
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የቀድሞ ጭፍራቸውን ገዱ አንዳርጋቸው በፓርላማ በስም ጠርተው ለተናገሩት ገዱ መልስ ሰጥተዋል።
ይህ ጽሑፍ ዓላማ ያደረገው ለገዱ ምላሽ አስተያየት ለመስጠት አይደለም። ምክንያቱም የመጀመሪያና ትልቁ ስህተት ያለው ገዱ በጻፉት የመጀመሪያው አንቀጽ ላይ ስለሆነ ነው። ያ ሳይስተካከል በገዱ ጽሑፍ ላይ ምንም ማለት አይቻልም። ገዱ የጠቅላዩን ንግግር የሰሙት እንዴት እንደሆነ ሲገልጹ “ሰዎች ቆርጠው በላኩልኝ የቪዲዮ ቅጂ” ነው ብለዋል።
ገዱ የግል ታሪካቸው እንደሚያስረዳው “መጀመሪያ ዲግሪ” የያዙት በተለምዶ “የዲግሪ ወፍጮ” ወይም “ድንጋይ ማምረቻ” ከሚባለው ሲቪል ሰርቪስ “ዩኒቨርሲቲ” ነው። ሲቀጥል “ማስተርስ ዲግሪ” ከአዙዛ ነው። መቼም ስለ አዙዛ መናገር እዚህ ላይ አያስፈልግም። ግልጽ መሆን ያለበት ጉዳይ ግን ከሲቪል ሰርቪስም ሆነ ከአዙዛ የተመረቀ ሁሉ ጭንቅላቱ ገዳዳ ነው ለማለትም አይደለም።
ዩኒቨርሲቲ የገባ ሰው አንድ በመሠረታዊነት የሚማረው፤ የምርምር ጽሑፍ አጻጻፍና አጠቃቀስ ነው። በአግባቡ አለመጥቀስም ሆነ አለመጻፍ ያስቀጣል፤ “የጽሑፍ ሌባ” ተብሎ ሊያስባርርም ይችላል። በተለይ ደግሞ በአንድ ጽሑፍ ላይ የሚሰጥ ትችት ሲሆን በቅድሚያ ሙሉውን ማንበብ የሚጠይቅ ነው። በዚህ መልኩ የማይጽፍ ተማሪ አስተያየቱ የተንጋደደ ስለሆነ ዋጋ ቢስ ነው።
ገዱ የጠቅላዩን ቪዲዮ የተቆረጠውን ነው ያዩት፤ ያውም ሰዎች ቆርጠው የላኩትን። ከየት እንደተቆረጠ፣ ምን ያህል ተቆርጦ እንደተላከላቸው፤ ምናልባትም በሰው ሠራሽ አስተውሎ (AI) ተስተካክሎ የተላከላቸው ይሁን ምንም የሚታወቅ ነገር የለም። ሰሞኑን አሜሪካ በረዶ ወረደ ሲባል ሕንድ ያሉ ወጣቶች በኤአይ በሠሩት ቪዲዮ ላይ ግድግንድ የበረዶ ኳስ በመኪና እና በቤቶች ላይ እየነጠረ ሲወርድ ይታይ ነበር፤ በረዶ ሲነጥር አይገርምም?!
ገዱ በምላሻቸው መጀመሪያ ላይ ነው ምላሻቸው የተንጋደደው፤ ያንን ያነበበ ሰው ደግሞ ለቀሪው ትንታኔያቸው ምላሽ ለመስጠት ብዙ ይቸገራል። ምክንያቱም ሙሉውን ባላዩት ቪዲዮ ምናልባትም እውነተኛ ባልሆነ ቪዲዮ ላይ ነው አስተያየት የሰጡት። ስለዚህ ምላሻቸው ገዳዳ ነው።
የገዱ ምላሽ ለምን ተንጋደደ? የቀድሞው የኢህአዴግ ካድሬ ኤርሚያስ ለገሠ አብዛኛዎቹን ካድሬዎች እሱ እንዳሰለጠናቸው በተደጋጋሚ ሲናገር ተሰምቷል። በሌላ አነጋገር የዲግሪ ቆብ የጫነላቸው ኤርሚያስ ነው። ያኔ ስለ ምርምር ጽሑፍ አጻጻፍ ወይ እነ ገዱን አላስተማራቸውም፤ ወይም ገዱ የብአዴን ስብሰባ ኖሮባቸው ያንን ክላስ ፎርፈው ነበር።
ምክር፤ ገዱ አሜሪካ ያውም ኤርሚያስ በቅርብ በሚገኝበት አካባቢ ስለሆነ ያሉት “ያቺን ያኔ ያመለጠችኝን ትምህርት እስቲ እዚህ በዙም ወይም በቴሌግራም ድገምልኝ” ይበሉት። ከዚያ “በምንባቡ መሠረት” እንደሚባለው በተማሩት መሠረት ለጠቅላዩ አዲስ ምላሽ ይጻፉ።
መቋጫ፤ ኤርሚያስ የቀድሞ ካድሬዎችን ጠንቅቆ ነው የሚያውቃቸው። ዐቢይ ፓርላማ ላይ ስለ ገዱ ከተናገሩ በኋላ፤ ኤርሚያስ ለገዱ ምክር ሰጥቶ ነበር፤ “እኔ ገዱን ብሆን ምላሽ አልሰጥም” ነበር ያለው። ገዱ የዚያን ቀን ያቺን ክላስ መፎረፋቸውን አስታውሶ ይሆን?
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ


Leave a Reply