
ከሁለት ጠቅላይ ግዛቶች የተውጣጡ አንድ ሺህ ወታደሮች ያካተተ “ግብረኃይል” ከአንድ ወር ተኩል በኋላ ወደ አፍሪካ ቀንድ እንደምታዘምት አሜሪካ አስታወቀች። ግብረኃይሉ “ቀዩ ዘንዶ” በሚል ስያሜ የሚጠራ ሲሆን በዜናው ጦሩ “ወደ ኢትዮጵያ ይሄዳል” በሚል የተነሳ ጉዳይ የለም። የተሰጠውም ተልዕኮ ለአፍሪቃ ቀንድ ግብረኃይል ተጨማሪ ድጋፍ ለመስጠት ነው ተብሏል።
ቅዳሜ ኅዳር 18፤ 2014 ዓም (ኖቬምበር 28፤ 2021) በተካሄደ ሥነሥርዓት ከ800 በላይ የሚሆኑ የቨርጂኒያ ግዛት ብሔራዊ አባላት ዘብ የተሸኙ ሲሆን ወደ 200 የሚጠጉ የኬንታኪ ግዛት ብሔራዊ ዘብ አባላት እንዲሁ ሽኝት ተደርጎላቸዋል፡፡
ይህ ከአሜሪካ የተላከው ግብረኃይል በምስራቅ አፍሪካዊቷ ጅቡቲ ከተቀመጠው የአፍሪካ ቀንድ ጥምር ግብረኃይል ጋር የሚቀላቀል ነው፡፡
ቤድፎርድ ከተባለችው የቨርጂኒያ ግዛት የተላከው ግብረኃይል ከኬንታኪው ጋር በመቀላቀል ወደ ቴክሳስ ግዛት በመሄድ ከ30 እስከ 45 ቀናት የሚወስድ ተጨማሪ ሥልጠና ይወስዳል፡፡ ይህ ሥልጠና ካበቃ በኋላ ነው ወደ ጅቡቲ ወታደሮቹ የሚላኩት፡፡
በዕለቱ የተሸኙት ወታደሮች ቤተሰቦቻቸውን በለቅሶ በተሰናበቱበት ወቅት “ሽኝት ቀላል ነገር አይደለም፤ ሁልጊዜ በጣም አስቸጋሪ ነው፤ በቤተሰቤ ሕይወት ውስጥ ቁልፍ የሆኑ ኩነቶች ያመልጡኛል” በማለት የግብረኃይሉ አዛዥ ሌተና ኮሎኔል ተናግረዋል፡፡
“ለቨርጂኒያ ብሔራዊው ዘብ 10 ዓመት ሳገለግል ይህ የመጀመሪያዬ ነው ወደ ውጭ አገር ስላክ” በማለት መጋቢ ሃምሳ አለቃ ካትሪን ተናግራለች፡፡ ከተጋቡ ሁለት ወራት የሆናትን ሚስቱንና ወላጆቹን ስሜት እየተናነቀው የተሰናበተው ሌላኛው ወታደር “ለዘመቻ መላክ በጣም ይደብራል፤ አባቴም ወታደር ስለነበር ሁኔታውን ይረዳል፤ ለሚስቴ ጥሩ እንክብካቤ ያደርግላታል ብዬ አስባለሁ” ብሏል፡፡
ዜናውን የተከታተሉ እንደሚሉት እነዚህ ወታደሮች ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ እና ውጊያ የሚያደርጉ አይደሉም፤ በዜናው እንደተጠቀሰው ጅቡቲ ለሚገኘው ኃይል ድጋፍ ለማድረግ ነው፡፡ ነገርግን ወደ ኢትዮጵያ እንግባ እንኳ ቢሉ ለሕይወቱ ቅንጣት ከማይሳሳ መከላከያ ሠራዊት፣ ልዩ ኃይል፣ ፋኖ እና ሚሊሻ ጋር ነው በአገሩ መልከዓምድር የሚገጥሙት ብለዋል፡፡
ትህነግ ወደ ሚሌ ሊያደርግ ያቀደውን ጉዞ በጭፍራም ይሁን በባቲ መስመር እንዳይሳካ ሆኖ በከፍተኛ ሽንፈት ላይ ባለበት ወቅት ይህ የአሜሪካ ግብረኃይል ለዘመቻ መላኩ የትህነግን ክስረት የሚያረጋግጥ ነው፡፡ በአንጻሩ ትህነግን ለመታደግ ቢሆን ኖሮ ቢቻል ከዚህ በፊት ባይሆን አሁን በፍጥነት መላክ ነበረበት፡፡ ሆኖም ከአንድ ወር በኋላ መላኩ በዜና ዘገባዎችም እንደተገለጸው አሜሪካ የራሷን መከላከያ ኃይል ለማጠናከርና ካስፈለገም የዜጎቿን ደኅንነት ለማስጠበቅ የላከቸው ኃይል እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡
የቨርጂኒያው ኃይል የተሸኘበት ቤድፎርድ የተባለችው ከተማ በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት የነበራት ሕዝብ ብዛት 3200 የነበረ ሲሆን በወቅቱ ብዙ ወታደር ያጣች ከተማ ነች፡፡ እኤአ በ1944ዓም 150ሺህ የአሜሪካ ወታደሮች ወደ ፈረንሳይ ከዘመቱ በኋላ እዚያ በደረሱበት የመጀመሪያ ቀን 4500 ወታደሮች ሲሞቱ ከእነዚያ ውስጥ 19ኙ ከቤድፎርድ ከተማ ቨርጂኒያ ግዛት የተላኩ ነበሩ፡፡ በጦርነቱ በአጠቃላይ 35 ወታደሮች ከከተማዋ ብቻ ሞተዋል፡፡
የዛሬ 28 ዓመት የሶማሌውን አንጃ መሪ ጄኔራል ፋራህ አይዲድን በቁጥጥር ሥር ለማዋል ከተላኩ የአሜሪካ ወታደሮች 19ኙ በሶማሊያ ኃይል ተገድለው 73ቱ ደግሞ መቁሰላቸው ይታወሳል፡፡ ከተገደሉት መካከል የተወሰኑት በሞቃዲሾ መንገዶች ላይ በመጎተታቸው አካላቸው ተቆራርጦና በጣም ከፍተኛ እንደደረሰባቸው የሚታወስ ነው።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
አይ ለይቶላቸው ወደ መቀሌ ቢሄድ አይሻልም ነበር። አሜሪካ የውሸት ፕሮፓጋንዳዋ ተቀባይነት ሲያጣ አሁን ደግሞ እሳት ይዛ እሳት ልታቀብል መዘጋጀቷን ይህ ነገር ያሳያል። ለዚያ ነው አሜሪካኖች ዋና ስራቸው ተንኮልና ሃገር ማፍረስ ነው የምንለው። ይህ ዝም ብሎ ከሚያልፍ ወንዝ የተቀዳ ወሬ ሳይሆን በዓለም ዙሪያ የሚፈጽሙት ተግባር ዋቢ ነው። ግራ ያጋባል የአሜሪካን የውጭ ጉዳይ ፓሊሲ ረጋ ብሎ ለተመለከተው። አንድ ጋ ሲባረሩ ሌላው ጋ እሳት ይጭራሉ። ዛሬ ዪክሬንን አፍንጫዋ ድረስ የሚያስታጥቁት አሜሪካኖች ራሽያ ዪክሬንን ብትወር ወታደሮቻቸው ዘር አይሉም። ያፋልማሉ እንጂ አይፋለሙም። እሾህን በእሾህ ያወጣሉ እንጂ እነርሱ እምብዛም አይሞቱም። ከሞቱም እየየውና ለቅሶው ለነጩ የተለየ ነው። አይ ሃገር። ሰላምና ዲሞክራሲን ለማስፈን እየተባለ የቆመን ማፍረስ፤ በፍርስራሹ ውስጥ ሴራን መንዛትና ምድሪቱ ለዝንተ ዓለም ለማኝና ችጋራም ሆና እንድትኖር ማድረግ ግባቸው ነው። ትላንት ለሌላው ሃገር ይተርፉ የነበሩት ሃገሮች በአሜሪካ ሴራና የኢኮኖሚ ማዕቀብ ተሽመድምደዋል። የሃገሬው ህዝብ የደነዘዘ በመሆኑ በአሜሪካ ህዝብ ስም መንግስታቸው የሚያደርገውን የፈጠራው ዜና ከሚያናፍሰው በስተቀር እውነቱን አያውቁም ማወቅም አይፈልጉም።
አፍቃሪ ትህነግ አሜሪካኖች ወያኔን አዲስ አበባ ለማስገባት ያልሞከሩት ዘዴ የለም። ችግሩ ወይ ፍንክች ሲሆንባቸው ከማስፈራራትና የለሌ ወሬ ከመንዛት አልፈው አሁን ጦር መዘው መጣን እያሉን ነው። ይሁና። እየሞቱ መኖር ነው። ጊዜውን እንደሆነ ይኖርብናል እንጂ እኛ በጊዜአችን መኖር አልቻልንበት። አሜሪካ ለይቶላት ኢትዮጵያ ላይ ትንኮሳ ካደረገች ልክ እንደ አፍጋኒስታን ፊልሚያው የስውርና የግልጽ ነው የሚሆነው። አሜሪካ ሃገሮችን በማስፈራራትና መሪዎቻቸውን በመግደል ታደርግ የነበረው ዘረፋና መቆጣጠር አክትሟል። ይሞክራሉ ግን ያው ስኬት አይኖረውም። በተለይ ኢትዮጵያ ላይ እንዲህ አይነት ችግር ከፈጠሩ ውጊያቸው በዓለም ላይ ካሉ ሰላም ወዳድና አሜሪካ ጠል ሃገሮች ጋር ነው የሚሆነው። እኛ ያልነውን ካልሰማችሁ ወዪላችሁ የሚለው የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ፓሊሲ በ 21ኛው ክፍለ ዘመን አይሰራም። አዎን እንራባለን፤ በዚህም በዚያም ሰዎችንና ሃገሮችን እያስታጠቁ እርስ በእርሳችን ያጋድሉናል ግን መጨረሻው ልክ በአፍጋኒስታን ከ 20 ዓመት በህዋላ እንደሆነው ሁሉ የሰው መሳቂያ ሆነው ነው የሚፈረጥጡት። የአሜሪካ ሴራ ማቆሚያ የለውም። የትኛውም የፓለቲካ ፓርቲ ስልጣን ላይ ይሁን አይቀየርም። ዛሬ ሱዳን ልቧን ነፍታ የኢትዮጵያን መሬት ወራ የያዘችውም በዚሁ በአሜሪካ አይዞህ ባይነትና ተንኮል ነው። በቅርቡ የመፈንቅለ መንግስቱ መሪ የሆነው የሱዳን ወታደራዊ መሪ በኢትዮጵያ ድንበር ውስጥ ገብቶ ጉብኝት እንዲያደርግ የገፋፉት እነርሱ ናቸው። ሲሻቸውና የመገልገያ ጊዜው ሲያበቃ ልክ እንደ ፓናማው ጄ/ኖርዌጋ በዚህም በዚያም አሳበው እስር ቤት ይጨምሩሃል ወይም ከጄኔራል ኖሬይጋ በፊት እንደነበረው የፓናማ መሪ ህዝባዊ ተሰሚነት ካለህም ገድለው ሞተ ይሉሃል። Read ” Confession of an Economic Hit man” by John Perkins እውነቱ እሱ ነው። አሁን አሜሪካ በኢትዮጵያ ላይ የምትከተለውም ዘይቤ በዚሁ መጽሃፍ ላይ ከተጠቀሱት ብልሃቶች የተወሰደና በዘመናዊው የኢንተርነት የአስረሽ ምቺው ውንብድናቸው የጣፈጠውን ነው። የእነ ዶ/ር ኤሌኒ ስብሰባ፤ የ 9ኙ የዲሲ የሽግግር መንግስት ድለቃ፤ የፊልትማን የኢትዮጵያ ምልልስ፤ የተመድ ድግግሞሽ ስብሰባ፤ ዜጎቼን አወጣለሁ፤ የኢትዮጵያ የአየር ክልል አደጋ አለበት ወዘተ እየተባለ የሚናፈሰውና የሆነው ሁሉ የዚሁ ሴራቸው ድምር ሂሳብ ነው።
አሜሪካኖች ከግብጽ ጋር ምን እየመከሩ እንደሆነ የሚያውቅ አለ? አሜሪካኖች ለዘመናት ኤርትራን ፈርጀው ለችጋር ያጋለጧት በእውነት የኤርትራው መሪ ከሌሎች ሃገራት መሪዎች ከፍተው ነው? እንዴት ይህንና ሌሎች መሰል ነገሮችን የሚሰማ፤ የሚያነብ፤ የሚያይ ሰው ወንድሙንና እህቱን ይገድላል? አያሳዝንም? እስከ መቼ ነው የነጭ መፈንጫ የምንሆነው? ግን አይዞን እንኳን 500 ዓመት ያልሞላው የአሜሪካው መንግስት ይቅርና የሮም መንግስትም ተፍረክርኳል። በእንግሊዝ ግዛት ጸሃይ አትጠልቅም የተባለላት እንግሊዝ አሁን በአንዲት ደሴት መሳይ ሃገር ነው ተወስና ያለችው። ቀልደኛው በእንግሊዝ ግዛት ጸሃይ አትጠልቅም ሲሉት ” አይ ፈጣሪ እንግሊዞችን በጨለማ ስለማያምናቸው ነው” በማለት ነበር ያፌዜው። ግን እውነትነት አለበት። ዛሬ በምድር ላይ ላሉ ፍትጊያዎች ሁሉ ምንጮቹ እንግሊዞች፤ ፈረንሳዪች፤ አሜሪካኖች ቀዳሚዎቹ ናቸው። አሁን እጣው በሃበሻው ምድር ላይ ወጣና ያጫንቁን ጀመር። እናያለን ቀን የሚያመጣውን። እስከዚያው አይዞን። በቃኝ!