
* በዕለቱ ቀሲስ ታጋይ ታደለ፣ ፓስተር ታደሰ አዱኛ እና የአካባቢው የሞርሞን ተወካይ ተገኝተዋል
* “የኦርቶዶክሳውያን ዕንባ ታብሷል” ቀሲስ ታጋይ
ላለፉት ዘጠኝ ዓመታት የማምለኪያ ቦታ በማጣት በብዙ ችግር ውስጥ የነበሩት የዩታ ጠቅላይ ግዛት ኪዳነ ምህረት ቅድስት ማርያም ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን አባላት ከሞርሞን ቤ/ክ በተደረገላቸው የሕንጻ ሥጦታና ድጋፍ ቅዳሜ ሰኔ 21 ቀን 2017 ዓም (ጁን 28፣ 2025) ቋሚ የማምለኪያ ሥፍራ ማግኘታቸው ታወቀ።
በቤተክርስቲያኑ ምረቃ ሥነስርዓት ላይ የኢትዮጵያ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ጠቅላይ ፀሐፊ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ታጋይ ታደለ፤ ከሞርሞን ቤ/ክ (ኃላፊውን በመወከል) ኤልደር ፔፐር መሪ እንዲሁም የኢትዮጵያ ዩኒየን ሚሲዮን ፕሬዚዳንት ፓስተር ታደሰ አዱኛ እና ሌሎችም ተገኝተዋል (ቪዲዮውን እዚህ ላይ መመልከት ይቻላል)።
በምረቃው ወቅት የዩታ ኪዳነምህረት ቅድስት ማርያም ቤ/ክ ኃላፊ አባ ፍሰሐጽዮን ሲናገሩ ምዕመኑ ተጨናንቆ ባንዲት ትንሽ ክፍል ውስጥ ያመልክ እንደነበር ጠቅሰው አሁን ግን “ይህንን በማየት የደስታ ዕንባ አነባለሁ” በማለት ደስታቸውን ገልጸዋል።
የዛሬ አራት ዓመት አካባቢ የኦርቶዶክሳውያኑን ችግር በመመልከት ቀሲስ ታጋይ ለሞርሞኑ ኤልደር ሮናልድ ራስባንድ (Ronald A. Rasband) መፍትሔ እንዲፈልጉላቸው መናገራቸውን የኪዳነምህረት ቤ/ክ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ሚካኤል ማሞ በዕለቱ አስታውሰዋል። ኤልደር ሮናልድ በተለምዶ ሞርሞን ቤ/ክ ወይም በኦፊሻል አጠራሩ የኋለኛው ዘመን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱሳን ቤ/ክ (The Church of Jesus Christ of Latter-day Saints) በሚባለው የ12ቱ ሐዋርያት አመራር (የ12ቱ ሐዋርያት ኮረም – Quorum of the Twelve Apostles) አንዱ ናቸው።
በሞርሞን ቤ/ክ የ12ቱ ሐዋርያት አመራር የሚባለው አካል ከፕሬዚዳንታዊው ኮረም ቀጥሎ ያለ የቤ/ክኑ ከፍተኛ የአመራር ሥልጣን ነው። የኮረሙ አባላት 12 ወንዶች ሲሆኑ እነዚህም ሐዋርያት ተብለው እንደሚጠሩ የቤ/ክኑ ድረገጽ ይናገራል። ከዚህ በተጨማሪም “ሐዋርያ” ተብሎ በዚህ ኮረም የሚካተት ማንኛውም ሰው “ነቢይ፣ ተመልካች እና ባለራዕይ” ተብሎ የሚጠራ ሲሆን ኤልደር ሮናልድ ራስባንድም በዚሁ ማዕረግ እንደሚጠሩ ገለታሪካቸው ይናገራል።
ቀሲስ ታጋይ ከኤልደር ሮናልድ ጋር ይህንን ንግግር ካደረጉ በኋላ የሞርሞን ቤ/ክ ለኦርቶዶክስ አማኒያን የማምለኪያ ሥፍራ ማፈላለጉን ጀመረ። በመቀጠልም ከዚህ በፊት የሞርሞን ቤ/ክ ለመጋዘንነት ወይም ዕቃ ማከማቻ ይጠቀምበት የነበረውን ሁለት ተለቅ ያሉ ሕንጻዎች ለኪዳነምሕረት በመስጠት የማደስ ሥራው ተጀመረ።
ላለፉት አራት ዓመታት ከኪዳነምሕረት፣ ከሞርሞን ቤ/ክ፣ ከስተርሊንግ ፋውንዴሽን (Stirling Foundation) እና ከሌሎችም በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ ሁለቱም ሕንጻዎች ታድሰው አንዱ ለማምለኪያ ሥፍራነት፤ ሌላኛው ደግሞ ለወጥቤት፣ ለመጸዳጃ ቤትና ለካህናት መኖሪያ እንዲያገለግል በጥሩ ሁኔታ ታድሰው ቅዳሜ በተደረገው የምረቃ መርሃግብር ተመርቋል።
ቅዳሜ በተደረገው የምረቃ ፕሮግራም ላይ የስተርሊንግ ፋውንዴሽንን በመወከል የተገኙት የተቋሙ ምክትል ፕሬዚዳንት ኒኮል ስተርሊንግ ሲናገሩ፤ “ይህ ሕንጻ በሃይማኖቶች መካከል በሚደረግ ጥረትና ትብብር ምን ማድረግ እንደሚቻል በቀዳሚነት አመልካች ሆኖ የሚታይ ነው። ሰዎች እግዚአብሔርን ለማምለክ ይችሉ ዘንድ ሁሉም ወደጌታ በጋራ ሲያለቅስ፣ ሲጮህ የሚመጣውን ውጤት የሚያሳይ ነው” ብለዋል።
ከሞርሞን ቤ/ክ ጋር በቅርብ የሚሠራው ስተርሊንግ ፋውንዴሽን በበርካታ የምግባረ ሰናይ አገልግሎቶች ላይ በዓለም ዙሪያ የተሰማራ ሲሆን ከነዚህም መካከል፤ የማኅበረሰብ ልማት፣ የትምህርት፣ የአስቸኳይ ጊዜ ድጋፍ፣ የጤና፣ ስደተኞችን መልሶ የማቋቋም፣ ወዘተ አገልግሎቶችን የሚሰጥ ሲሆን ከዚሁ ጋር የሃይማኖት መቻቻል እና በሃይማኖቶች መካከል መግባባትና መተባበር እንዲኖር የሚሠራ ትርፍ ዓልባ ተቋም እንደሆነ ድረገጹ ይጠቁማል።
ቅዳሜ ሰኔ 21 (ጁን 28) በኪዳነምህረት ቤ/ክ በተካሄደው የምረቃ ሥነስርዓት በክብር ዕንግድነት የተገኙት ፓስተር ታደሰ አዱኛ የሃይኖቶች መተባበር ለሰላም አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል። ፓስተር ታደሰን ጠቅሶ ዴዘርት ኒውስ (Deseret News) የተባለው ሚዲያ እንደዘገበው በዓለም የሚገኙ ሃይማኖቶች ሁሉ አንዱ ኃላፊነታቸው እርስበርሳቸው ሰላም እንዲሰፍን ማበረታታት መሆኑን ፓስተር ታደሰ መናገራቸውን ዘግቧል። ፓስተሩ ሲቀጥሉም፤ “እርስበርስ መረዳዳት አለብን፤ ምክንያቱም ኢየሱስ የኖረው ለራሱ ሳይሆን ለሌሎች ነው፤ ክርስትናም ማለት ይኸው ነው፤ እርስበርስ መረዳዳት ነው፤ ስለዚህ የሌሎች ሰዎች ሕይወት እንዲሻሻል መሥራት አለብን” ብለዋል። “ይህ ማለት” አሉ ፓስተሩ፤ “ዓላማው ሰላም ለመፍጠርና (ሰዎችን) ከፍ ለማድረግ ነው እንጂ ሰዎችን (ሃይማኖታቸውን) ለማስለወጥ ወይም አስተሳሰባቸውን ለማስቀየር አይደለም” ብለው ለሚዲያው መናገራቸውን ድረገጹ ዘግቧል።
ኤልደር ሮናልድ ራስባንድን በመወከል ከሞርሞን ቤ/ክ የተናገሩ ኤልደር ፔፐር መሪ (Elder Pepper Murray) ሲሆኑ እርሳቸውም በፓስተር ታደሰ የንግግር ቃላት ላይ አጽንዖት በመስጠት ዋናው ትኩረት መሆን የሚገባው “የዶክትሪን የአስተምህሮ ልዩነት” ላይ መሆን እንደሌለበት ከዚያ ይልቅ ግን “የወዳጅነትን ድልድዮችን በመገንባትና በመግባባት ላይ መሆን እንዳለበት” ለዴዘርት ኒውስ ተናግረዋል።
ኤልደር ፔፐር ሲቀጥሉም “በዓለማችን ላይ የሃይማኖት ነጻነት ከዕለት ወደ ዕለት አደጋ ላይ እየወደቀ ባለበት ባሁኑ ወቅት ወዳጅነትንና ቁርኝትን በማጠናከር እና ድልድዮችን በመገንባት ላይ መሥራት ነው የሚያስፈልገን” ብለዋል። “እንደዚህ ያለውን ጉባዔ ማጠናከር ሁላችንንም ያጠናክረናል፤ ማኅበረሰብ ሲጠናከር እኛን የተሻልን፤ ማኅበረሰቡን ደግሞ የተጠናከረ እንዲሆን ያደርጋል፤ ስለዚህ በተናጠል ወይም በፍላጎት ተለያይተን ከምናደርገው ይልቅ በትብብር በጣም የተሻለ ማድረግ ይቻላል” ብለዋል።
በአሜሪካ የምረቃ ሥነስርዓቱ ሲካሄድ በአዲስ አበባም የሞርሞን ቤ/ክ አባላትና ወዳጆች በቀጥታ ሥርጭት መርሃግብሩን ተከታትለዋል። ወደ አርባ የሚጠጉ በተካፈሉበት የሆቴል አዳራሽ የተገኙት የሞርሞን ኢትዮጵያ ሚሲዮን ኃላፊ ኦሊቫ ኮውሊ (Oliva Cowley) “እንዲህ ዓይነቱ ኩነት ሃይማኖትን ወይም ዘርን ወይም እምነትን ሳይነኩ እርስበርስ መደጋገፍን የሚያደፋፍር ነው” ብለዋል። አበባ ብርሃኔ የተባሉ በአዳራሹ የተገኙ የኦርቶዶክስ ቤ/ክ አባል ደግሞ “ኤልደር ሮናልድ ራስባንድ ቤ/ክኗ ቦታ እንድታገኝ የቤተክርስቲያኗ አባላት ደግሞ ሕንጻውን በማደስ በመተባበራቸው ደስ ብሎኛል” ብለዋል። “በብዙ ኪሎሜትሮች ቢራራቁም የሁለቱም ቤተክርስቲያናት መሪዎች መተባበር መቻላቸውና ይህንን ማድረጋቸው ልቤን ነክቶኛል” ማለታቸውን የሞርሞን ቤ/ክ ድረገጽ ዘግቧል።
በሞርሞን ቤ/ክ እና በኦርቶዶክስ ቤ/ክ መካከል በተገነባው ድልድይ ምክንያት ሁለቱን ሃይማኖቶች ከሚያለያይዋቸው ይልቅ የጋራ የሆኑ ነገሮች እንዳሉ አባ ፍሰሐጽዮንም ተናግረዋል። ዴዘርት ኒውስ እንደዘገበው አባ ፍሰሐጽዮን የሞርሞን ቤ/ክ የግማሽ ዓመት ጉባዔ ሁለት ጊዜ የተሳተፉ ሲሆን የቤ/ክኑ መዘምራን የሚያቀርቡትን መዝሙርም መከታተላቸውን፣ ከሚሲዮናውያኑም ጋር መገናኘታቸውን እንዲሁም ከቤ/ክኑ አመራሮች ጋር የቀረበ ግንኙነት እንዳላቸው ታውቋል።
ኢትዮጵያውያን በአሜሪካ የዩታ ጠቅላይ ግዛት እንክብካቤ እንደሚደረግላቸው ሁሉ የሞርሞን ቤ/ክ አባላትም በኢትዮጵያ ተመሳሳይ እንዲደረግላቸው በወቅቱ ተነስቷል።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply