
የወልቃይት መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴዎች እና የዋልድባ መነኮሳትን ጨምሮ ከመቶ በላይ ከእስር ቤት የተለቀቁ የዴሞክራሲና የፍትህ ተቆርቋሪ ታጋዮች በታሪካዊቷ ጎንደር ከተማ ግንቦት 2 ቀን 2010 ዓ.ም በተደረገላቸው የክብር ራት ግብዣ ላይ የተገኘው ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ ለታዳሚው ያደረገውን ንግግር ከተመስገን ባገኘነው ፈቃድ መሠረት ለጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ አንባቢያን እንደወረደ በሚከተለው መንገድ አቅርበነዋል። በዕለቱም ለህሊና እስረኞች የተለያየ ስጦታም እንደተበረከተ ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል።
እዚህ የተሰበሰባችሁ ታላላቆቼም፣ ታናናሾቼም በመጀመሪያ እንኳን ለዚህ ዕለት አበቃችሁ፤ አበቃን። በተለይም ባለፉት ሁለት አስርታት የወልቃይትን ሕዝብ የማንነት፣ የፍትሕ፣ የዴሞክራሲ እና የፖለቲካ ጥያቄ አደባባይ እንዲወጣ በተወለዳችሁበት አፈር ላይ ተተክላችሁ ለከፈላችሁት ውድ ዋጋ ጥልቅ አክብሮቴን ለመግለጽ እፈልጋለሁ። ከዚህ በኋላም ለሚመጡ ተጋፋጮች እናንተ መልካም ምሳሌ ናችሁና። እንደ ጋሽ ሲሳይ ታከለ እና ጎቤ መልኬ (ዋዋ) የመሳሰሉ ሰማዕታትንም ታሪክ ለዝንተ ዓለም እንደሚዘክራችሁ አምናለሁ። በተጨማሪም፤ የጎንደር እናቶች የደርግ የቀይ ሽብር ጭፍጨፋ ያሳረፈባቸው መጥፎ ጠባሳ ሳይበግራቸው፤ ከአርባ ዓመታት በኋላ በጃን ተከል ዋርካ ሥር የተሰባሰቡ የሕዝባዊ እምቢተኝነት አራማጆችን፣ የውሃ ጥም ለማርካት ከእንስራዎቻቸው ቀድተው በማጠጣት አጋርነታቸውን ያስመሰከሩበትን ላቅ ያለ አበርክቶት እስር ቤት ሆኜ ስሰማ ያሳደረብኝን ሐሴት ቃላት አይገልጸውም። በትግሉ ተዋፅዎም የሴቶች ተሳትፎ አናሳ በሆነበት አውድ የእነዚህ እናቶችና ለዕድሜ አቻዎቿ ዓርአያ መሆን የቻለችው የንግሥት ይርጋ ጀግንነትም ከፍ ያለ ዋጋ እንዳለው አይካድም። ጎንደርም ከመካከለኛው ዘመን የስልጣኔ እምብርትነት በዘለለ፣ የ21ኛው ክፍለ-ዘመን የፀረ-ጭቆና ብርሃን ፈልቃቂ ከተማ የመሆኗን ጉዳይ ባለፉት ሁለት ዓመት ያየነው ሃቅ ይመሰክራል። በዚህ አጀንዳ ላይ ያለኝን አጭር አስተያየት ከማቅረቤ በፊት፤ ከወልቃይት የማንነት ጥያቄ ጋር ተያይዞ ባለፉት አርባ ዓመታት በግፈኛውሥርዓት ሕይወታቸው ላለፈ ወገኖቻችን የአንድ ደቂቃ የህሊና ፀሎት እንድናደርግ በትህትና እጠይቃለሁ።….አመሰግናለሁ።
ዛሬ በመላ ሀገሪቱ ለተከሰቱና ለመከሰትም እያንዣበቡ ላሉ ምስቅልቅሎሽና ግጭቶች አንደኛ ተከሳሽ የሆነው ከደደቢት የተነሳው ዘውገኛ ብረት-ነካሽ የጠዋት ማኔፌስቶ በግላጭ እንደሚነግረን “ነጻ የትግራይ ሪፐብሊክ”ን በመመስረት ቅዠት መለከፉን ነው። ግና፤ በወቅቱ ቅዠቱን ለማስፈጸም የሚችልባቸው “ደጋፊ-አቃፊ ሁኔታዎች” ስላልተሟሉ፣ ስልታዊ የአቋም ለውጥ አድርጎ፣ የትግሉን አጀንዳ በ“ብሔር-ጭቆና” ስም በመጥለፍ አያሌ ሀገራዊ ጥቅሞቻችንን ለምዕራባውያንና ለአረብ ሀገራት ጭምር በመስዋዕትነት አቅርቦ ለስልጣን በቅቷል። ወያኔ የነጻ መንግስት ጥያቄውን ለጊዜው መሳቢያ ውስጥ ቢከተውም፤ ለግንጠላ ያዘጋጀውን የበረሃ ካርታ ግን ከመተግበር ያገደው አንዳችም ኃይል አልነበረም። በዚህ ምክንያትም ከጎንደር እና ከወሎ ግዛቶች የተነጠቁ በርካታ መሬቶችን “እወክለዋለሁ” ለሚለው ማሕበረሰብ እንደ አንባሻ ሸንሽኖ ማከፋፈሉን ሁላችንም የምናውቀው ሐቅ ነው።
የሆነው ሆኖ በሽፍታ-መራሹ ስብስብ የተጫረው “ወያኔያዊ አብዮት” ሁለት-ግቦችን በአምድነት የተሸከመ ሲሆን፤ በመጀመሪያው ምዕራፍ፤ ግዛት ማስፋፋትን ታሳቢ አድርጎ ባካሄደው ሥር-ነቀል አብዮት የትግራይን ወሰን ተሻግሮ በጠብ-መንጃ ወርሮ በያዛቸው ግዛቶች ነባሩን ማሕበራዊ መዋቅር አፈራርሶ በአዲስ ተክቷል፤ የማሕበረሰቡን ርዕዮተ-ዓለማዊ ምልከታንም በዓይነቱ አዲስ በሆነ ገዥ-ሃሳብ ቀይሯል። ሌሎች ስር-ነቀል እርምጃዎችንም ወስዷል። እነሆም በዚህ መልኩ ወደ መሬት ያወረደውን ደም-የጠገበ ፖሊሲን ነው የ“ታሪክ ማስረጃ” እያለ ረብ-የለሽ ሙግት አንስቶ የሚያነታርከን።
የሶሻል ሳይንስ ምሁራን ትንታኔ እንደሚያፍታታው “የዛሬ ፖለቲካ የነገ ታሪክ ነው።” በዚህ ሥነ-አመክንዮ መሰረትም፣ ትላንት የተጭበረበረ ፖለቲካ፣ ዛሬ ወደ ታሪክነት ሲቀየር የተጭበረበረ ከመሆን የሚያነጻው አንዳችም የንስሃ ዘይት አለመኖሩን እንረዳለን። ነገር ግን አበው “የሌባ አይነ ደረቅ…” እንዲሉ፤ ወያኔና የጥቅም ተጋሪዎቹ ይህንን የትላንት ብላሽ ፖለቲካ የአባቶቻቸው እውነተኛ ታሪክ አድርገው ከመውሰዳቸውም ባለፈ፤ አካባቢው “የትግራይ ማህበረሰብ ይዞታ ነው” ለሚሉት ሙግት በማስረጃነት በማቅረብ እኛም አምነነን እንድንቀበል ለመጋት ሲዳዳቸው በትዝብት እየተመለከትን ነው።መላው ኢትዮጵያዊ እውነቱን እንዳያውቅ የወያኔ ግርዶሽ የጨለማ ምርጊት ሆኖበታል።
የመቀሌ ዩኒቨርሲቲን የመሰለ ወገንተኛ ተቋም አሁንም “የሸዋ የበላይነት ሊመጣ ነው!” የሚሉ ትርኪምርኪ ጥናቶችን በቅምጥ ምሁራን እያዘጋጀ ህዝባዊ ትግሉን ለማደናቀፍ እየሞከረ ነው። እዚህ ጋ መዘንጋት የሌለበት ቁምነገር፤ የወልቃይትና አዋሳኝ መሬቶች በድህረ የካቲት አብዮት ለተነሱ የሽምቅ ተዋጊዎች ሁሉ ዋነኛ መፋለሚያ መድረክ ሆኖ በመቆየቱ መረጃዎች በቃጠሎ፣ በዘረፋ፣ በመበላሸት እና በመሳሰሉት መንገዶች የመጥፋት እድላቸው ሰፊ መሆኑን ለመገንዘብ የጥናት ሪፖርት መጠበቅ አያሻንም። ስለዚህም በዘመናዊ ዓለም መሠል ግጭቶች በሚፈታበት ህዝበ ውሳኔ (የሪፈረንደም ጽንሰ ሀሳብ) የወልቃይትም ጉዳይ እንዲበየንበት መገፋፋት ካስነዋሪ የሕወሓት ቧልትነት ያለፈ ፋይዳ የለውም። ምናልባትም ‘በጠብ-መንጃ ክምችት እና በሰራዊት ብዛት የትኛውንም ህጋዊ ጥያቄ እየደፈቅን ለዘላቂው እንቆያለን’ የሚል መታበይ ከተጣባቸውም የታሪክ ድርሳናትን ጠንቅቀው እንዲያነቡ እንመክራለን። “ዓለምን ከእግሬ ጫማ በታች አሳድራታለሁ” እያለ መቄዶኒያን በሽለላ ሲያርዳት የነበረው ታላቁ እስክንድርም ወድቋል። ለጀግንነቱም ሆነ ለብልህነቱ ወደር ያልተገኘለት ናፖሊዮን ቦናፓርቲም ተሸንፏል። አውሮፓን በብረት መዳፉ የጨበጠው አዶልፍ ሂትለርም የማታ ማታ የውርደትን ጽዋ ተጎንጭቷል። ክንደ ብርቱው መንግስቱ ኃይለማርያም ለአሳፋሪ ስደት ተዳርጓል። እውነት እውነት እላችኋለሁም የወያኔ መዘባበትና ዕብሪትም ከዚህ የተለየ ዕጣ ፈንታ ሊገጥመው አይችልም።
የወያኔ ሁለተኛው አብዮት ዕቅድ፤ መዳረሻውን ምኒልክ ቤተ-መንግስት በማድረግ በተቀረው የሀገሪቱ አካባቢ የአዛዥ ናዛዥ ሚና እንዲኖረው የሚያስችሉትን ሁለት መላዎችን ዘይዶ ያስፈፀመበትን እናገኛለን። የመጀመሪያው፤ በመናኛ ሀሳብ ቡትቶ ፌዴራሊዝም ማንበር ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ፤ በሁሉም ክልሎች የአሻንጉሊት አስተዳደር መመስረትን ግቡ ያደረገ ነው። ሙሉ በሙሉም ተሳክቶለታል። ቢሮክራሲውን፣ ኢኮኖሚውን፣ ሠራዊቱን፣ ደህንነቱን በስግብግብነትና በዓይን አውጣነት ጠቅልሎ ይዟል። ይህን ዕኩይ ሴራ ለማስፈፀም መደላድል ይሆናሉ ተብለው ቡራኬ ከተቀበሉ ድርጅቶች መካከልም ብአዴን በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳል። አብዛኛው የድርጅቱ አመራርም ከኤርትራና ትግራይ ቤተሰብ የተገኘ ቢሆንም የጎጃሜውን ገብሩ አስራትና የወለየውን ሳዕረ መኮንንን ፈለግ በመከተል ለወጣበት ማህበረሰብ ከመታመን ይልቅ ለደደቢት ፍሬዎች በመንገድ መሪነት አገልግሏል። እያገለገለም ነው። በወረራ የተያዙት መሬቶች ጥንትም የትግራይ ለመሆናቸው ለሚቀርቡት የኑፋቄ ሐቲት በደቀ መዛሙርትነትም ተሰልፎ በሰሚ አልባ ጩኸቱ አደንቁሮናል። በግብረ-አበርነት በመሳተፍም የወልቃይትና የአካባቢው ነባሩ ማህበረሰብ የጅምላ ፍጅትና ሰንፋጭ ጭቆና እንዲፈፀምበት አድርጓል።
ለዚህም ነው ብአዴን በትጉኃን የህዝብ ልጆች ቁጥጥር ስር መዋል አለበት የምንለው። በነገራችን ላይ ዘግናኙ ጭፍጨፋ ልባችንን በሀዘን ቢሰብረውም ደመቁጡ ወጣቶች ትግሉን እንዲቀላቀሉ ገፊ ምክንያት በመሆኑ ደግሞ እንፅናናለን። ከሞላ ጎደልም እንደ ተድላ ባይሩ እና ዋቆ ጉቱ ሁሉ እነ ኮሎኔል ደመቀ ዘውዴ፣ አታላይ ዛፌ፣ መብራቱ ጌታሁን እና መሰል ብርቱ ጓዶችን እየፈጠረ እንደሆነ በዓይናችን ተመልክተናል። እናንተ ዐውደ ብርሀንን የተጎናፀፋችሁ ጀግኖችም በጨለማው ላይ እንደምትሰለጥኑም አምናለሁ። በአናቱ በወልቃይት ጉዳይ እናንተ የመጨረሻዎቹ ታጋዮች ትሆኑ ዘንድ የፍትህና ዴሞክራሲ ወገን ሁሉ ከጎናችሁ እንዲቆም መወትወት አለባችሁ።
በጥቅሉ የወያኔና ደጋፊዎቹ ማንአህሎኝነት፣ መዘባነን፣ የፖለቲካ መሰሪነትን በጥልቅ ሀዘን ስናስተውል ኧረ ለመሆኑ በወልቃይት ጥያቄ ላይ ጉጅሌው ቡድን እንዲህ እንዲሳለቅ “ሊቼንሳ” የሰጠው ማነው? ስንል አጥብቀን እንጠይቃለን። እዚህ ጋ ሳልጠቅስ የማላልፈው ከቀይ ሽብርም የከፋ ግፍ በአካባቢው ተወላጆች ላይ መፈፀሙ የማይስተባበል ዕውነታ ነው። በደጉ ቀይ ሽብር ዘመን የጥቃት ዒላማ የፖለቲካ አቋምን ታሳቢ ያደረገ ሲሆን የወልቃይት ግን ማንነትን ተንተርሶ የተፈፀመ የዘር ማፅዳት ወንጀል ነው።
በመጪዎቹ ጥቂት ወራትም ይህንን ጉዳይ በሠላማዊ መንገድ፣ በህጋዊ እና በቅንነት መፍታቱ በዜጎች ማህበራዊ ግንኙነትም ሆነ ፖለቲካዊ ጉዳዮች ሊከሰት የሚችለውን ጽንፈኝነትና በጦር ሜዳ መሸናነፍ ላይ ማዘንበልን ይታደጋል ብዬ አምናለሁ። ሂደቱ ያለ ግጭት እንዲያልቅ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ለማፍያውና አፋኙ ሕወሓት የጎን ውጋት መሆን እንዳለበትም ለማስታወስ እወዳለሁ። ጊዜው የህግ እንጂ የውንብድና መሆኑ አንድ ቦታ ላይ መቆም አለበት። በተቀረ ጥያቄውን በተለመደው መንገድ እወጣዋለሁ የሚለው ሕወሓታዊው ዕብሪት ለሕንድ እና ለፓኪስታን ዛሬም ድረስ ራስ ምታት የሆነችውን “የካሽሚር ግዛት” ክሱት እንዳደረገው ሁሉ፤ እዚሁ ዓይናችን ሥርም “ጥቁሯን ካሽሚር” ማዋለዱ አይቀሬ መሆኑን ለመናገር የነብይነት ፀጋን አይጠይቅም። “ጭቆና ቀቢፀ ተስፋን ያስፋፋል” የሚሉ ጸሐፍትም ከግዙፉ የአመድ ክምር ስር ፍም-ረመጥ የሚፈለቅቅ ሞት አይፈሬ ትውልድ ለመምጣቱ ምልክቶቹን እንዲያስተውሉ እመክራለሁ።
እናም በዋናነት ትግርኛ ተናጋሪውን ጨምሮ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ከግፉአን ጎን መቆም እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተን እንናገራለን። ይህንን ጥያቄ ወደ አደባባይ ማምጣቱ የማህበረሰብን ኅልውና ያናጋል የሚለው ሙግትም ጊዜ ያለፈበት መድሀኒት ነው፤ የሚገድል እንጂ የማያሽር። የተማረው መደብም ምሁራዊ አይናፋርነቱን ገትቶ የመፍትሔ ሀሳቦችን ሊጠቁሙ የሚችሉ ስራዎች ላይ ማተኮር እንደሚኖርበት እናሳስባለን። ልሂቃኑም የሕሊና ፍርድ ሊሰጡ ግድ ይላቸዋል። ከሁሉም በላይ ግን ብአዴን የተባለው የክልሉ አስተዳዳሪ “መልከ ሕወሓት” ጭምብሉን አውልቆ በመጣል የጥያቄው ባለቤት ሊሆን እንደሚገባው ነጋሪ መፈለግ የለበትም እንላለን።
በግልባጩ እንደ ከዚህ ቀደሙ በወያኔ ጥላ ስር እዝናናለሁ የሚል ከሆነ ባለፉት ሦስት ዓመታት ከፊል ክልሉን የነቀነቀው ህዝባዊ ቁጣ ክሽፈቱን አርሞ፣ ኃይሉን በብዙ እጥፍ አግዝፎ እየመጣ ነውና አንገቱን ለጊሎትን ማሽን ከማዘጋጀት ውጭ አማራጭ እንደማይኖረው ከወዲሁ አምኖ መቀበል አለበት። ስለምን ቢሉ በእንዲህ አይነቱ የህዝብ ፍርድ የዘረፋና የጭቆና ሀሳብ አመንጪው ሕወሓት ብቻ ሳይሆን፤ ተባባሪው ብአዴንም ከታዳኝነት አያመልጥምና ነው። ነገር ግን እንደ ኦህዴድ ጓዶቹ የራሱን ህዝብ በምርኩዝነት ተጠቅሞ ጥያቄውን ከማስፈፀም ባሻገር ቅጥ ያጣውን አፈና፣ እስር፣ ግድያ፣ መሬትን ጨምሮ ሁለንተናዊ ንብረት ነጠቃን የማስቆም ሽራፊ ወኔ ካለው ያን ያህል አዳጋች እንደማይሆንበት የማህበረሰቡን መነቃቃት ጠቅሰን እናስገነዝባለን። በአናቱም የጭቆናውን ቀንበር የማላላት፣ የብዝበዛውን ሸክም የማቅለል፣ ፖለቲካዊ ኃላፊነቶቹን መዘንጋት የለበትም። ከዚህ በኋላ በእንዲህ ዓይነት ጉዳይ መሞት-ካለመሞት፤ መታሰር-ካለመታሰር የሚኖርበት ግብር ሰብሳቢው፣ ሀብት አስተዳዳሪው፣ በስልጣን ተምነሽናሺው… ብአዴን ብቻ መሆኑን ለማስታወስ እወዳለሁ። በመጨረሻም ይህንን ቃል ለዓመታት ብየዋለሁ፤ ዛሬም እናንተ ፊት እደግመዋለሁ፡-በሞት ሸለቆ ሳይታለፍ ታሪክ መቀየር አይቻልም።
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!
ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ
Leave a Reply