ብር ተሰርቋል፤ ዶ/ር ዐቢይ አስቸኳይ ማብራሪያ ጠይቀዋል

February 24, 2023 08:39 am by Editor 1 Comment

ሰሞኑን የአዲስ አበባ መስተዳድር ለከተማዋ አስመጣሁት ካላቸው አውቶቡሶች ቢያንስ አንድ ቢሊዮን ብር መመዝበሩ ተነገረ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በስድስት ቀን ውስጥ ስለ ጉዳዩ ማብራሪያ እንዲሰጣቸው ትዕዛዝ አስተላልፈዋል። ጉዳዩ ከንቲባዋን በቀጥታ የሚመለከት ነው ተባለ።

የአዲስ አበባ መስተዳድር ከቻይና ያስገባቸው 100 አውቶቡሶች ግዢ ጉዳይ የመነጋገሪያ አጀንዳ ሆኖ ሰንብቷል። መስተዳደሩ እንደሚለው አንዱ አውቶቡስ የተገዛው በ19 ሚሊዮን ብር ወይም 355ሺህ ዶላር አካባቢ ነው። የ200ዎቹ ድምር ዋጋ ደግሞ 3.8 ቢሊዮን ብር ወይም 71 ሚሊዮን ዶላር ነው። አውቶቡሶቹ ይህንን ያህል ለምን እንዳወጡ ለሚጠየቀው ጥያቄ የአዲስ አበባ መስተዳደር የሚሰጠው ምላሽ አውቶቡሶቹ ልዩ ናቸው የሚል ሲሆን ለዚህም የሚከተለውን ዝርዝር ያቀርባል።

  • በሀይገር ካምፓኒ የተመረቱና ለመጀመሪያ ጊዜ በሀገር ውስጥ አቅራቢዎች መቅረብ መቻሉ
  • ለአካል ጉዳተኛ በልዩ ሁኔታ አጋዥ ሆነው የተሰሩ እና ዊልቸር ተጠቃሚ ለሆኑ የዊልቸር ማቆሚያ (ማሰሪያ) ያላቸው መሆኑ
  • በቴክኖሎጂ ቁጥጥር ለማድረግ ሲስተም የተገጠመላቸው መሆኑ
  • ተሳፋሪን ለመጫን ሲቆሙ ከመሬት ወለል ዝቅ ብለው ምቹ በሆነ መልኩ የሚጭኑ
  • ርዝመታቸው 12 ሜትር ፣ ቁመቱ 3.4 ሜትር እንዲሁም ስፋታቸው 25 ሜትር ነው
  • 40 ሰው በወንበርና 30 ሰው ያለ ወንበር በድምሩ 70 ሰው በተንደላቀቀ ሁኔታ የመያዝ አቅም ያለው
  • እንደየመንገዱ ባህሪ (ሁኔታ) ዝቅ እና ከፍ እያሉ የተሳፋሪን ምቾት ጠብቀው የሚጓዙ
  • ተሳፋሪ በጉዞ ላይ እያለ የUSB PORT (ሞባይል ቻርጅ) ማድረግ የሚያስችል ሲስተም አለው
  • የቻንሲ አካላት (ካንቢዎ፣ ሞተርና ኤርባግ ) በቀላሉ እንዳይጎዳ ጠንካራ ብረት የተገጠመላቸው
  • ተሳፋሪዎች በድምፅ የደረሱበትን ቦታ መረጃ የሚሰጡ
  • አውቶብሶቹ ሙሉ በሙሉ አለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ
  • የተሳፋሪውን እንቅስቃሴና ደህንነት በካሜራ መቆጣጠር የሚችል
  • የሞተር ሙቀትን የመከላከል አቅም ፋን (ማቀዝቀዣ) የተገጠመላቸው መሆኑ ልዩና ፍፁም ዘመናዊ እንደሚያደርጋቸው ከከንቲባ ጽ/ቤት ያገኘነው መረጃ ያሳያል በማለት አዲስ ሚዲያ ኔትዎርክ ከአስር ቀን በፊት በፌስቡክ ገጹ አብራርቷል።

ይህንን አወዛጋቢ ጉዳይ በተመለከተ የፋና ብሮድካስት ጋዜጠኛ የሆነው ዳዊት መስፍን የከተማዋን የትራንስፖርት ቢሮ ኃላፊ ምትኩ አስማረን እና የግዢ ክፍል ኃላፊውን መንግሥቱ አጥናፉን አነጋግሮ ነበር። ጣቱን በተጠያቂዎቹ ላይ ከማነጣጠር ይልቅ የቤት ሥራውን በተገቢው ሠርቶ የጥያቄ ሸጉጥ ቢያነጣጥርባቸው የተሻለ ነበር የሚሉ አስተያየት ሰጪ “ዳዊት ይጠይቃቸው የነበረው ወይ ተጽፎ የተሰጠውን ነው ወይም ከጠየቀ በኋላ መልሱን ከካሜራ ውጪ እያሳያቸው ነበር” በማለት ከተማው ሚዲያውን መጠቀሚያ እንዳደረገው ይናገራሉ። ሙያዊ ምርመራ ያደረገውና ቃለ ምልልሱን የሰማው ኢንጂነር ፋሲል ሁለቱ ባለሥልጣናት ገዢ ሳይሆን ሻጭ ነበር የሚመስሉት፤ ለገዢ ሳይሆን ለሻጭ ነበር ይከራከሩ የነበረው በማለት አስተያየቱ ሰጥቷል።

ሁለቱ ኃላፊዎች ተዝናንተው የሰጡት መልስ በአብዛኛው አውቶቡሶቹ እንዴት ልዩ እንደሆኑ በመግለጽ ነበር። ከዚህ በተረፈ ቃለ ምልልሱ የተጠናቀቀው ተጠያቂዎቹ የተለመዱ “እንደ አጠቃላይ፣ እንደ ከተማ፣ እንደ ተጠቃሚ፣ እንደ ተቀመጠው አቅጣጫ፣ …” በሚሉ የካድሬ ቃላትና አሰልቺ ወሬ እንደነበር ሌላ አስተያየት ሰጪ ተናግረዋል።

በዘርፉ የ21 ዓመት ልምድ ያለውና በትምህርቱ ሜካኒካል ኢንጂነር የሆነው ፋሲል ሽፈራው ከ21 ዓመት ልምዱ 12 ዓመት ከጨረታ ሥራ ጋር በተያያዘ የሽያጭ ኢንጂነር ሆኖ ሠርቷል፤ የጨረታ ሥራ ከፍተኛ ባለሙያ ነው። ነጻ ውይይት በተሰኘው ዩትዩብ ላይ ስዩም ተሾመ አነጋግሮት ነበር። ምሥጢሩን ለመተንተን በደንብ ተዘጋጅቶ የመጣው ባለሙያ እያለ ስለ ጉዳዩ ምንም ዕውቀት የሌለው ስዩም ከተጠያቂው ፋሲል የሚሰማውን ጥራዝነጠቅ መረጃ እየለቀመ የራሱ ትንታኔ እያስመሰለ ውይይቱን በተደጋጋሚ ሲደናቅፍ ቢቆይም ፋሲል በርካታ ነገሮችን በጨዋነትና በድንቅ ሙያዊ ትንተና አብራርቷል።

ኢንጂነር ፋሲል የአዲስ አበባ መስተዳድር በልዩ ትዕዛዝ ያሠራሁት ነው የሚለውን መዘርዝር ይዞ ያንኑ መዘርዝር እንደ ገዢ ሆኖ ወደ ቻይናዊው ካምፓኒ የአንድ ባስ ዋጋ ይጠይቃል። ፋሲል እንደሚለው ከዋጋው ሌላ ለማስመጣት፣ ለወደብ፣ ለመጫን፣ ለማስተላለፍ፣ ወዘተ ይከፈላሉ የሚባሉትን ክፍያዎች በሙሉ የአዲስ አበባ መስተዳድር ሊከፍል ይችላል ከሚለው በላይ እያደረገ ነው የአንዱን አውቶቡስ ዋጋ የሠራው። እንደ አብነት ለመጥቀስ ከጅቡቲ ወደብ ባሶቹን እየነዱ ቢያመጧቸውም እርሱ ግን ተጭነው ቢመጡ በሚል ነው የዋጋ ሥሌቱን የሠራው።

ኢንጂነር ፋሲል በሠራው እና እጅግ በተቀናጣ የዋጋ ሥሌት ትርፍ ሳይጨምር የአንድ አውቶቡስ ዋጋ ቀረጥና ግብር (ቫት) የማይከፈል ከሆነ 9.7 ሚሊዮን ብር የሚያወጣ ነው። ቀረጥና ግብር ይጨመር ቢባልና ትርፍ ባይታሰብ አንዱን አውቶቡስ በ11.2 ሚሊየን ብር ማስገባት ይቻላል። እዚህ ዋጋ ላይ የተለመደው 12% ትርፍ ይታሰብ ቢባልና በዋጋው ላይ ቢሰላ የአንዱ አውቶቡስ አዲስ አበባ ላይ የማስረከቢያ ዋጋ 12.4 ሚሊየን ብር ነው የሚመጣው። ይህ ማለት አስመጪው በአንድ ባስ 1 ሚሊየን ብር ወይም ከ200 ባሶች 200 ሚሊየን ብር ንጹህ ትርፍ ቢያገኝ በሚል ሥሌት ነው። ትርፉ በ12% ታስቦ ግን ቀረጥና ታክስ የማይከፈል ከሆነ የአንዱ አውቶቡስ ዋጋ 10ሚሊየን ብር ይሆናል። ትርፉን ከፍ አድርጎ በ20% ቢሰላ እንኳን ቀረጥና ግብር የማይከፈልበት የአንዱ ባስ ዋጋ 10.8 ሚሊየን ብር ሲሆን ቀረጥና ግብር የሚከፈል ከሆነ ደግሞ የአንዱ አውቶቡስ ዋጋ በ20% ትርፍ ሥሌት 13.3 ሚሊየን ብር ይሆናል።

ኢንጂነር ፋሲል ሽፈራው

የአዲስ አበባ መስተዳድር ግን አንዱን አውቶቡስ ገዛሁ ያለው በ19 ሚሊየን ብር ነው። በትንሹ የ5 ሚሊየን ብር ልዩነት ከፍ ካለ ደግሞ የ7 ሚሊየን ብር ልዩነት ከእያንዳንዱ አውቶቡስ ላይ አለ። ሌላ መጠቀስ የሚገባው ነገር እነዚህ አውቶቡሶች በብዛት እንደመገዛታቸው ለ200 አውቶቡስ ተመሳሳይ ዋጋ ሳይሆን ከብዛት የተነሳ ያነሰ ዋጋ እንደሚሰጥ መገመት ይቻላል።

ባለሙያው ፋሲል ሌላው በዝርዝር ያስረዳው የጨረታውን አካሄድ ነው። በተለይ በመጀመሪያውና ሁለተኛው ጨረታ አሸናፊ የነበረው ወረታ ኢንተርናሽናል ትሬዲንግ ከግዢው ከተወገደ በኋላ ሦስተኛው ውሱን ጨረታ የተካሄደው በጥሪ ነው። ውሱን ጨረታን አሠራሩ የሚፈቅድ ቢሆንም ለጨረታ ከተጋበዙት ስምንት ድርጅቶች ውስጥ 3ቱ እንደማይጫረቱ የታወቁ ሲሆን ሌሎቹ ሦስት ድርጅቶች ምንም የበቃ ሙያ እና ልምድ የሌላቸው እንዲያውም የአስመጪነት ፈቃድ ካወጡ አንድ ዓመት አካባቢ ዕድሜ ያላቸው ናቸው።

መጨረሻ ላይ በላይነህ ክንዴ ቴክኒኩን ባለማለፉ የወደቀ ሲሆን ለፋይናንስ ያለፉት ሁለት ተጫራቾች ናቸው። እነዚህም ኤሊያስ ሳኒ ዑመር እና ያደታ ጁነዲን በክሪ (ብራይተን ትሬዲንግ) ናቸው። ከመጨረሻው ተጫራች ጋር የቀረበውና 22 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያቀረበው ኤሊያስ ሳኒ ዑመር በኢትዮጵያ ውስጥ መኪና አስመጪነት ይቅርና በአጠቃላይ በአስመጪነት ያልተመዘገበ ነው። የጨረታው አሸናፊ ያደታ ጁነዲን በመኪና አስመጪነት የተመዘገበው ሁለተኛው ጨረታ የወጣ ሰሞን ነበር። ከንቲባዋ አዳነች ያመሰገኑት የያደታ ጁነዲን በክሪ ብራይተን ትሬዲንግ ጨረታውን አሸነፈ ተብሎ አንድ አውቶቡስ እጥፍ በሚያክል ዋጋ እንዲያስመጣ ተፈቀደለት።

ጥያቄው እንዲህ ጨረታውን እንዲያሸንፍ የተለፋለት ያደታ ጁነዲን ማነው? የሚለው ነው። የጥቅም ትሥሥሩ ከእነማን ጋር ነው? ከከንቲባዋ ጀምሮ እስከ ታች ትራንስፖርትና ግዢ ክፍል ይህንን ማወቅ ብቻ ሳይሆን ተሳትፏቸው ምንድነው? የሚሉት መመለስ የሚገባቸው ጥያቄዎች ናቸው።

በትህነግ ዘመን ይህንን መሰል ጉዳይ አይደለም በትኩሱ ዘመናት ከተቆጠሩ በኋላ እንኳን መጠየቅ ዋጋ የሚስከፍል ከመሆኑ አንጻር ይህ በዚህ ዘመን በሚዲያ ለሕዝብ መቅረቡ ይበል የሚያሰኝ ለውጥ ነው። ሊደፋፈርና ተጠናክሮ እንዲቀጥል ሊበረታታ የሚገባው ጉዳይ ነው።

እነዚህ አውቶቡሶች ከመገዛታቸው በፊት በዕቅድ ላይ በነበረበት ወቅት አዲስ ሚዲያ ሰኔ 21፤ 2013ዓም (ጁን 28፣ 2021) የሚከተለውን ዜና አስነብቦ ነበር፤ “በዓለም ባንክ ድጋፍ የአንድ መቶ አውቶቡሶች ግዥ ለመፈፀም እየተሰራ መሆኑን የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ አስታወቀ። አውቶቡሶቹ ሙሉ በሙሉ በአውሮፓ ስታንዳርድ ተጠናቀው የሚገቡ እያንዳንዱ አውቶቡስ ከስድስት እስከ ስምንት ሚሊየን ብር ወጪ ተደርጎበት ግዥው የሚፈፀም ይሆናል ተብሏል”።

ይህ ከአንድ ዓመት ከሰባት ወር በፊት የወጣው መረጃ የሚጠቁመው የአውቶቡሶቹን የመግዣ ገንዘብ የመጣው ከዓለም ባንክ መሆኑን እና የአንዱ አውቶቡስ ዋጋ ከስድስት እስከ ስምንት ሚሊየን እንደሚያወጣ ነው። ግዢው ተፈጽሞ በከንቲባ አዳነች የተረከቡት አውቶቡሶች የአንዱን ዋጋ 19 ሚሊዮን ብር እንደሆነ ነው። ጭማሪው በትንሹ ከእጥፍ በላይ ነው።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ይህ ጉዳይ ተጣርቶ ማብራሪያ እንዲሰጣቸው አስቸኳይ ጥያቄ ማቅረባቸውን ጎልጉል የደረሰው መረጃ ያመለክታል። በዚህ ጉዳይ ላይ የሚያስተላልፉት እርምጃ ወይም ቆራጥ አመራር በእርግጥ ከሕዝብ ጋር መወገናቸውን የሚሳይ ነው ተብሎ ይታመናል። በተለይም በሌብነቱ የከተማዋን ከንቲባ ከሥልጣን እስከማንሳት መጀገን እንደሚገባቸው አስተያየት ሰጪዎች ይናገራሉ። አለበለዚያ ይህ በቸልታ የሚታለፍ ከሆነ ሌሎች እጅግ በርካታ ሌቦችን ለማምረት ምቹ መደላድል የሚፈጥር ይሆናል። እርሳቸውንም የሌባ ተባባሪና ደጋፊ የሚያስብላቸው ይሆናል።

ኢንጂነር ፋሲል ያቀረበውን ትምህርት ሰጪ ሙያዊ ትንታኔ በሁለት ቪዲዮ የቀረበውን መመልከት ስለ ጉዳዩ የበለጠ ግንዛቤ ይሰጣል።

https://www.youtube.com/watch?v=4vZC-qBv3aQ&t=3394s
https://www.youtube.com/watch?v=qN8WcRN-JTs

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ©    

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Middle Column, News, Politics Tagged With: abiy ahmed, Adanech Abebie, addis ababa city buses, Ethiopia corruption, mayor of addis ababa, operation dismantle tplf, prosperity party

Reader Interactions

Comments

  1. Tesfa says

    February 25, 2023 09:12 am at 9:12 am

    በየዘመናቱ በብድርና በእርዳት መልክ የሚገኙ የቁሳቁስም ሆነ የጥሬ ገንዘብ የአጭርና የረጅም ጊዜ ብድሮች ሁሉ መሸራረፍና መበላት የሚጀምሩት ገና ከለጋሹ ወይም ከአበዳሪው አካል እጅ ሳይወጣ በጉዞ ላይ እያሉ ነው። አውቶቡስ ተገዛ የተባለው የሚሸጠው ኩባንያና ገዢው አካል ተመሳጥረው የሚዘርፉበት የቆየ ብልሃት በወያኔ ዘመን ከመከላከያ እስከ ቡና ሽያጭ ሲበላበት የኖረ የሻገተ ውስልትና ነው። አሁን የአዲስ አበባ መስተዳደር አንዴ በጥቁር ገቢያ ሂሳብ ነው የተገዙት ሌላ ጊዜ ሌላ የሚሉንም ይህኑ የገፈፋ ስልታቸውን ለመደበቅ ነው። ጊዜው ያለፈው 30 ዓመት ለወያኔና ለፍርፋሪ ለቃሚዎቻቸው ጠቃሚ እንደሆነ ሁሉ አሁን ደግሞ የኦሮሞ ወረፋ ሆኖ ይኸው አይናችን እያየ ይበሉናል። ሰውን ከመኖሪያው እያፈናቀሉ፤ ሲላቸው ለምን ጥቁር ለበሳቹሁ በማለት ያለምንም ሃፍረት ሰውን ከስራ ያባራሉ፤ ያስራሉ። አፍሪቃዊው የመደመር ቀመር ይህ ነው። በጊዜ ተጫውቶ ሌላው ላይ አላግጦ በሌሎች አላጋጮች ተሽቀንጥሮ መጣል።
    ምድሪቱ ፈጣሪን የማይፈሩ፤ ሰውን በሰውነቱ የማይመለከቱ ድርቡሾች አፍርታለች። ወያኔ መቀሌ ላይ ተወሽቆ ከአፋርና ከአማራ የወሰድኳቸው ቁሳቁሶች ሁሉ የማረኳቸው ናቸው ይለናል። እብደት ነው። ልጅ የአባቱን ቤት ዘርፎ ምርኮ ሲደረድር። የአዲስ አበባው የድህነት መንግስት ስንዴ ለውጭ ላኩ፤ ዝናብን በራሴ ጉልበት አዘነብኩ እያለ ዛሬ ቦረና ላይ እንስሳትና ሰዎች ሲያልቁ በሩቅ ማየቱ የመውደቂያ ጊዜውን እያፋጠነ እንድሆነ አሊ አይባልም። ሰው በግፍ ማማ ላይ የሚቆየው ለጥቂት ጊዜ ብቻ ነው። የረዘመ ቢመስልም ብዙው እንቅልፍ የማጣትና የሰቆቃ ነው። ለሰው ልጅ በአማካይ የ 70 ዓመት እድሜ መኖሪያና መጦሪያ የሚያስፈልገው ብዙ አይደለም። እምብርት እንደሌለው እንስሳ ከድሃና ከሃገር ላይ እየቀሙ መክበር በቃኝን አለማወቅ ነው። አሁን ያለ ልክ አፍቃሪ ወያኔ የሆነው ዶ/ር አብይ ጊዜና ሰአት ቢያገኝ ወያኔ እንደ ቄራ ከብት ጎትቶ እንደሚያርደው አይገባው ይሆን? ለወያኔ የወርቅ ምንጣፍ ቢነጠፍለት ከተንኮልና ከግድያ ባህሪያቱ አይለወጥም። አማራው በመንግስት ላይ እምነት ማድረጉን በመተው ለ 4ኛው ወረራ ከአሁኑ ዝግጅት ማድረግ አለበት። የምናየውና የምንሰማው ከኦሮሞ መሪዎችም ሆነ ከወያኔ ትራፊ ደም አፍሳሾች አሁንም ፉከራ ነው። ለኦሮሞውና ለወያኔ ጠባብ ብሄርተኞች ሁለት ጠላቶች አሏቸው። አማራና የኢትዮጵያ ተዋህዶ ቤ/ክ፤ አሁን ከሆነ ወዲህ ደግሞ ወያኔ ኤርትራንም ጨምሮ ሚሳየል እስከ መወንጨፍ ደርሷል። ሚሳኤል ወደ ኤርትራ የተኮሰውም እላዪ ላይ ሆነው በሚጋልቡት ታዞ ያለ ልቡ እንደሆነ በሶስተኛው ወረራው ታይቷል። አሁን ኢትዮጵያን ለማጥፋት ሽርክናው በኦሮሞና በወያኔ ጠባብ ብሄርተኞች ጥምረት የሚመራ ሆኗል። እልፍ ቶን እህልና ነዳጅ ወደ ትግራይ ከቢሊዪን ገንዘብ ጋር የብልጽግናው መንግስት ሲያጓጉዝ ከቀያቸው ተፈናቅለው በየታዛው የወደቁትን የአማራ፤ የኦሮሞና የደቡብ ህዝቦች ዞር ብሎ አላያቸውም። ደግሜ ደጋግሜ እንዳልኩት ወያኔ በህይወት እያለ ኢትዮጵያ ሰላም አትሆንም። ጠ/ሚ አብይም ወያኔን እንደ ደጀ ሰላም በየጊዜው መሳለሙ ለራሱም ሆነ ለሃገሪቱ ደህንነት አደገኛ ነው። እስቲ ንገሩን የታለ የደ/አፍሪቃውና የናይሮቢው ስምምነት ተግባር ላይ የዋለው? ያለስራ የቆሞ የሰሜን እዝ ታንክና መድፍ ማስረከቡ ፌዝ አይደለም? በሰው ህይወት ገበጣ መጫወት ግፍ ነው ዶ/ር አብይ ንቃ! ወያኔ ጊዜ እየገዛ አንዴ በኤርትራ ሰራዊት ሌላ ጊዜ በግዛት ይገባኛልና በአማራ የሚያሳብበው ለምን ይሆን? የጠ/ሚሩ ቆራጥና ቆፍጣና አመራር ማጣትና ሁሉን ላስደስት ማለት ገና ምድሪቱን የባሰ አዘቅት ውስጥ ይከታታል። ለገደለ፤ ሞት፤ ለዘረፈ፤ እስራት፤ ላፈናቀል ግርፋት የሚሰጥ እስኪመጣ ድረስ በዘር በተመነዘረ ፓለቲካ ሃገር ተሰርታ አትቆምም። ይህ አሁን በመጓጓዣ አውቶብሶች ላይ ዘረፋ ተፈጸመ የሚባለውም አባይን በጭልፋ እንዲሉ እንጂ ብዙ የቀጥታና የእጅ አዙር የግፍ ዘረፋዎች እየተፈጸሙ እንደሆነ በየስፍራው እንሰማለን። ወደፊትም ይቀጥላል ሌላው የተራበና ተረኛ የፓለቲካ ቡድን በጡጫ በማለት ያለውን ገፍትሮ በስፍራው እስኪሆን ድረስ ዓለም ትሽከረከራለች። ገፍታሪውን ሌላ ገፊ እየገፋው በውሸት ፓለቲካ ህዝባችን እየደለልን ዘመን አልፎ ዘመን ሲተካ ነጻነትን ሽተን እንሆ ዛሬም የአፓርታይድ ዘመን ላይ ደርሰናል። ለዚህ ነበር ከዘመናት በፊት ሃይለስላሴ ደስታ ” ኦ ሰላም በስምሽ ስንት ግፍ ተሰራ” በማለት እይታውን ያካፈለን። በአንደኛው የዓለም ጦርነት ከአንድ ሚሊዮን በላይ አርሜኒያን ሲጨፈጨፉ፤ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት 6 ሚሊዪን አይሁዶች ሲነድ ከሩቅና ከቅርብ ዝም ብሎ የተመለከቱት የያኔ መንግስታት ዛሬ በዪክሬንና በራሺያ በኩል ለሚደረገው ፊልሚያ እሳት አስነሽዎቹና ቆስቋሾቹ ራሳቸው ናቸው። ዓለማችን ጠኔና መከራ የማይለያት አንድ ጋ ጋብ ሲል ሌላ ጋ ሰው ለነፍሱ የሚሮጥባት ገዳዳና ፍርድ የለሽ ዓለም ናት። በሃበሻው ምድር የምናየውም እልፈት የሌለው ከረመጥ ወደ ከፋ እሳት እየገፉንና እኛም በውጭ ሃይሎችና በራሳችን የዘርና የቋንቋ ስካር ተይዘን ወንድምና እህታችን ገድለን የምንፎክርበት ዘመን ላይ እንገኛለን። ዝርፊያው፤ የፓለቲካ ሽኩቻው፤ ረሃቡና ጠኔው፤ እንባና ሰቆቃ ይቀጥላል። በቃኝ!

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • ወርቁ አይተነው የሸሹት ከዝርፊያ፣ ውንብድናና ዕዳ ጋር በተያያዘ ነው September 21, 2023 02:38 pm
  • ወደ አማራ ክልል ሊተላለፍ የነበረ መሣሪያና ሰነድ ተያዘ September 19, 2023 04:35 pm
  • በትግራይ መርዶ በይፋ ሊታወጅ ነው September 19, 2023 04:22 pm
  • ጃርቶች ለምን ይጮኻሉ? September 19, 2023 04:37 am
  • “ዐቢይ ግድቡን ሸጦታል” ጌታቸው ረዳ September 11, 2023 10:18 am
  • አቶ አገኘሁ መረጃ አሳልፎ በመስጠት ዋጋ እንደሚከፍሉ ተሰማ September 10, 2023 06:52 pm
  • ለዋዜማ ሬዲዮ “ኢትዮጵያን ቋሚ የውሀ ባለ እዳ” ያደርጋል ያላችሁት ረቂቅ ሰነድ የታለ? September 10, 2023 01:58 am
  • ወደር የሌለው የኅብረተሰባዊት ኢትዮጵያ ጀግና! ብርጋዴር ጄኔራል ተስፋዬ ኃብተማርያም September 8, 2023 02:31 pm
  • የትግራይ መፍረስ በርዕሰ መስተዳደሩ አንደበት September 8, 2023 02:49 am
  • ከያቤሎ አዲስ አበባ የተላከ ኮንትሮባንድ ጉለሌ ተያዘ September 7, 2023 01:40 pm
  • “እንኳን ተለያይተንና እርስ በርስ ተባልተን በአንድነት ቆመንም ወጀቡን መሻገር አቅቶናል” September 7, 2023 01:31 am
  • ራሱን መሪ አልባ የሚያደርገው አማራ ክልል August 24, 2023 11:50 pm
  • ጀብደኛው August 24, 2023 10:06 am
  • ጎንደርና ባሕር ዳር ከተሞች ወደ ቀድሞ ሰላማቸው ተመልሰዋል August 13, 2023 10:55 pm
  • ኢትዮጵያ በታሪኳ የመጀመሪያውን ግዙፍ ወታደራዊ ኃይል አስመረቀች August 13, 2023 10:26 pm
  • ሪፖርተር የፓርላማ ወንበር አስልቶ የአስቸኳይ አዋጁ በፓርላማ እንዳይደገፍ አቅጣጫ አመላከተ August 13, 2023 09:11 pm
  • ወደ ኤርትራ በኮንትሮባንድ የሚሻገሩ ቆሳቁሶች እየተያዙ ነው August 11, 2023 12:52 pm
  • የአማራ ክልል ትልልቅ ከተሞች ተኩስ ዓልባ ሆነው ውለዋል August 10, 2023 04:31 pm
  • “አንድ ሰው ለመግደል ኅንፃውን ማቃጠል” የኢ-ዲሞክራሲና ጽንፈኛ ኃይሎች ቅዠት፤ (ክፍል ሁለት) August 10, 2023 09:44 am
  • “አርበኛ” መሳይ – “የድል ዜና” ሳይበርድ 50ሺህ ዶላር በጎፈንድሚ August 10, 2023 09:08 am
  • በሕዝቡ ድጋፍ ከተሞች ከዘራፊው መንጋ ሥጋት ነጻ መሆናቸው ይፋ ሆነ August 9, 2023 11:47 am
  • ትህነግ አራተኛውን ሞት ሞተ  August 8, 2023 05:47 pm
  • “ሃሳብ ሲነጥፍ ነፍጥ አንግቤ እዋጋለሁ” የሚሉ አካላት ላይ እርምጃ ይወሰዳል – የመከላከያ ሠራዊት August 1, 2023 09:25 am
  • ደቡብ አፍሪካ የመሸጉ ወንጀለኞች ለሕግ ተላልፈው ሊሰጡ ነው July 31, 2023 09:27 am

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2023 · Goolgule