
መስከረም 23 እና 24 የሚከበረውን የኢሬቻ በአል ለመበጥበጥ የተዘጋጁ 503 ሰዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ፡፡ መሳሪያም ተገኝቶባቸዋል።
የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ጄኔራል ኮማንደር አራርሳ መርዳሳ ትላንት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንደገለፁት፤ የኢሬቻ በዓል ላይ የሚሳተፉ የበዓሉ ታዳሚዎች በሰላም ወጥተው እንዲገቡ ኮሚሽኑ በጥብቅ እየሰራ ነው።
የግል ፍላጎታቸውን ለማሳካት በተለያየ አቅጣጫ እየተንቀሳቀሱ ያሉ ሀይሎች እንዳሉና ኮሚሽኑም እንደደረሰባቸው የገለፁት ኮማንደሩ፤ እስካሁን ድረስ 503 ሰዎች፣14 ክላሽ ፣ 26 ቦምብ እና 103 ሽጉጦች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ተናግረዋል፡፡
ከኦሮሚያ ኮሙኒኬሽን ቢሮ ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው የኢሬቻ በዓል በኮረና ምክንያት እንደ ከዚህ ቀደሙ በርከት ባለ ሰው የማይከበር ሲሆን በገዳ አባቶች የተላለፈውን ውሳኔን ህብረተሰቡ ስራ ላይ ማዋል እንዳለበትም ጄኔራል ኮማንደር አራርሳ ተናግረዋል፡፡
ህብረተሰቡ ከፀጥታ ሀይሉ ጋር በመሆን ከህወሓት እና ከሸኔ የተሰጣቸውን ግዳጅ በመውሰድና ኦሮሚያን የጦርነት አውድማ ለማድረግ እየተንቀሳቀሱ ያሉ ሀይሎችን በማጋለጥ በዓሉ በሰላም እንዲጠናቀቅ የበኩላቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
የስልጣን ጥም ያላቸው አካላት “ከመስከረም 25 በኋላ መንግስት የለም” እያሉ ህብረተሰቡን ለማወክ የሚፈልጉ አካላት በምንም ሁኔታ እንደማይሳካላቸው ጄኔራል ኮማንደር አራርሳ ተናግረዋል፡፡
የኦሮሚያ ፖሊስ የህዝቡን ሰላም የሚያውኩትን በመከታተል ህግ ለማስከበር በቁርጠኝነት መዘጋጀቱንም ኮማንደሩ ማስታወቃቸውን ፕሬስ ድርጅት ዘግቧል፡፡
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply