
የአማራ ክልል ፕላንና ልማት ቢሮ እየተካሄደ የሚገኘውን ጥናት አስመልክቶ መግለጫ ሰጥቷል። መግለጫውን የሰጡት የአማራ ክልል ፕላንና ልማት ቢሮ ኀላፊ አንሙት በለጠ አሸባሪው የትግራይ ወራሪ ቡድን በአማራ ክልል መጠነ ሠፊ የሰብዓዊ ጥሰት፣ የንብረት ዘረፋና ውድመት ፈጽሟል ብለዋል።
በሽብር ቡድኑ ምክንያት የደረሰውን አጠቃላይ ውድመት ሳይንሳዊ በሆነ መልኩ እየተጠና እንደሆነ አቶ አንሙት አስረድተዋል። በጥናቱ መሠረት ትክክለኛ ውድመቱ እንደሚገለጽ ነው የተናገሩት። ጥናቱ በጎደለው ልክ ለመሙላት አጋዥ እንደሚሆንም ጠቁመዋል።
ከጥናቱ በኋላ የወደሙ መሰረተ ልማቶች ተመልሰው በሚገነቡበት ሁኔታ ላይም ስትራቴጂክ እቅድ እየተዘጋጀ እንደሆነ አመላክተዋል። አቶ አንሙት እንደተናገሩት የጥናቱ ዓላማ ቡድኑ ያደረሰውን ውድመት ትክክለኛ መረጃን መስጠትና በሰነድ ማስቀመጥ፣ የሽብር ቡድኑ ተጠያቂ እንዲሆን ማድረግና ለመልሶ ጥገናው ሁኔታዎችን ማመቻቸት ነው።
በተለይ ዲያስፖራው በሚደረገው የመሰረተ ልማት መልሶ ጥገና ላይ ድጋፍ እንዲያደርግ፣ የጉዳቱን መጠን በሄደበት ቦታ ሁሉ እንዲያጋልጥ ከፍተኛ ኀላፊነት ይጠበቅበታል ብለዋል። ዲያስፖራው ረጂ ድርጅቶች በቀጥታ ድጋፍ እንዲያደርጉ የማስተባበር ተግባር እንደሚጠበቅበትም አስገንዝበዋል።
ዲያስፖራው የተለያዩ የኢንቨስትመንት አማራጮችን በመጠቀም እራሱንና የተጎዳውን ክልል ማሳደግ ይጠበቅበታል ነው ያሉት። ለዚህም የተለያዩ የልማት አማራጮች ለዲያስፖራው እየተዘጋጀ መሆኑን ኀላፊው ገልጸዋል። ከክልል ጀምሮ እስከ ወረዳ ድረስ ከ15 መሥሪያቤቶች ከየዘርፉ የተውጣጡ ባለሙያዎች በጥናቱ መሳተፋቸውንም ኀላፊው አስረድተዋል።
ከክልሉ መንግሥት እውቅናና ፈቃድ ውጭ ማንኛውም አካል ጥናት ማድረግ እንደማይችል አቶ አንሙት አሳስበዋል። ጥናቱ በቅርቡ ይፋ እንደሚሆንም ገልጸዋል።
ለጥናቱ ስኬታማነት ሁሉም ኅብረተሰብ ተባባሪ እንዲሆን ኀላፊው ጥሪ አድርገዋል። (አሚኮ)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply