ለረጅም አመታተ የጣልኩትን ብዕር ድር ካደራበት ሰገባው እንድመዝ አስገደደኝ – በ ኢትዮ-ሚዲያ (Ethiomedia) እና በጎልጉል (Googlgule) ድህረ-ገፆች ላይ ከወራት በፊት በዶክተር ፍቃዱ በቀለ በተባሉ ግለሰብ በ”የተቆለፈበት ቁልፍ” መፅሐፉ ላይ የቀረበ አንድ ፅሑፍ።
“ሃያሲው” በዘመናችን አቻ ያላገኙለት (ወደር የሌለው) መፅሐፉ መሆኑን ነው የገለፁልን።
“…የስነ-ጽሁፍም ዋና ዓላማው በአንድ ህብረተሰብ ውስጥ ያሉትን አስቀያሚም ሆነ ቆንጆ ነገሮች ስዕላዊ በሆነ መልክ መግለጽ ሲችሉና አንባቢውን በልዩ ሃሳብ ውስጥ ተመስጦ እንዲዋኝ ማድረግ ሲችሉ ብቻ ነው።…” በማለት ካብራሩ በኃላ ከ`ዚህ አንፃር “የተቆለፈበት ቁልፍ” እንደተዋጣለት መሰክርነታችውን ይሰጣሉ። አንዲህ ሲሉ “….በታሪካችን ውስጥ በመጀመሪያ ጊዜ በልዩ አቀራረብ የተዘጋጀና የተጻፈ ትምህርታዊ መጽሀፍ ነው ….መጽሀፍ በአገራችን ታሪክ ውስጥ በዐይነትም ሆነ በአቀራረብ የመጀመሪያው ስለሆነ ለወደፊት ምርምራችንና ዕድገታችን እንደመመሪያ ሊያገለግል የሚችል መጽሀፍ ነው።”
ከሀገርና ከአህጉር አልልፈውም “…. በዓለም አቀፍ ደረጃ አሉ ከሚባሉት ስነ-ጽሁፎች ውስጥ ሊካተት የሚችል መጽሀፍ ነው….” ሲሉም ድንበር አሻግረው ከምርጦቹ ጎራ አልቀው ይሾሙታል።
የመፅሐፍን ደራሲ ዶ/ር ምሕረት ደበበንም “…ብቸኛው ኢትዮጵያዊ ….ፈላስፋ…..” እያሉም አሞጋገስውልናል።
በእርግጥ ይህ መፅሐፍ እርሳቸው በአስቀመጡልን ደረጃ ቦታ የምንሰጠው ነውን?! የደራሲውስ የሥነ-ፅሐፍ ችሎታና ክህሎት በእውነት በአደነቁት መጠን የሚጨበጨብለት ነው?! የወዳጅነት ፍቅር፣ አክብሮትና ስሜታቸውን ነው የገለፁት ወይስ በእውነት ምክንያታዊ ትችታቸውን?!
“ሃያሲው” ዶ/ር ፍቃዱ ከጽሁፋችው መግቢያ ጥቂት የማይሰኙ መፅሐፍትን ለማንበበ ሞክረው “….ዝም ብሎ ትረካ…” ሰለሆነባቸው በጅምር አንደተዋቸው ገልፅው በዘመኑ ከሚወጡ መፅሐፍት ውስጥ አንብበው ከጨረሱት ይልቅ ከግምታቸው በታች ሆነውባቸው በጅምር የተዋቸው በእጅጉ እንደሚበዙ ጠቅሰዋል። እዚህ ላይ የምጋራቸው ስሜት ተመሳሳይ ነው:: ያደኩት በአሸናፊ ዘ-ደቡቡ እና በጎርጎሪዎስ የብዕር ጦርነት አውድማ ላይ ነው። የ`ነ ዳግላስ ጴጥሮስን (ጌታቸው በለጠ)፣ መምህር ፍቅሩ ደበበን፣ ዳንዴው ሰርቤሎን፣ ዕዝራን፣ ሚካኤል ምሥግናን… የብዕር ቱሩፋትን የተቌደስኩ በመሆኔ እኔም እንደ`ርሳቸው ጎልዳፋ ብዕር አይዋጥልኝም። ይጎረብጠኛል። ነገር ግን በ”የተቆለፈበት ቁልፍ” መፅሐፍ ላይ ያለን ግንዛቤ ለየቅል ነው። የተመለከትንበት መነፅር ይለያያል። አተረጉአጎማችንና አረዳዳችን ወዲያ እና ወዲህ ነው።
አንድ የሚያውቀኝ ወዳጄ ለዕረፍት ሀገር ቤት በሄድኩበት ወቅት ሲፈራ ሲቸር “ካሉት መፅሐፍት ይሻላሉ!።” ብሎ ከሰጠኝ ዐራት ሥራዎች አንዱ ነበር – ይኸው የተቆለፈበት ቁልፍ።
በመልስ ጉዞዪ አውአሮፕላን ከገባሁ በኃላ በአጋጣሚ ከቦርሳዪ በቅድሚያ መዝዤ አወጣሁት። ዳጎስ ያለ በመሆኑ አትላንቲክን እያጫወተ ያሻግረኛል በሚል ተስፋ እንዳያልቅብኝ እየሰሰትኩ ማንበብ ጀመርኩ።
ዋናውን ሽፋንና የመግቢያ ሀተታዎቹን ሳይጨምር ታሪኩ ከሚጅምርበት ምዕራፍ በኃላ ከሁለትና ሦስት ቅጠሎች በላይ ወደ ግራ ገልጬ ማሻገር ሳልችል ቀረሁ። የመፅሐፉ ጠርዝ ቀኝ እጄን እንደመዘነ አጠፍቁት። በጅምር።
መልካም ስምና ጥዑመ መዓዛ ያለው ምግብ ቀርቦለት ለመብላት ሰፍ ብሎ ድንገት ከላዩ ላይ ጸያፍ ነገር ዓይቶ ወስፋቱ “እንደተቆለፈበት” ተመጋቢ ዘጋኝ – “የተቆለፈበት ቁልፍ”።
“እንዴ…?! ምኑ? ለምን?”
ምክንያቴን እንሆኝ!
አንድን መፅሐፍ “ምሉዑ” ከሚያስኙት መስፈርቶች አንዱና ዋናው ደራሲው ሃሳቡን ለመግለፅ የሚጠቀመበት የቋንቋ ውበት ነው። ከ`ዚህ አንፃር የመጽሐፉ “ደራሲ” የቃላት ሰበዝ አመዛዘዝ፣ አስተታጠፍና አወጋግ፣ የዓረፍተ-ነገር አሽራረብ፣ የአንቀጽ አገማመድ… የአንባቢን ስሜት የሚዘበራርቅ ሆኖ ነው ያገኝሁት። አይመቹም። እንደሚናገሩት እንደወረደ መፃፍ እና ሥነ-ፅሑፋዊ ውበትን ጠብቆ እያማጡ ወረቀት ላይ ማስፈር ልዩነት አላቸው። ሁላችንም ደራሲ መሆን ያልቻልንበት ሚስጥርም ይሄው ይመስለኛል።
በ`ዚህ በዶ/ር ምሕረት ደበበ “የተቆለፈበት ቁልፍ” መፅሐፍ ተመሳሳይ ቃላት ከመጠን በላይ ተደራርበው ነው የምናገኙው። በዚህም ሳቢያ ሀረጋት ሳይወዱ በግድ መንትተው የቃላት ማጥ ፈጥረዋል። ይህ ደግሞ አንባቢን በተገቢው ፍጥነት ከታሪኩ ፍሰት ጋር አብሮ እንዳይወርድ ያዳልጡታል። ይጎረብጣሉ። መፅሐፉንም አሰልቺ ያደርገዋል። ይህ ምሕረትን ጨምሮ ብዕራቸውን የሚያሙዋሹ ቡቃያ ደራስያን ፈተና ነው።
መፅሐፉ “ቁልፍልፍ” በሚለው ርዕስ ከገጽ ሰባት ይጀምራል። በአንደኛና በሁለተኛ አንቀጻት ላይ ገና ከድርሰቱ መነሻ “ቁልፍ” የሚለው ቃል ከ`ነ እርቢዎቹ ዶ/ር ምህረት መደጋገም ብቻ ሳይሆን አምርተዋቸዋል ማለት ይቻላል። እንቁጠራቸው።
መፅሐፉን አንደማልጨርሰው ስጋት የገባኝ እዚሁ ምዕራፍ አንድ አንቀጽ ሁለት ላይ ነው።
ወደ ቀጣዩ ገጽ ስምንት የመፅሐፉ ሦስተኛ አንቀጽ አለፍኩ። ስለ ሶሎሜ ይገልፃል። ስለ ሥራዋ። “ሥራ” የሚለው ቃል በ`ርግጥም “ለደራሲው” ዶ/ር ምህረት ደበበ ከባድ ሥራ ሆኖባቸው በ”ሥራ” ለ`ኛም ሥራ ሰጥተውናል።
እዚሁ አንቀጽ ላይ የ”ድኸነት” አና የ”ችግር”ን ቃላት ድግግሞሽ ልብ ይሏል።
ወደ ቀጣዮቹ አራት ሰድስት ሰባትና ዘጠኝ አንቀጻት እናምራ።
እዚህ ላይ ነው ከመፅሀፉ ጋር የተለያየነው … ።
ከወራት በኋላ ከመነሻዬ የገለፅኩትን የአድናቆት ሂስ አነበብኩና በእንዴት ሊሆን ይችላል?!መፅሐፉን እንደገና አንስቼ ከቆምኩበት ለመቀጠል ተገደድኩ። ሞከርኩ አንጂ አልቻልኩም። አለፍ አለፍ አድርጌ ገላለጥኩት። ባለሙያ ያልሆነች ሴት እንደቆላችው ዓይነት ቡና ሆኖ ነው ያገኝሁት። ለማንኛወም ለቀጣዩ የደራሲው ሥራ መታረሚያ ይሆን ዘንድ እጄ ከጣለኝ ገፅ ላይ ያገኝሁትን ግድፈቶች በስሱ እቦርሻለሁ።
የቃላት ድግግሞሹ በከፋ መልኩ አንደቀጠለ ነው።
ገፅ 25፣ 55 እና 247ን ለናሙና እንመልከት።
እንደ እውነቱ ደራሲው ያነሷቸው ጭብጦች ዘርፈ ብዙ ናችው። የገጸ-ባህሪያቸውን ሥነ- ልቦና ጥንፍፍ አድረገው የማወቃቸውን ያህል የተደራሲን የግንዛቤ አድማስ ስፋት ያዩት አይመስሉም። እሳቸው ባሰመሩት እና ባዘነሙት የቃላት ብዛት መጠን ነው ስዕል ቀርፀው ቀልብን መግዛትና አዕምሮን መንደፍ የፈለጉት።
ደራሲ ቃላትን አንደጥይት ከማርከፍከፍ ይልቅ እንደ እርሾ መጥኖ ነው መጠቀም ያለበት። አንባቢ የሚያውቀውን እንዲያስታውስ መርዳትና ያነበበውን በሕሊናው ጓዳ በራሱ መንገድ ቀርፆ መመልከት አንዲችል ነው ማመቻቸት የሚኖርበት። ቃላቶቹ የምናብ ነፃነትን አንዳይጋፉ አድርጎ በመክተብ እያላሰ በልኩ ማጉረስ ግድ ይለዋል። መፅሐፉ ልብ-ወለድ (ፈጠራ) መሆኑን የሚያውቀው አንባቢ ድርጊቱ በ`ውነት እነደተፈጠረ አድርጎ እንዲቀበለው የሚሸነግለው የገዛ ሕሊናው ነው። ምናቡ ከደራሲው ነጥቆ ያመጥቅዋል። በገሃዱ ዓለም ያናኝዋል። ይህ የደራሲውና የአንባቢያን ውህደት ነው መፅሐፉን ሕያው የሚያደርገው። “አንባቢ የደራሲው ረዳት ፅሐፊ ነው።” የሚባለውም ከዚህ አንፃር ነው።
“በ`ኔ ዓይነ-ልቦና ተመልከት!” ብሎ የራሱን የብዕር ጭማቂ ብቻ በደረቁ ለመጋት የሚያስጨንቅ ደራሲ ወረቀት ላይ ከጻፈው ጥቁር ቀለም በቀር ከቶውንም ሌላ ሕይወት ሊያመጣ አይቻለውም።
ዶ/ር ምህረት ደበበ በድርሰታቸው ቁልጭ አድርገው በበቂ ያሳዩንን ክስተቶች እንደገና መልሰው መላልሰው ደግመው ደጋግመው የመግለፃቸው ጭንቀት ምክንያቱ አልገባኝም። ይህ ድካማችው ድርሰታችውን ብቻ ሳይሆን አንባቢንም ሲያደክም በተደጋጋሚ ተስተውሏል።
በገፅ 27
በገፅ 208
በገፅ 156 የሶለንን ህመም ለመግለጽ “የደም መርጋት”ን ረብርበውታል።
ደራሲው አላስፈላጊ ቦታ እየገቡ አላስፈላጊ ማብራሪያና መገለጫዎች ከሰጡባቸው ቦታዎችም ገፅ 19 በዋቢነት ይጠቀሳል። “አባባ አረጋዊን ይዛ ወደ ካፌው ለመግባት ስትሄድ በተረብ የለከፏትን ልጆች ዝም ያስባለላት ወጣት ነበር” የሚለው ሐረግ በግልጽ የሚታይና ወጣቱ በራሱ አንደበት ድርጊቱን ያስታወሳት በመሆኑ እንደገና ማብራሪያ ሊሰጠው ባልተገባ ነበር።
ወደ ሌላ ነጥብ አለፍኩ። ደራስያን አይረሴ ገጽ-ባህርያትን በአንባቢ ሕሊና ለይቶ ለማስቀመጥ ከሚጠቀሙበት ቅመም አንዱ ባህርያቱን ባነጋገር ወይም በድርጊት ይትብሃል መለየት ነው። ይህ የተውሰኑ ቃላትን በንግግራቸው ጣልቃ በማጣፈጫነት አዘውትረው እንዲናገሩ ወይም በልማድ የሚያደርጉትን ነገር እያሰለሱ በመግለፅ ሊሆን ይችላል። በበዓሉ ግርማ “ደራሲው” ላይ ሲራቅ “ሜርድ” የሚላትን ቃል እና የእትዬ አልታዬን ወርቅ ጥርስ፣ በሲሳይ ንጉሡ “ሰመመን” የማርታን “ደረቅ” ብሎ ስድብ የእስክንድርን “እርጥብ” የፌዝ ምላሽ፣ የቤተ-ልሔምን የሽንት ቤት ሩጫን ያስተውሏል።
ከዚህ አንፃር ዶ/ር ምህረት የፈጠሯቸውን ገጽ-ባህሪያት ቃላት በሚገባ የመረጡላቸው አይመሰሉም። የአነጋገር ውርርስ በባለታሪኮቹ መሀል ይስተዋላል። ለአብነት ያህል “ሀሪፍ” የሚለው ቃል የሶሎሜ መለያ ነው። ገፅ 26 አንቀጽ አንድ ላይ ተጠቅማበታልች። ገፅ 40 አንቀጽ 7 ገፅ 41 አንቀጽ 5 ና 7 ላይ ቃሉን አንደ ትኩስ ድንች ከአፏ አልለየችውም። ነገር ግን እዚሁ ገፅ 41 አንቀጽ 9 ይህን ቃል በመላኩ ትነጠቃለች:: ምህረት በመለያነት የሰጧትን ዐርማ ነው መልሰው የበወዙት።
በሶሎሜ “ሀሪፍ” ሲቃኝ የቆየ የጆሮ ታንቡር ድንገት ቃሉ ከመላኩ አፍ ሲፈተለክ ሲሰማ “የማን ድምፅ ነው?” ብሎ ግር መሰኝቱ አይቀሬ ነው። ይሕ አይነቱ ውዥንብር አንባቢው ባለታሪኮቹን አንዲያምታታ የሚጋብዝ ነው። ለነገሩ ሶሎሜ አና መላኩ ንግግራቸው ከመቀላቀሉም በፊትም ሆነ በኃላ ከፆታ ልዩነት በቀር እዚህ ግባ የሚባል መለያ የተበጀላቸው አይደሉም። የመንታ ያህል ነው የሚመሳሰሉት ውብ ፈገግታችው፣ አጠያየማቸው፣ ተክለ-ሠውነታችው ….ተነፃፃሪ ብቻ ሳይሆን አንድ አይነት ነው።
በየምዕራፉ አዳዲስ ባህርያት ስለሚፈለፈሉ ደራሲው ዋናዎቹን መቆጣጠር አልቻሉም። የገፅ-ባህርያቱ ብዛትና የአወጣጥ ፍጥነት ለአስቸኳይ ሰላማዊ ሰልፍ የተጠሩ ነው የሚመስለው። ይህ ከቁጥጥር ውጪ የሆነባቸው ዶ/ር ምህረት በተመሳሳይ ቃላትና ንፅፅር መሪ ባህርያቱን ጨምሮ “ይመስላል፣ ያስመስላታል…” እያሉ ነው የመደዱት።
– ገፅ 56 አንቀጽ 3 መላኩን እንዲህ ይገልፁታል ” …ቀጭን መሆኑ ከሆነው በላይ ረጅም ያስመስለዋል….”
– ገፅ 77 አንቀጽ 3 ሶሎሜን ደግሞ “…ቀጠን ያለው ሰውነቷ የበለጠ ረጅም ያስመስላታል…”
– ገፅ 139 አንቀጽ ስንክሳርን “…ዐንገቷ ረዘም ያለ መሆኑ ቁመቷን ረጅም ያስመስለዋል።”
መስመር ከኔ።
በአንድ ድንጋይ ሦስት ወፍ?! ሥነ- ፅሑፍ ላይ በተለይ በረጅም ልብ-ወለድ አይሰራም። ደራሲ እና ገበሬ አንድ ናቸው። “አደባብሰው ቢያርሱ ባረም ይመለሱ።” … የደራሲ ዕንቁ ሀብቱም ማስተዋሉ ነው።
ወደ ሌላ ነጥብ እንለፍ። አንባቢ ደህና ከታሪኩ ጋር ራሱን እያዋደደ ከመፅህፉ ከርስ እየዳከረ መናኝት ሲጀምር ዶ/ር ምህረት ” በመጨረሻም ፣ ቀጥሎም ፣ ከዚያም ፣ ወዲያውኑ፣ በኃላም፣ እናም …” የሚሉ ረባሽ ቃላትን ሰንቅረው ተመስጦን ሲኮሰኩሱ የተስተዋለበት ግዜ አንድ ሁለት ተብሎ የሚቆጠር አይደለም። ከፍ ብዬ እንደጠቀስኩት ምህረት ለአንባቢ ምናብ ሙሌት መተው የሚገባቸውን ሂሳብ እራሳቸው ቀምረው ሊያወራርዱ ሲሞክሩ የሚሰሯቸው ስህተቶች ናቸው።
በ`ዚህ አና በሌሎች ተዛማጅ ምክንያቶች ደራሲው መፃህፋቸውን ለህትመት ከመላካቸው በፊት ጀማሪ ደራስያን አንድሚያደርጉት በቀደሙ የሙያ ዐውራዎች ቢያስፈትሹ ኖሮ የተሻለ ነገር ይዘውለን ይቀርቡ እንደነበር ጥርጥር የለውም። በመፅሐፉ መግቢያ ምስጋና ያቀረቡላቸው ግለስብ (በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአማርኛ ቋንቋ የሥነ-ፅሑፍ ረዳት ፕሮፌሰር) ረቂቁን ተንተርሰው እንጂ አንብበው እንዳልመለሱላቸው መገመት ይቻላል። አሁንም ቢሆን ጅምራቸው “ሃያሲው” በአመለከቱት ደረጃም ባይሆን ምስጋና የሚያሰጣቸው ነው። እናመሰግናቸዋለን! ዶ/ር ምህረት ደበበ በሚጠሩበት ማዕረግ ወይም የሙያ መስክ እንደተባለው “ሊቅ” ወይም “ፈላስፋ” ሊያስብላቸው የሚችል ጥበብና ዕውቀት ሊኖራቸው ይችል ይሆን ይሆናል። በኢትዮጵያ የስነ-ፅሑፍ ታሪክ ውስጥ ወዳጃቸው ምናልባትም የስራ ባልደረባችው (ዶ/ር ፈቃዱ በቀለ) የደረቡላችውን የወርቅ ካባ ለማጥልቅ ግን በጣም ብዙ ማሻሻያዎችን ማድረግ ይጠበቅባቸዋል። እእአእ…
በግርድፉ የነቀስኳቸውን ድክመቶቻቸውን ለቅመው በማውጣት በቀጣዩ የጥበብ ቡራኬያቸው የተሻለ ሥራ ይዘው እንደሚቀርቡልን እምነቴ ፅኑ ነው።
በአልታዬ ገ/መድህን (altayegmedhin@gmail.com)
“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡
አለም says
ውድ አልታዬ፣
ያልከው ትክክል ነው። አንድ ዋነኛ ችግር፣ ጠንካራና ገለልተኛ አርታኢ አለመኖር ይመስለኛል። የወዳጅ ሃያሲ ደግሞ መጨከን አይሆንለትም፤ ይህ ሲሆን ጉዳቱ ለአገራችን ስነ ጽሑፍ፣ ለደራሲውና በተለይም ለአንባቢው ነው [አንባቢ ያን ሁሉ ወጪ አውጥቶ ሩብ ገለባ የተደባለቀበት እህል ሸምቶ ሲገባ]። ምናልባት ለውጥ ሊመጣ የሚችለው “የሙያ ዐውራዎች”ና ጀማሪ ደራሲያን ትሑት መሆን ሲጀምሩ ነው።
Ali says
You didn’t get it, Alem. Pls read this writing:
https://www.goolgule.com/a-rejoinder-to-alyayes-critique-on-the-key/
አለም says
ውድ አሊ፣
እርስዎና አልታዬ ማን እንደሆናችሁና ከደራሲው ጋር ምን ጉዳይ እንዳላችሁ አላውቅም።
“የተቆለፈው ቍልፍ” እንደታተመ አግኝቼ አንብቤዋለሁ። ብዙ ጥሩ ገጽታዎች አሉት።
ደራሲ ምሕረት የስነ ልቡና ጥበቡን ደህና አድርጎ ተግባር ላይ አውሎታል። ጥሩ አርታኢ ግን አላገኘም
ነው ያልኩት። በመጽሐፉ የሚታዩት ግድፈቶችና አላስፈላጊ ድግግሞሾች ሊወገዱ ይችሉ ነበር።
እርስዎ ለአልታዬ ያቀረቡት ምላሽ ትኵረት ከመጽሐፉ ይዘት ይልቅ ግለሰቡን መወረፍና
[“ድር ያደራበት ብዕርዎትን ከሰገባው ባያወጡት ይሻል ነበር!”] ደራሲውን
መደገፍ ነው። ይህ ደግሞ ከኪነጥበባት ትችትና ግምገማ የተለየ ነው።
ለአልታዬ ያልኩትን ልድገም፦
አንድ ዋነኛ ችግር፣ ጠንካራና ገለልተኛ አርታኢ አለመኖር ይመስለኛል። የወዳጅ ሃያሲ ደግሞ
መጨከን አይሆንለትም፤ ይህ ሲሆን ጉዳቱ ለአገራችን ስነ ጽሑፍ፣ ለደራሲውና በተለይም
ለአንባቢው ነው [አንባቢ ያን ሁሉ ወጪ አውጥቶ ሩብ ገለባ የተደባለቀበት እህል ሸምቶ ሲገባ]።
ምናልባት ለውጥ ሊመጣ የሚችለው “የሙያ ዐውራዎች”ና ጀማሪ ደራሲያን ትሑት መሆን ሲጀምሩ ነው።
Altaye says
ውድ ዓለም… መዝገቡ የዘመኑ ደራስያን የሚሰጡንን እንደ`ኔ ቢጤ ምፅዋት “`ሺ!” ብለን ተቀብለን አንገታችንን ደፍተን ይዘን እንድንሄድ ነው የፈለጉት:: … እሩቡ ገለባ መገለቡ አስቆጥቷቸዋል:: ዓለም እንዳሉት “…የወዳጅ ሃያሲ ደግሞ መጨከን አይሆንለትም፤…” መዝገቡ “ከቲፎዞነትም” ባለፈ መልኩ የደራሲው ባለ ሙሉ ስልጣን አምባሳደር እስኪመስሉ ድረስ (የፈረደበትን የ`ዚያ የበዓሉ ግርማን ስም እያነሱ የሙያ አቻው አድርገውልን) ፅሁፋቸውን እንደ ሙዳይ በቀለም አቀላልመው፣ሽንጣቸውን ገትረው ነው የተከራከሩላችው:: የተባሉት ግድፈቶች ቁልጭ፣ፍንትው ብለው የሚታዩ በመሆናችው አልመለስበትም:: ለቃላት እንካ-ሰላምታ ግዜ ይታክተናል:: የዓምድ ዐርብም ይጠብብናል:: ደግሞም ከምክንያት ጋር እንጂ ከስሜት ጋር ማን ይላፋል?! …መቼም ደራሲው እንደ መዝገቡ ቆዳቸው ስስ አይመስለኝም:: ይማሩበታል:: ይመስለኛል::
….ዓለም ስለመልካም ግንዛቤዎና ሥነ-ፅሑፍ ተቆርቋሪነቶ አመሰግናለሁ::
አልታዬ
Yodite Medhin says
Altaye was one of a great writer at early 80s E.C. next to Asenafi Z Debubu. I Never forget his articles which he contributed to Addis Zemen, Yezaritu Ethiopia, Sunday morning radio, Legedadi too. Where are you Altaye this days p/s show up? It is shameful to ask who you are. We always love you Altaye. You were one of the best Ethiopian writers. You did so on here too. All what you have said was true.