
የሰሜን ምዕራብ ዕዝ ኮሙኒኬሽንና ኤሌክትሮኒክስ ሳይበር መምሪያ በኅልውና ዘመቻ እና በዘመቻ ለሕብረብሔራዊ አንድነት የግዳጅ ወቅት ከፍተኛ ጀግንነት ለፈጸሙ የመምሪያው አባላት የዕውቅናና የምስጋና መርኃግብር አካሂዷል።
በመርኃግብሩ ላይ በመገኘት ሽልማቱን የሰጡት የሰሜን ምዕራብ ዕዝ ምክትል አዛዥ ሜጀር ጀኔራል ሙሉዓለም አድማሱ እንደተናገሩት አሸባሪው የትህነግ ቡድን በሰሜን ዕዝ ላይ ጥቃት ከፈፀመበት ጊዜ ጀምሮ የሰሜን ምዕራብ ዕዝ ኮሙኒኬሽንና ኤሌክትሮኒክስ ሳይበር መምሪያ ሀገርን ከውድቀት ለመታደግ ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል።
መምሪያው በቀጣይ የሚሰጠውን ሀገራዊ ግዳጅ በጀግንነት ለመወጣት ይበልጥ ዝግጁ መኾን እንደሚገባውም ምክትል አዛዡ አሳስበዋል።
የዕዙ ኮሙኒኬሽንና ኤሌክትሮኒክስ ሳይበር መምሪያ ኀላፊ ኮሎኔል ወርቅነህ ነዳሳ በበኩላቸው ክፍሉ በግዳጅ አፈጻጸም ወቅት የሠራዊቱ የጀርባ አጥንት በመኾን በርካታ አኩሪ ተግባራትን ፈጽሟል ነው ያሉት። በዚህም አዳዲስ ሞያተኞችን ከነባር የመገናኛ ባለሞያዎች ጋር በማቀናጀት ዘርፈ ብዙ ሥራዎች መከናወኑን ገልጸዋል።
የሰሜን ምዕራብ ዕዝ ኮሙኒኬሽንና ኤሌክትሮኒክስ ሳይበር መምሪያ በጦርነቶች ከፍተኛ ልምድ ያካበተ እንደመኾኑ መጠን በዕውቀት እና ቁሳቁስ የሰው ኀይሉን በመገንባት ግዳጅ የመፈጸም አቅሙን አስተማማኝ ደረጃ ላይ ማድረስ መቻሉን ተናግረዋል።
ሽልማት ከተበረከተላቸው የመምሪያው አባላት መካከል ሻምበል ዝናቡ በቀለ በአሸባሪው ትህነግ ተበጣጥሶ የነበረውን የግንኙነት መስመር በራሱ ጥረት ቀጥታ አዲስ አበባ ካለው የጦር ክፍል ጋር ግንኙነት የመሰረተ ጓድ በመኾኑ የ1ኛ ደረጃ ሜዳይ ተሸላሚ ኾኗል።
ሌላኛዋ ተሸላሚ አስር አለቃ አገሬ ያለው የዳታ እና ግንኙነት ባለሙያ ናት። የተሰጣትን ኀላፊነት በአስተማማኝ ብቃት የተወጣች በመኾኗ የ3ኛ ደረጃ ሜዳይ ተሸላሚ ለመኾን ችላለች።
በዕውቅናና የምስጋና መርኃግብሩ ሌሎች ተሸላሚ አባላቶችም የተካተቱ ሲኾን በቀጣይም የኢትዮጵያን ኅልውና ከሚፈታተንና ከሚቃጣ ማንኛውም አደጋ ሀገራቸውን ለመታደግ ቁርጠኛ እንደኾኑ መግለጻቸውን ከመከላከያ ሠራዊት የተገኘ መረጃ ያመላክታል።
በሌላ በኩል የአማራ ልዩ ኀይል ተከዜ ክፍለ ጦር አሸባሪውን የትግራይ ወራሪ ቡድን በመደምሰስ ኢትዮጵያን ለማዳን በተደረገው ትግል የላቀ አፈጻጸም ላስመዘገቡ አመራሮች እና አባላቱ የእውቅናና የማዕረግና እድገት ሽልማት ሥነ ሥርዓት አካሂዷል።
በሥነ ሥርዓቱ የሀገር መከላከያ ሠራዊት ከፍተኛ የሥራ ኀላፊዎች፣የአማራ ልዩ ኀይል ረዳት ኮሚሽነርና የክፍለጦሩ አዛዥ፣የሰሜን ጎንደር ዞን ከፍተኛ የሥራ ኀላፊዎች፣የሃይማኖት አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎች ተገኝተዋል።
በመድረኩ የተከዜ ክፈለ ጦር አዛዥ ኮረኔል አብጀው ተፈራ አሸባሪው የትግራይ ወራሪ ቡድን የአማራን ሕዝብ ለማጥፋት የከፈተውን ጦርነት ለመመከትና የአማራን ሕዝብ ከጥፋት፣ ኢትዮጵያን ከመፍረስ ለመታደግ በተደረገው ተጋድሎ ተከዜ ክፍለ ጦር ከሌሎች አሃዶች፣ ክፍለ ጦሮችና ከመላው የጸጥታ ኀይል ጋር በመጣመር ትልቅ ታሪክ ሠርቷል ብለዋል።

ክፍለ ጦሩ በተሰለፈባቸው አውደ ውጊያዎች ኹሉ ትልልቅ ጀብዱዎችን እየፈጸመ የዘለቀ ነው ያሉት አዛዡ በክፍለ ጦሩ ውስጥ የላቀ ጀብዱ ለፈጸሙ አመራሮችና አባላት የማበረታቻ ኒሻን ሽልማት ተሰጥቷቸዋል ብለዋል። የተሰጣቸው ሽልማትም በቀጣይ ለሚኖረው ተልዕኮ በሞራል ዝግጁ እንዲኾኑ ያደርጋቸዋል ነው ያሉት።
ለአባላቱ የእውቅናና የማዕረግ እድገት ሽልማቱን ያበረከቱት የአማራ ልዩ ኀይል ረዳት ኮሚሽነር አዳነ አስማረ ማዕረጉ በብዙ ውጣውረድና ከፍተኛ መሥዋእትነት የተገኘ ነው ብለዋል።
“መንግሥት እውቅናና ሽልማቱን የሰጠው አሸባሪው የትግራይ ወራሪ ቡድን የአማራን ሕዝብ ለማንበርከክ ለዳግም ወረራ እየተዘጋጀ መኾኑን ተገንዝባችሁ ሊመጣ የሚችለውን ወረራ ለመቀልበስ ዝግጁ እንድትኾኑ አደራ እየሰጣችሁ ነው” ብለዋል ለልዩ ኀይል አባላቱ።

ሽልማት ከተበረከተላቸው የክፍለ ጦሩ አባላት መካከል ኢኒስፔክተር ፍትህአለው ሙሉ በፈጸሙት ጀብዱ በዕለቱ የሻለቃነት ማዕረግ አግኝተዋል።
ሻለቃ ፍትህአለው ‟በብዙ ጓዶች መሥዋእትነት እዚህ መድረሴን ባልዘነጋም በሽልማቱ ደስተኛ ነኝ” ብለዋል።
በቡያ፣ጠለምት፣አድርቃይ፣ብርብራ፣ቦዛ፣ብና ሜዳና ሌሎች አውደውጊያዎች ላይ እንደተሳተፉ ያነሱት ተሸላሚው በቀጣይ ለሚኖረው ማንኛውም ግዳጅ ሽልማቱ መነሳሳትን እንደፈጠረላቸውና ዝግጁ መኾናቸውን አረጋግጠዋል።
ሌላኛው ተሸላሚ ኢንስፔክተር ጀጀው ፈረደ አሸባሪው የትግራይ ወራሪ ኀይልን ለመደምሰስ በተደረገው ተጋድሎ የአማራ ልዩ ኀይል ከጀግናው የሀገር መከላከያ ሠራዊት ጋር ተጣምሮ በርካታ ጀብዱውችን ፈጽሟል ብለዋል።በዚህ ውስጥም ተከዜ ክፍለ ጦር ሚናው ከፍተኛ ነበር ነው ያሉት።
ሽልማቱ በብዙ ጀግኖች መሥዋእትነት የተገኘ መኾኑን እረዳለኹ የሚሉት ተሸላሚው ‟የተሰውትን ጀግኖች ቃል ጠብቀን በቀጣይ ለሚኖር ግዳጅ ከፍተኛ መነሳሳትን ፈጥሮልናል” ነው ያሉት።
ክፍለ ጠሩ አሸባሪው የትግራይን ወራሪ ቡድንን ለመደምሰስ ባደረገው ተጋድሎ ከጸጥታ ኀይሉ ጎን ተሰልፎ በስንቅ፣በውጊያና በሞራል ድጋፍ ላደረገው የሰሜን ጎንደር ሕዝብ፣ለፋኖ አባላትና ለሌሎች ግለሰቦች የእውቅና ወረቀት ሽልማት አበርክቷል። (አሚኮ)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply