• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ግልጽ ደብዳቤ፦ ለኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ)

December 27, 2017 02:10 pm by Editor Leave a Comment

ጉዳዩ፦ በቂሊንጦ እሳት ሰበብ ስለታሰሩት ሰዎች የተደረገውን ምርመራ በተመለከተ

እንደሚታወቀው ኢሰመኮ በቀን 20 ጥቅምት 2010፣ በደብዳቤ ቁጥር ሰመኮ/2.1/29/2010 እንደገለጸው ነሐሴ 1/2008 አዲስ አበባ ማረሚያ ቤት (ቂሊንጦ) ግቢ ውስጥ የተነሳውን እሳት መንስዔ ለማጣራት በተደረገው ምርመራ አሰቃቂ የመብቶች ጥሰቶች ተፈፅመዋል። በእነ መቶ ዐለቃ ማስረሻ ሰጤ መዝገብ (38 ተከሳሾችን) በተመለከተ መንግሥት ባለበት አገር ይፈፀማሉ ተብለው የማይጠበቁ የጥፍር መንቀል፣ በሚስማር ሰውነት የመብሳት፣ ግርፋት እና የመሳሰሉት አካላዊ ጉዳት የሚያደርሱ፣ ሰብኣዊ ክብርን የሚያዋርዱ የጭካኔ ተግባራት በተያዙ ሰዎች ላይ ተፈፅሞባቸዋል። ይሄ ሁሉ የሆነው ፍርድ ቤት በአደራ እንዲጠብቃቸው ያስረከበው የቂሊንጦ ማረሚያ ቤት ኃላፊነቱን ባለመወጣቱ ነው። ሆኖም፣ ዋነኞቹ የምርመራው (ወይም በትክክለኛ አገላለጽ የማሰቃየት ተግባሩ) በፖሊሶች የተፈፀመ መሆኑን ታራሚዎቹ ለፍርድ ቤት በተደጋጋሚ ገልጸዋል።

ኮሚሽኑ ከላይ በጠቀስኩት ሪፖርቱ ያካተተው በተለይ በአንድ መዝገብ ከተከሰሱት 38 ሰዎች ውስጥ የ16ቱን ብቻ ነው። በዚህ ጉዳይ ላይ ተከሳሾቹ በጻፉት አንድ ደብዳቤ ላይ የኮሚሽኑ ሪፖርት «1ኛ) የተፈፀመብንን ኢሰብአዊ ድርጊት ሙሉ ለሙሉ አላካተተም፣ 2ኛ) የማሰቃየት ተግባር የፈፀሙብንን አካላት ለሕግ እንዲቀርቡ በመጠየቅ ፈንታ የተለሳለሰ ‘ምክረ ሐሳብ’ ማስቀመጡ አግባብ አይደለም፣ 3ኛ) የደረሰብንን የማሰቃየት ተግባር የፈፀሙብን የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን እና የሕክምና ቡድን አባላት እንዲያጣሩ ማዘዙ ‘ኢሰመኮ መልሶ አሳልፎ ለነሱ ሰጥቶናል’ በሚል ቅር እንድንሰኝ አድርጎናል» በማለት ቅሬታዎቻቸውን ከገለጹ በኋላ፣ ሪፖርቱ በምርመራ ወቅት በግዳጅ እንዲያምኑ የተደረጉትን የሐሰት ውንጀላ ለመከላከል ስለሚረዳቸው ኮሚሽኑን አመስግነዋል። በተጨማሪም፣ ተከሳሾቹ ታኅሣሥ 6፣ 2010 ሪፖርቱን በተመለከተ አስተያየታቸውን እንዲሰጡ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት፣ ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በቀረቡበት ወቅት በኮሚሽኑ እምነት በማጣት እና “የሰብአዊ መብቶች ጥሰት ላደረሱባቸው ሰዎች መረጃውን የሚሰጡባቸው ስለመሰላቸው” የደረሰባቸውን ሰብአዊ መብት ጥሰቶች ሳይናገሩ የቀሩ ተከሳሾች እንዳሉ ተናግረዋል። በተጨማሪም በክስ መዝገባቸው ላይ የከሳሽ፣ ፌዴራል ዐቃቤ ሕግ ምስክሮች ሆነው እየቀረቡ ያሉት ራሳቸው እስረኞች መሆናቸውን ገልጸው “እነርሱም ሊመሰክሩብን የተስማሙት በድብደባ ብዛት ነው እና የመብቶች ጥሰት ማጣራት ምርመራው እነሱንም መጨመር አለበት” የሚል ጠቃሚ ምክር ሰጥተዋል። ኮሚሽኑ ገጽታውን ለማስተካከልም፣ ሕጋዊ ኃላፊነቱንም ለመወጣት ሲል ምርመራውን አጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል።

በእርግጥ ይህንን ዓይነቱን የምርመራ ሪፖርት ማዘጋጀት የኮሚሽኑ ሥራ ቢሆንም፣ ሕዝባዊ አመኔታን ካጣው ኢሰመኮ ያልተለመደ ውጤት በመሆኑ በዚህ የተሻለ ሪፖርቱ እኔም መደሰቴን እገልጻለሁ። ይሁን እንጂ፣ ይህንን ግልጽ ደብዳቤ የጻፍኩት፣ ሪፖርቱ ውስጥ የተጓደሉት የመብት ጥሰቶች ተሟልተው፣ አስቸኳይ ፍትሐዊ እርምጃ ለእነዚህ መብቶቻቸው እና ሰብአዊ ክብሮቻቸው የተገፈፉ ዜጎች እንዲሰጥ ግፊት በማድረግ ኮሚሽኑ ሕዝባዊ እና ሕገ መንግሥታዊ ኃላፊነቱን እንዲወ:ጣ ጥሪ ለማድረግ ነው።

ኢሰመኮ መጋቢት 27 ቀን 2009 ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግ፣ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የቃጠሎውን መንስዔ እና ጉዳት አብራርቷል። በዚህ ወቅት የቃጠሎው ዋነኛ መነሻ ከቃጠሎው አንደ ቀን በፊት የቤተሰብ ምግብ እንዳይገባ መከልከሉን ተከትሎ የተከሰተው አድማ እንደሆነ ይገልጻል። ይሁን እንጂ በዕለቱ የቀረበው ሪፖርት እንደሚለው ለአድማው ቀድመው ሲዘጋጁ የነበሩ ሰዎች አሉ። ኮሚሽኑ እዚህ መደምደሚያ ላይ የደረሰው የማረሚያ ቤቱን ኃላፊዎች እና በቃጠሎው ወቅት የነበሩ የጥበቃ አባላትን በመጠየቅ ነው። ይሄ ጉዳይ ኃላፊዎቹ እና የፀጥታ ኃይሉ ለደረሰው ጉዳት ተጠያቂ ላለመሆን የሚሰጡት ሰበብ አስባብ መሆኑን መረዳት ቀላል ነው። ኮሚሽኑ እንዳረጋገጠው በወቅቱ ምንም መሣሪያ ባልያዙ ታራሚዎች ላይ የጥበቃ አባላት ከውጭ ወደ ውስጥ መተኮሳቸው ተገልጿል። በዚህም በሕግ መጠየቅ ያለባቸው አካላት እንዳሉ በኮሚሽኑ ቢገለጽም እስረኞቹ የሁሉንም ዕዳ እንዲከፍሉ ተፈርዶባቸዋል።

በቃጠሎው ጉዳይ ከ150 እስረኞች በላይ መታሰራቸው ይታወቃል። ይሁን እንጂ እኔ በተለይ የምከታተለው በሽብር የተከሰሱትን 38 እስረኞች ጉዳይ ነው። የእነርሱ ክስ የሚለው ከቃጠሎው ወራት በፊት አድማውን ለሽብር ተግባር አቅደውታል ቢሆንም በቂ ማስረጃ እስካሁን አልቀረበም። ተከሳሾቹ የቂም በቀል መወጫ እና የማረሚያ ቤቶች ኃላፊነታቸውን አለመወጣት ለመሸፈን ሲባል ሰለባ እየሆኑ ነው ያሉት። ከነዚህ ውስጥ ቢያንስ ሦስቱ (ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ፣ አግባው ሰጠኝ እና ሚስባሕ ከድር) ከቀድሞው ክሳቸው ነጻ በመውጣታቸው መፈታት ነበረባቸው። እነዚህ ሰዎች በነጻ በመፈታታቸው በፊት የተጠረጠሩበትን ነገር አልሠሩም ማለት ነው። ስለዚህ አግባብ ባልነበረው ክሳቸው ምክንያት ባይታሰሩ ኖሮ ለዚህ ክስ አይዳረጉም ነበር። ከነርሱም በተጨማሪ፣ ሌሎችም የቀድሞ ክሳቸውን ፍርድ ታስረው በመጨረሳቸው አባሪዎቻቸው ተፈትተው ከቤተሰባቸው ሲቀላቀሉ ያልተፈቱ ተጠርጣሪዎችም አሉ።

ስለሆነም፣ ኢሰመኮ የነዚህን ተከሳሾች ኢፍትሐዊ አያያዛቸውን፣ የደረሰባቸውን የሰብአዊ መብቶች ጥሰት በመረዳት የሚከተሉትን እርምጃዎች እንዲወስድ በአንድ የዜጋ ድምፄ እጠይቃለሁ፦

1ኛ፣ ተጨማሪ የመብቶች ጥሰት ምርመራ በጉዳተኞቹ ላይ እና በእነሱ ላይ እንዲመሰክሩ በተደረጉት እስረኞች ላይ እንዲደረግና ለሕዝብ እንዲገለጽ፣

2ኛ፣ በሠላማዊ ዜጎች ላይ ጥይት የተኮሱ የጥበቃ አባላት ላይ ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድ ተጨማሪ ምርመራ በማድረግ የተገኘውን የምርመራ ማስረጃ ለፌዴራል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ እንዲያደርስ እና ጉዳዩ ፍትሕ እንዲያገኝ ግፊት እንዲደረግ፣

3ኛ፣ በምርመራ ወቅት ተከሳሾች ላይ የማሰቃየት ተግባር የፈፀሙ የመንግሥት አካላትን በአስቸኳይ አጣርቶ ለፌዴራል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ በማቅረብ በሕግ እንዲጠየቁ እንዲደረግ፣

4ኛ፣ ትክክለኛው የቃጠሎው መንስዔ የማረሚያ ቤቶቹ ብልሹ አስተዳደር ያስቆጣው የእስረኛ አያያዝ ስለሆነ ክሱ ተቋርጦ የእርምት እርምጃ እንዲወሰድ ኮሚሽኑ ግፊት እንዲያደርግ እጠይቃለሁ።

በተጨማሪም ኮሚሽኑ በፖሊስ ምርመራ ወቅት እና በየማረሚያ ቤቶቹ ውስጥ የሚደርሱ የመብቶችን መተላለፍ እና የማሰቃየት ተግባሮችን ለማስቆም እንደመልካም አጋጣሚ በመውሰድ ይህንን ጉዳይ በልዩ ሁኔታ እና ትኩረት እንዲከታተለው እጠይቃለሁ። ይህንን በማድረግ ኢሰመኮ ከሕዝብ ያጣውን አመኔታ ከመመለስም ባሻገር፣ ሕገ መንግሥታዊ ግዴታውን መወጣት ይችላል።

ከሠላምታ ጋር
በፍቃዱ ኃይሉ
ከሕግ አክባሪ ዜጎች አንዱ


“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ። ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ™ አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው።

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: Law, Opinions Tagged With: ehrc, eprdf, Ethiopia, human rights, kilinto, meles, Right Column - Primary Sidebar, tplf

Reader Interactions

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የሲኖዶሱ ውዝግብ አካሄድና መጪው የአፍሪካ ኅብረት ጉባዔ February 6, 2023 02:03 am
  • የእሁዱ ሰላማዊ ሰልፍ ተራዘመ፤ ተጠባቂው ዕርቅ ፍንጭ እያሳየ ነው February 3, 2023 05:17 pm
  • የብላቴ: የውጊያ ማርሽ ቀያሪ ሠራዊት መፍለቂያ ማዕከል February 3, 2023 10:06 am
  • በኢትዮጵያ 27 በመቶ የሚሆነው የአእምሮ በሽተኛ ነው ተባለ February 3, 2023 09:47 am
  • “አስደንጋጭ”! 1 ሚሊዮን ከሚጠጋ ተፈታኝ ተማሪ ወደ ዩኒቨርሲቲ የሚገባው 30 ሺህ (3.3%) ብቻ ነው  January 27, 2023 09:11 am
  • የማይዘነጋዉ የኢትዮጵያዊያኖች የጀግንነት ተጋድሎ ታሪክ፡- ኮሎኔል ባጫ ሁንዴ (ታጠቅ) January 27, 2023 06:12 am
  • ጎርጎራ – የመጻዒው ዘመን ሙሽራ! የዉበት ፈርጥ! January 17, 2023 04:18 pm
  • ሁለተኛው መስቀል አደባባይ January 17, 2023 04:13 pm
  • በአቡዳቢ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን January 17, 2023 04:08 pm
  • በንፋስ ስልክ ላፍቶ ስምንት የመሬት ሌቦች ተያዙ January 16, 2023 11:36 am
  • ሺሻ ሲያስጨሱ በተገኙ ሆቴሎችና የምሽት ጭፈራ ቤቶች ላይ እርምጃ ተወሰደ January 16, 2023 08:50 am
  • በሐሰተኛ መታወቂያ የደኅንነት አባል ነን ብለው ሲያጭበረብሩ የነበሩ ተያዙ January 13, 2023 02:03 pm
  • ተሽከርካሪ ወንበር ለትግራይ – “ናይ ኣካል ጉዱኣት ተሽከርካሪ ዘለዎ ወንበር” January 12, 2023 07:17 pm
  • የአማራው ኩራት፣ የኢትዮጵያ ዘብ፣ የትህነግን ቅስም ሰባሪ! January 12, 2023 04:00 pm
  • በኢትዮጵያ ላይ የተጣሉ ማዕቀብ እና ሌሎች አስገዳጅ ሕጎች ሙሉ ለሙሉ ተሰረዙ January 12, 2023 01:52 pm
  • የቻይና ዕዳ ስረዛ “Payday Loan Diplomacy” ወይስ ኢትዮጵያን ያዳነ ተግባር? January 12, 2023 11:00 am
  • የአዲስ አበባ አስተዳደር ከቋንቋ ጋር በተያያዘ ውሳኔ አስተላለፈ January 12, 2023 10:46 am
  • “አምባሳደሩ” የቀድሞ ጌቶቻቸውን እንዲያቋቁሙ ተሾሙ January 11, 2023 03:47 pm
  • መከላከያ ሸኔን የሚዋጉ ሚሊሻዎችን አሠልጥኖ አስመረቀ January 10, 2023 05:37 pm
  • በሰባት ተጠርጣሪዎች ላይ ከባድ የሙስና ወንጀል ክስ ተመሰረተ January 10, 2023 03:36 pm
  • የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አቅጣጫ January 6, 2023 03:26 pm
  • “ከዕብሪቱ አስተንፍሰነዋል” – ኢሳያስ January 2, 2023 07:29 pm
  • [ኢትዮጵያን] “አስታክኮ ኤርትራን መውጋት ለሚፈልግ ኃይል አንተባበርም” January 2, 2023 07:11 pm
  • የ፰ ወር ሕጻንና ጨቅላ ወንዶች የሚደፈሩባት ትግራይ December 14, 2022 02:49 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2023 · Goolgule