
* ከደመቀ መኮንን ጋር የተበቀ ግንኙነት ያላቸው ባለሃብቶች መመለስ “ከዚያስ” አስብሏል
* ባለሃብቶቹ በፋኖ ስም ለሚንቀሳቀሰው ሚዲያ በሙሉ “ዩኤስኤይድ” ናቸው
በውል የሚታወቁ የጎጃም ባለሃብቶች ከፋኖ ጋር በተያያዘ አስቀድመው ሀገር ለቀው መውጣታቸው ይታወሳል። እነዚሁ ክፍሎች ናቸው ወደ አገራቸው ለመመለስ እንቅስቃሴ ማድረጋቸው የተሰማው። ከቀድሞው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ጋር ጥብቅ ግንኙነት ያላቸው የጎጃም ባለሃብቶች ተመልሶ ወደ አገር ቤት መግባት “ከዚያስ?” የሚል ጥያቄ አስነስቷል። በፋኖ ስም የሚንቀሳቀሰውን ሚዲያ በመደገፍ የሚታወቁትና “የሚዲያው ዩኤስኤይድ” በሚል ቅጽል ስም የሚጠሩት ባለሃብቶች ከተመለሱ የብዙዎቹ የሚዲያ እንቅስቃሴዎች የሚከስም ይሆናል ተብሏል።
ወደ አገር ቤት ለመመለስ እየተንቀሳቀሱ ያሉት ባለሃብቶች ከፋኖ ጀርባ ሆነው በፋይናንስና በሎጂስቲክስ ታጣቂዎችንና ሚዲያዎችን ይደግፉ እንደነበር ይታወሳል። ባለሃብቶቹ በተለይ ከአቶ ደመቀ መኮንን ጋር ጥብቅ ወዳጅ የነበሩና አብረው በመሥራትም የሚታወቁ በመሆኑ ዜናውን እንዲጎላ አድርጎታል።
በሦስተኛ ወገን ግፊትና ትሥሥር በአማራ ክልል ከሁለት ዓመት በፊት የተጀመረውን የፋኖ እንቅስቃሴ ተከትሎ ከአገር የኮበለሉ እነዚህ የጎጃም ባለሃብቶች ወደ አገር ቤት ለመመለስ ፍላጎት ማሳየታቸው በወፍ በረር ሲነገር ነበር።
አሁን ላይ ኢትዮሪቪው እንደዘገበው ባለሃብቶቹ ወደ አገር ቤት የሚመጡበት አግባብ እንዲመቻች ለጊዜው ይፋ ያልሆኑ ወገኖች እየሠሩ ነው። ሆኖም ረብሻውንና ቀውሱን በሚፈልጉት ወገኖች ዘንድ መረጃው የመርዶ ያህል ሆኗል። “ከዚያስ” የሚል ጥያቄም አስነስቷል።
የኢትዮሪቪው ታማኝ የመረጃ ምንጮች እንዳሉት የተጠቀሱት “ዕውቅ” ባለሃብቶች ወደ ሀገራቸው ለመመለስ እንቅስቃሴ ከጀመሩ ሰነባብቷል። ጅማሮው ተስፋ የሚሰጥ ሆኗል። በተቃራኒው ዜናው የክልሉንና የሀገሪቱን ብጥብጥ ለሚፈልጉና ከጀርባ ሆነው ለሚያቀጣጥሉ አስደንጋጭ እንደሚሆን ተመልክቷል።
በስም ከሚታወቁ የጎጃም ባለሃብቶች መካከል ከፋኖ እንቅስቃሴ ጀርባ መሆናቸውን አደባባይ ወጥተው የመሰከሩ መኖራቸው አይዘነጋም። ከፋኖ እንቅስቃሴ ጋር በተያያዘ የሚሠሩ ሚዲያዎችንና በሚዲያው ላይ የሚሠሩትን ወርሃዊ ደሞዝ ከመስጠት ጀምሮ መቋቋሚያ ሲሰጡ የነበሩ መኖራቸውንም በተደጋጋሚ መገለጹ አይዘነጋም።
ኢትዮ 360 ሲመሠረት ዳጎስ ያለ መቋቋሚያ ከሰጡ በኋላ፣ ገንዘቡ ከዱባይ የተላለፈለት አንድ የሚዲያው አባል ገንዘቡን ወደ ራሱ ኪስ ማዞሩን ተከትሎ ከፍተኛ ረብሻ መነሳቱና ጉዳዩ አደባባይ እስከመውጣት መድረሱም የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው።
ባለሃብቶቹ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ መንገድ በተለይ በውጪ ላሉት የማኅበራዊም ሆነ የመደበኛ ሚዲያ አውታሮች የሚያፈሱት መጠነ ሰፊ ገንዘብ “የሚዲያው ዩኤስኤይድ” የሚል ቅጽል ስም በአንዳንዶች ዘንድ ይታወቃሉ።
የአሜሪካው ዩኤስኤይድ መዘጋት በዓለም ዙሪያ ታላቅ መናጋት እንዳስከተለ “የሚዲያው ዩኤስኤይድ” የሆኑት የጎጃም ባለሃብቶች መመለስ ብዙዎቹን የሚዲያውን ኔትዎርክ በጣጥሶ ብዙዎቹን ከጥቅም ውጪ እንደሚያደርጋቸው ይጠበቃል።
በዚህን መሰሉና ቀደም ሲል በኅልውናው ትግል ወቅት ጀምሮ ዝግጅት የነበራቸው አካላትን ሲደግፉ የነበሩት የጎጃም ባለሃብቶች ከሀገር የወጡት በኅቡዕ ሲያከናውኑ የነበረው ድጋፍ በመታወቁ መሆኑም አይዘነጋም።
አሁን ላይ ባለው ተጨባጭ ሁኔታ የሀገሪቱን ፖለቲካ በመገምገም ባለሃብቶቹ በምህረት ወደ አገራቸው ገብተው በሰላማዊ መንገድ ለመሥራት ከውሳኔ መድረሳቸው ተሰምቷል። ሁሉም ይሁኑ የተወሰኑት ባይገለጽም በዚሁ ውሳኔያቸው መሠረት ጉዳይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር እንዲደርስ ዕቅድ መያዙን የዜናው ባለቤቶች ነግረውናል።
ካለፉት ሁለት ዓመታት ጀምሮ በሰላም ከሚኖርበት መንደሩ ሳይቀር ሁከት፣ ዝርፊያ፣ ግድያ፣ እገታ፣ የማዳበሪያ አቅርቦት፣ ሕክምና፣ ትምህርት ቤት፣ ማኅበራዊ አገልግሎት፣ የትራንስፖርት አቅርቦት፣ የሸቀጦች ፍሰት ወዘተ ለተናጋበት የአማራ ሕዝብ ዜናው በጎ ነገሮችን ይዞ እንደሚመጣ ዜናውን ያካፈሉን አስታውቀዋል።
እንደ እነዚሁ ሰዎች ገለጻ ከሆነ የባለሃብቶቹ መመለስ ብረት ባነሱትና ብረት ያነሱትን ተቧድነው በሚደግፉ ሚዲያዎች አማካይነት የሚሰራጨውን ብጥብጥ የሚያባብስ አካሄድ ያስተነፍሳል። ምን አልባትም የተወሰኑትን ሊያቆማቸው ይችላል። ከምንም በላይ ግን በአገር ውስጥ ይህ ነው ሊባል የማይችል እፎይታ እንደሚፈጥር ገልጸዋል።
በአማራና ኦሮሚያ ክልል ያለው የትጥቅ ትግል ፖለቲካዊ ግብ የሌለው የንግድ ጉዳይ እንደሆነ፣ በርካቶች “ትግል” የሚባለውን አግባብ ለገንዘብ መሰብሰቢያ የሚጠቀሙበት መሆኑ በስፋት እየተገለጸና እየታመነበት መምጣቱን በርካታ ሰለባዎች እያስታወቁ ነው። የሰላማዊ ሰዎችን ህይወት ጭምር እየበላ ያለው ውጊያ ሕዝቡን ክፉኛ ያሰላቸው መሆኑም በተለያዩ መድረኮች በተደጋጋሚ እየተገለጸ ይገኛል።
በአንዳንድ ሕዝባዊ ስብሰባዎች ላይ ሕዝቡ “አሁንስ የት እንሂድ?” በማለት መንግሥትን ሲማጸን መስማት የተለመደ ሆኗል። እነዚህ ዜጎች በየአቅጣጫው “የሰላም ያለህ” እያሉ በሚያነቡበት ወቅት የጎጃም ባለሃብቶች ወደ አገራቸው ለመመለስ ያሳዩት ተነሳሽነት ሊደገፍና በአስቸኳይ ዕልባት ሊያገኝ እንደሚገባው ዜናውን የነገርናቸው ገልጸዋል።
አሁን ላይ መቀንጨርን ዜሮ ለማድረግ “የአዳም” በሚል ድርጅት የከፈቱት፤ ከኢሳት የተወሰኑ ጋዜጠኞች ጋር ከበፊት ጀምሮ ግንኙነት የነበራቸው፣ ከኃላፊነታቸው እስከ ለቀቁበት ቀን ድረስ የዝግ ስብሰባዎችን ምሥጢር በማሾለክ የሚጠረጠሩት አቶ ደመቀ መኮንን ይህን ዜና በምን መልኩ እንደሚመለከቱት ለጊዜው የታወቀ ነገር እንደሌለ የዜናው ሰዎች ገልጸዋል።
እነዚሁ አካላት አቶ ደመቀ አማራ ክልልን በፓርቲው መሪነትና በጸጥታ (የደኅንነት) ዘርፍ ለረዥም ጊዜ የመሩና የክልሉ መዋቅር ሙሉ በሙሉ እጃቸው ላይ የነበረ መሆኑን የሚገልጹት የዜናው ሰዎች፣ እሳቸው ከጎጃም ባለሃብቶች ጋር ከነበራቸው የጠበቀ ግንኙነት አንጻር አማራ ክልል አሁን ለደረሰበት ቀውስ እንዳይጋለጥ ማድረግ ይችሉ እንደነበር ይገልጻሉ።
እነዚህ ወገኖች ብቻ ሳይሆን በርካታ የክልሉ ነዋሪዎችና የራሱ የክልሉ ባለሥልጣናት ይህን እውነት ይጋራሉ። ዜናውን ያጋሩን እንደሚሉት አቶ ደመቀ አሁን ላይ ስለተጀመረው እንቅስቃሴ ምንም የሚያውቁት ነገር፣ ወይም እጃቸው የሌለበት መሆኑን ቢጠቅሱም ራሳቸውን ለመከላከል ሲሉ ምን አልባትም ደስተኛ ሊሆኑ እንደማይችሉ ከሃብት ጋር አያይዘው ገልጸዋል። ዝርዝሩን ወደፊት እንደ አስፈላጊነቱ እንደሚያቀርቡ አመላክተዋል።
አቶ ደመቀ በሽልማት አሸኛኘት እንደተደረገላቸው አይዘነጋም። (ኢትዮሪቪው)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ


የሃገራችን ችግር ውስብስብ ነው። ኑሮ ያስመረረው፤ ሥራ ጠፍቶ ታጣቂ የሆነ፤ ስልጣን ናፍቆ አይ አይሆንም የተባለው ኸረ ስንቱ እያኮረፈና እያስኮረፈ የዚህ ብሄር ነጻ አውጭ የዚያ ሥፍራ እንባ ጠባቂ እያለ ሲቃጅ ማየትና መስማት ልብን ያደክማል። ዓለም በሩን በስደተኛ ላይ እየዘጋና አትምጡብኝ በማለት ሰላማዊ ሰልፍ እያደረገ ባለበት በዚህ ወቅት ሁሉን ነገር በሰላምና ለሰላም ሲባል በሰከነ መልኩ አይቶና ፈትሾ በይቅርታ አብሮ እንደመኖር ሁሌ ጠበንጃ አንግቦ እንዘጥ እንዘጥ ማለት የውድቀት ምልክት እንጂ ጀግንነት አይደለም።
27 ዓመት ወያኔ በጅምላ ሲነዳው ዝም ብሎ የተነዳው ሁሉ አሁን ኑ አብረን እንስራ ሲባሉ እንደ ተልባ ስፍር በዚህም በዚያም እየተንሸራተቱ ሃገር ማመስ ለማንም አይጠቅምም። አንድ መንግስት የሚመዘነው በቃሉ ሳይሆን በተግባሩ ነው። ጠ/ሚሩ ወደ ስልጣን ከመጣ በህዋላ አያሌ ነገሮች በአጭር ጊዜ ውስጥ ተገብተዋል። ግን አይኑን ጨፍኖ ዓለም ሁሉ ገደል ሆኗል ብሎ ለሚያምን ሰው መራመድ ችግር ነው። አይቶ መፍረድ የለምና። ሰው እንዴት የሰራውን በጎ ነገር ተመልክቶ ማሞገስ፤ በርታ፤ በርቱ ማለት ይሳነዋል። ግን በዘርና በቋንቋው ተሳክሮ ብሄሩን ተገን አርጎ ባሩድ ሲያሸት ለሚውል የሙታን ስብስብ ገድሎ ከመሞት፤ አፍርሶ ከመዝረፍ ሌላ የሚታየው ምንም ነገር የለም። ጊዜው ሰላም በጦር መሳሪያ የሚመጣበት አይደለም። ትላንት ቀበሮ ጉድጓድ ውስጥ ተደብቆ ከጠላት ያመልጥ የነበረው ተፋላሚ ዛሬ በድሮን ባለበት እንዲሰናበት ይደረጋል። በዪክሬንና በራሺያ ፍልሚያ እያየን ያለነው ይህኑ ነው። የሶስት ወራቱ የራሺያ የጦርነት እቅድ ሶስት ዓመት ዘለለው። በዚህ ጊዜ ውስጥ ስንቱ ሞተ/ተሰደደ/ተደረመሰ…. ቤቱ ይቁጠረው። ፓለቲካ አቅጣጫ የሌለው ነፋስ ነው። ያኔ ሻቢያንና ወያኔን ያግዙ የነበሩት እነ ኢራቅ/ሊቢያ/ ሶሪያ/ሱዳን/ሶማሊያ ወዘተ.. ዛሬ ያሉበትን ልብ ብሎ ለተመለከተ “What goes around comes around” የሚለውን የፈረንጆችን አባባል ትርጉም ይሰጠዋል። ያው እኮ የእኛ አባቶችም አሳምረው አስቀምጠውታል። “በሰፈሩት ቁና መሰፈር አይቀርም” የኢትዮጵያን መፍረክረክ ማየት የናፈቁ ሁሉ ራሳቸው ተበትነዋል። ገናም ይበተናሉ! ኢትዪጵያ ግን እየተውተረተረችም ቢሆን አሁንም ቆማ ትገኛለች!
ባጭሩ የጎጃም ባለሃብቶች በሃገሪቱ ልማትና እድገት ላይ ቢያተኩሩ መልካም ነው። የትጥቅ ትግል የሚባል የጅሎች አስተሳሰብ ጊዜ ያለፈበትና የሻገተ በመሆኑ የወጣውን መክሮ፤ የከፋውን አይዞህ ብሎ ሰው ተባብሮ በሰላም እንዲኖር ህግና ደንብን ለማስከበር መጣር ነው። በሌላ መልኩ የሃገሪቱ መሪዎችና አስተዳዳሪዎች በጎ ነገር ሲያደርጉ በርቱ፤ ደግሞ ሲያጠፉ ተው ማለት ተገቢ ነው። የጠ/ሚሩ መንግስት በእነዚህ አጭር አመታት ያደረጋቸውን በጎ ነገሮች መርምሮ ማለፊያ ሥራ ሰርተሃል በዚህ በኩል ደግሞ እንዲህ ቢሆን መልካም ነው ማለት የመሸነፍ ምልክት አይደለም። የተቃዋሚ ጎራውን ሁሌ ተሸናፊ የሚያደርገው በጅምላ ሁሉን ጥላሸት እየቀቡ ዓለም ሁሉ ጠንብቷል ማለታቸው ነው። እስቲ ሌላው ይቅር በአረንጓዴ አሸራው የተተከሉ እጻዋት ጸድቀው ማየት ደስ አያሰኝም? የአባይ ግድብ መጠናቀቁ ሃገሩን ለሚወድ ኩራት አይሆንም? በዚህ ምድር ላይ በቀረን ጊዜ ባለሃብትም ሆነ ሌጣው ድሃ ለሰላም መስራቱ ለራስም ለሃገርም ጥቅም ነውና ድርጊታችን ሁሉ ለሰላም ዘብ መቆም ይሁን። ሌላው ሁሉ ለወፎች የሚበተን እንክርዳድ ነው!