
* በስጋት ከቀያቸው የተፈናቀሉት የትግራይ ተወላጆች ቤታቸው ሳይፈርስ፣ ንብረታቸው ሳይጎድል ለዓመታት ጠብቋቸዋል
በትላንትናው የፓርላማ ውሎ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በኢሉባቦር ዞን ሁሩሙ ወረዳ ይኖሩ የነበሩ የትግራይ ተወላጆችን አስመልክቶ የተናገሩ የብዙዎችን ልብ የነካና ኢትዮጵያዊነትን አድምቆ ያሳየ መረጃ ነበር።
“ለምሳሌ ጦርነት ሲጀመር” አሉ ዐቢይ “ከኢሉባቡር ሸሽተው ትግራይ የሄዱ አርሶ አደሮች ነበሩ። ከዛ የመጣችሁ ሰዎች አጥኑ ይሄን ጉዳይ ትክክለኛ መረጃ ነው።
“ሰዎቹ ሸሽተው ትግራይ ገብተዋል፤ ኢሉባቡር ያሉ አርሶአደሮች ከእነርሱ ማሳ ቡና ለቅመው ሸጠው ገንዘቡን በአካውንታቸው ያስገባሉ፤ ሰዎቹ የሉም። ከእርሻቸው ላይ የተመረተ ምርት ሸጠው ገንዘቡን በራሳቸው አካውንት ያስገባሉ።
“ሰዎቹ ‘የኛ ሰዎች በሌለንበት ሰርተው አካውንታችን እያስገቡ ነውና በቃ እንመለስ’ ብለው ተመልሰው ኢሊሉባቡር አሉ አሁን፣ እየኖሩ ነው” ብለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በፓርላማ ማብራሪያቸው ላይ የጠቀሱት ይህ የአብሮነት እሴት፣ ኢትዮጵያ በፈተናዎች ውስጥም ጠንካራ መሰረት እንዳላት ማሳያ ሆኗል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው ጦርነቱ ሲጀመር በኢሉአባቦር የነበሩ አርሶ አደሮች ከአካባቢው ሸሽተው ትግራይ ከገቡ የትግራይ ተወላጆች ማሳ ላይ ቡና ለቅመው፣ ሸጠው ገንዘቡን በአካውንታቸው ያስገቡ እንደነበር ገልፀዋል።
ይህንን ያዩት አርሶአደሮችም ተመልሰው ከቤታቸው ገብተዋል ያሉት ጠቅላይ ሚነስትሩ በራያ፣ በፀለምት እና በኦሮሚያ አካባቢዎች ሌሎችም ወደ ቄያቸው ተመልሰው እየኖሩ ነው ብለዋል።
ከዓመታት በፊት በኢሉአባቦር ዞን ይኖሩ የነበሩ የትግራይ ተወላጆች በጸጥታ ስጋት ምክንያት ንብረታቸውን ጥለው ወደ ትግራይ ተሰደው ነበር።
ከእነዚህም መካከል አቶ መሀሪ ወልዴ እና አቶ መኮንን በርሄ ይገኙበታል። ተፈናቃዮቹ አርሶ አደሮች ከዓመታት በኋላ ወደ ቀደመ መኖሪያቸው ሲመለሱ የጠበቃቸው ነገር እጅግ አስገራሚ ነበር።
ቤታቸው አልፈረሰም፤ አደራቸውም ተጠብቋል፤ ገቢያቸውም አልተቋረጠም። ቤት ንብረታቸውን ጥለው ወደ ትግራይ የተሰደዱት ተፈናቃዮች የመኖሪያቸው “ቆርቆሮው ጥርኝ ሳይነካ፣ አጥራቸው ሳይነቃነቅ” ጠብቋቸዋል።
በስደት በነበሩበት ወቅትም የቡና ምርታቸውና የቤት ኪራይ ገቢያቸው አቶ አዲሱ አወቀ እና አቶ ታምራት አረጋን በመሰሉ የአካባቢው ነዋሪዎች አማካኝነት በባንክ ከነበሩበት ድረስ በታማኝነት ይላክላቸውም እንደነበር ይናገራሉ።
“በኦሮሞ ማህበረሰብ ዘንድ አደራ መጠበቅ ትልቅ ኃላፊነት ነው” የሚሉት ነዋሪዎቹ፣ የወንድሞቻቸውን ንብረት እንደራሳቸው ጠብቀው አደራቸውን በታማኝነት በመወጣት አስረክበዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በፓርላማ በሰጡት ማብራሪያ፣ ይህንን የኢሉአባቦርን ታሪክ በማንሳት፤ ኢትዮጵያውያን በፖለቲካ ትኩሳት ሳይበገሩ በአብሮነት የመኖር ጥልቅ እሴት እንዳላቸውና ይህንንም ማጠናከር እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተውበታል። የሁሩሙ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሀብታሙ ቸርነት እንዳሉት፣ ዛሬ በወረዳው ሁሉም ኢትዮጵያውያን በፍቅርና በአንድነት እየኖሩ ነው። (EBC)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ






Leave a Reply