የብር ኖቶች መቀየር በህወሓት ሠፈር መደናገጥ ፈጥሯል
ኢትዮጵያ በአዳዲስ የብር ኖቶች እንደምትጠቀም ጠ/ሚ/ር ዐቢይ ይፋ ካደረጉ በኋላ መቀሌ የመሸገው ህወሓት ችግር ውስጥ መግባቱ ተሰምቷል። አዳዲሶቹ ብሮች ሙስናን እና የኮንትሮባንድን ንግድ መቀልበስ ዓላማው ማድረጉ ተነግሯል።
ላለፉት ሁለት ዓመታት መቀሌ መሽጎ የሚገኘው ህወሓት የተባለው የበረኻ ወንበዴዎች ስብስብ ላለፉት እጅግ በርካታ ዓመታት ኢትዮጵያን ያለገደብ ሲዘርፍ የነበረ ቡድን መሆኑን ራሱም የሚመሰክረው ሐቅ ነው።
ከሁለት ዓመት ተኩል በፊት ከምኒልክ ቤተመንግሥት ከተባረረ ወዲህ መቀሌ በየሆቴሉ መሽጎ የሽብር ተግባራትን ሲፈጽም ቆይቷል። ይህንንም ተግባሩን ለማስፈጸም እንዲረዳው በሕገወጥ የገንዘብ ዝውውር፤ ሐሰተኛ የብር ኖቶች በማተም ተግባር፤ በኮንትሮባንድ ንግድ፤ ገንዘብ ከአገር በማሸሽ፤ ወዘተ ሕገወጥ ተግባራት ተሰማርቶ አገር የማፍረስ ሥራውን በትጋት ሲሠራ ቆይቷል።
የኢትዮጵያ የገንዘብ ኖቶች ይቀየራሉ የሚለው መረጃ ሲነገር የቆየ ቢሆንም ጉዳዩ ለበርካታ ጊዜያት በምሥጢር ተይዞ ቆይቷል። ህወሓትም ባንድ በኩል የብር ኖቶችን ወደ ዶላርና ፓውንድ በመቀየሩ ተግባር በሥፋት ተሠማርቶበት የነበረ ቢሆንም ባልተጠበቀ ጊዜ ዜናው ይፋ መደረጉ በህወሓት ሠፈር መደናገጥ ፈጥሯል።
የወንበዴዎቹ ቡድን ድርጎ የሚሠፍርላቸው ተላላኪዎች የብር ኖቶቹ መቀየራቸው ከተሰማበት ጊዜ ጀምሮ በህወሓት ሠፈር ሽብር መፈጠሩን የሚያመላክቱ መረጃዎችን ሲበትኑ ቆይተዋል። አንዳንዶቹ አስቀድመን ብሩን ወደ ውጭ ምንዛሪ ቀይረናል በማለት አልተሸነፍንም ለማለት የሞከሩ ሲሆን ሌሎቹ ደግሞ ሌሎች አጀንዳ የማስቀየሪያ መረጃዎችን በማሰራጨት ትኩረት ለመሳብ ሲሞክሩና በግልጽም ሲናገሩ ተስተውለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ነባሮቹን የ10፣ የ50 እና የ100 ብር የገንዘብ ዓይነቶች ሙሉ ለሙሉ በመተካት ለግብይት የሚሆን አዲስ የገንዘብ ዓይነት በዛሬው ዕለት (ሰኞ) ይፋ አድርገዋል። ከዚህ በተጨማሪ ኢትዮጵያ የሁለት መቶ ብር ኖትን ወደ ሥራ ታስገባለች ብለዋል። በወጣው መረጃ መሠረት የ5 ብር ገንዘብ ባለበት ቀጥሎ፣ ከተወሰነ ጊዜ በኋላ ወደ ሣንቲም የሚለወጥ ይሆናል።
የብር ኖቶቹ የመለወጥ ጉዳይ ይፋ ከሆነ በኋላ በትግራይ የህወሓት ሰዎች በተለያዩ ወጣቶች ብር በማስቀመጥ ለመለወጥ ሙከራ እያደረጉ እንደሆነ ተሰምቷል። ይህም በሕገወጥ መንገድ በህወሓት የተሰበሰበውን ብር ሕጋዊ ለማድረግ የታሰበው አካሄድ አስቀድሞ በፌዴራል መንግሥቱ የታሰበበት መሆኑን የሚያመለክት ሆኗል።
ጠቅላይ ሚ/ሩ እንደተናገሩት፤
- ከ1.5 ሚሊዮን ብር በላይ ይዞ የሚመጣ ሰው ገንዘቡ ይወረሳል
- በውክልና ገንዘብ መቀየር አይቻልም
- ከኢትዮጵያ አጎራባች አገራት ወደ አገር ውስጥ የሚገባ ገንዘብ ይወረሳል
- መከላከያ ወይም ፖሊስ ይህንን ወርሶ ተቋሙን ለማጠናከሪያ እንዲውል ይደረጋል
- የሚቀየረው ገንዘብ ይዞ የመጣው ሰው ባለው ወይም በሚከፍተው የባንክ ሒሳብ የሚገባ ሲሆን ከሁለት መቶ ሺህ ብር በላይ መውሰድ አይቻልም
- ሕገወጥ ገንዘብ በመለወጥ ሒደት ላይ የሚሳተፉ፤ በጎጥ፣ በዘር፣ በሃይማኖት፣ በወገንተኝነት፣ ወዘተ በመተባበር ሕገወጥ የሆነ ወይም ሃሰተኛ የብር ኖት በመቀየር የሚተባበሩ ባንኮች ወዲያውኑ ኅልውናቸውን ያጣሉ፤ ይዘጋሉ፡፡ እንደ ጠቅላይ ሚ/ሩ አነጋገር “በሚቀጥለው ቀን ባንክ መሆናቸው ያከትማል” ብለዋል፡፡
አዲሱ የብር ኖት 2.9 ቢሊዮን ታትሞ በሁሉም የአገሪቱ አካባቢዎች ለስርጭት ዘግጁ መሆኑን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ አስታወቀ።
በዕለቱ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ዶ/ር ይናገር ደሴ አዲሱን የብር ኖት በማስመልከት መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም፤
- አዲሱን የብር ኖት ለማሳተም 3.7 ቢሊዮን ብር ውጭ መደረጉንም ገልጸው፤ በሁሉም ክልሎች በበቂ ሁኔታ ለማድረስ ዝግጅት መደረጉንም ተናግረዋል።
- የብር ቅያሬው በውክልና የማይከናወን በመሆኑ መታወቂያ በመያዝ ባለቤቱ ብቻ ማከናወን ይኖርበታል ብለዋል።
- ከአጎራባች አገራት የሚገባን ህገ ወጥ ገንዘብ ለመቆጣጠር በድንበር አካባቢ ጥብቅ ቁጥጥር የሚደረግ መሆኑን ዶክተር ይናገር መግለፃቸውን ኢዜአ ዘግቧል።
የብር ኖቶቹን ለምን መቀየር አስፈለገ?
- መደበኛ ባልሆነ መንገድ እንዲሁም ከፋይናንስ ተቋማት ውጪ የሚዘዋወረውን ገንዘብ ለመሰብሰብ፣
- ሙስናን እና የኮንትሮባንድ ሥራዎችን ለመቀልበስ፣
- ለሕገ ወጥ እንቅስቃሴዎች የሚደረግን ድጋፍ ለማስቀረት ፣
እርምጃው የፋይናንስ ተቋማት የገንዘብ እጥረትን ለመቋቋም እንዲችሉም እንደሚያግዝ ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
አሁን በምን ደረጃ ላይ ይገኛል?
አብዛኛው የሕትመት ሥራ ተገባዶ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ግምጃ ቤት ይገኛል። የስርጭት ስርዓት እና ዕቅድ የተዘጋጀ ሲሆን፣ በሚመለከታቸው አካላት አማካኝነት ይተገበራል።
በገንዘብ ቅያሬው ሂደት ውስጥ የጸጥታ አስከባሪ አካላት ከፍተኛ ሚና የሚጫወቱ ሲሆን፣ የሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ከማኅበረሰቡ ጋር በመተባበር ጥንቃቄ በሞላበት መንገድ ያስፈጽማሉ ተብሏል።
ከብሔራዊ መከላከያ ሠራዊት፣ ከብሔራዊ የመረጃና ደህንነት አገልግሎትና ከፌደራል ፖሊስ የተውጣጣ ኮማንድ ፖስት ተቋቁሞ፣ ሂደቱን በበላይነት ያስተባብራል። የክልል መንግሥታት ተመሳሳይ ኮማንድ ፖስት አቋቁመው ሥራውን እንዲያከናውኑ ይጠበቃል።
- አዲስ የታተሙት የብር ኖቶች ዓይነት፣ የደህንነት መጠበቂያ ምልክቶች እና ምስሎች
ተከታታይ ቁጥሮች
- የገንዘቡ ቁጥሮች በሚያጎላ ማሽን ሲታዩ ከጥቁር ወደ አረንጓዴ ፍሎረሰንት ቀለም ይለወጣሉ።
ማየት ለተሳናቸው ዕውቅና ምልክት
- የብሩን ዋጋ የሚገልፅ ማየት የተሳናቸው በእጅ ዳሰሳ ማወቅ የሚችሉበት የደህንነት መጠበቂያ ምልክት አለው።
ጎርባጣ መስመሮች
- የባንክ ኖቱ ሲዳሰስ የመጎርበጥ ስሜት እንዲሁም የኖቱ ዋጋ ይታያል።
ደማቅ አንፀባራቂ ምልክት
- ገንዘቡ ወደ ላይ ወይም ወደታች ሲዞር የሚንቀሳቀስ ደማቅ የቀለም ፍንጣቂ የደህንነት መጠበቂያ ምልክት።
የደህንነት መጠበቂያ ክር
- የሚሽከረከር ደማቅ ቀለም ኮከብ አዲስ የደህንነት መጠበቂያ ክር፤ በክሩ ውስጥ NBE፣ ኢብባ እና የገንዘቦቹ አይነት ተፅፎ ይገኛል።
የውሃ ምልክት
- ገንዘቡ ወደ ብርሃን አቅጣጫ ተደርጎ ሲታይ በላዩ ላይ ከሚገኘው ምስል ፊት ለፊት ተመሳሳይ ደብዛዛ የውሃ መልክ ያለው ምልክት ይታያል።
ትይዩ ምልክት
- የብር ኖቶች ከብርሃን አቅጣጫ ሲታዩ ኳስ መሳይ ምልክት ከገንዘብ በስተኋላው ካለው ተመሳሳይ ጋር በፍፁም ትይዩ ሆነው በአንድ ቦታ ላይ ያርፋሉ።
ፈሎረሰንስ ምልክት
- አንበሳው ምስል ራስ ላይ አልትራቫዮሌት ጨረር ሲበራበት ወደ ቢጫነት የሚለወጥ ፍሎረሰንት ምልክት።
አዲሱ የብር ኖቶች ከሚያመጡት በርካታ ጠቀሜታዎች በተጨማሪ በህወሓት ዘመን በሃሰት ሲሰራጩ የነበረውን የገንዘብ መጠን፤ አለአግባብ ወደ ኢኮኖሚ የተረጨውን የብር ኖት ለመሰብሰብ እና የዋጋ ግሽበትን ለመከላከል እንደሚጠቅም ተነግሯል፡፡
በኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ ከመደበኛው የባንክ ሥርዓት ውጪ ከ113 ቢሊዮን ብር በላይ ይንቀሳቀሳል። አዲሱ የብር ኖት ለውጥ ይህንን በኢኮኖሚው ውስጥ የተረጨ ገንዘብ በባንኮች ተቋማዊ አሠራር ውስጥ እንዲያልፍ ያደርጋል ተብሎ ተገምቶዋል።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Rahel says
በርታልኝ፡አቢቹ፡ጀግናዬ፡ያመንከው፡እየሱስ፡አሁንም፡ከፍ፡ያድርግህ፡ከፍ፡አድርገኽናል