
በአሜሪካ የኦሃዮ ጠቅላይ ግዛት ሴናተር የሆኑት ሪፓብሊካኑ በርኒ ሞሬኖ ጣምራ ዜግነት እንዲቀር ለሕግ መወሰኛው ምክር ቤት Exclusive Citizenship Act of 2025 በሚል ርዕስ ረቂቅ ሕግ አቅርበዋል። አዋጅ ሆኖ ከጸደቀ ዜጎች በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ የሚፈልጉትን እንዲመርጡ ይደረጋሉ።
አሜሪካ በስደተኞች የተመሠረተች አገር እንደመሆኗ የኢሚግሬሽን ሕጓ ከአውሮጳውያኑ በተለየ ለስደተኞች የሚያደላ ነው። ለምሳሌ አሜሪካ መጥቶ ጥገኝነት የጠየቀ ሰው ጉዳዩ ከጸደቀለት ከአምስት ዓመት በኋላ ዜጋ መሆን ይችላል። በአሜሪካዊ ዜግነቱ ከሌላ ሀገር ሚስት ቢያመጣ አሜሪካዊ ስላገባች በሚል እሷ በሦስት ዓመት ዜጋ መሆን ትችላለች። ጉዳዩ ሳያልቅለት ወይም ሕጋዊ ሳይሆን ቢቀርና በመካከል ግን ልጅ ቢወልድ ልጁ ዜጋ ይሆናል።
ዜግነትንም በተመለከተ ጣምራ ዜግነት በሕግ የሚፈቀድ ባይሆንም በጥብቅ የተከለከለ ግን አይደለም። በሚሊዮን የሚቆጠሩ የአሜሪካ ዜግነትን የወሰዱ ሰዎች የሀገራቸውንም ፓስፖርት እንደሚጠቀሙ ይታወቃል። በዚህ ረቂቅ ሕግ መሠረት ግን ይህ እንዲቀር ነው የተጠየቀው። በሁለት ፓስፖርት መጠቀም አይቻልም ነው ረቂቅ ሕጉ የሚለው።
ጥያቄውን ያቀረቡት ሴናተር በርኒ ሞሬኖ በትውልድ ኮሎምቢያዊ ሲሆኑ በ፲፰ ዓመታቸው ነበር አሜሪካዊ ዜግነትን ያገኙት። ለውሳኔ ስላቀረቡት ሕግ ሲናገሩ ዕዕዕየታማኝነት ጉዳይ ነውዕዕ ይላሉ። በመሆኑም አሁን ያቀረቡት ረቂቅ ሕግ ዜጎች አሜሪካዊ ከሆኑ የሌላ አገር ዜጋ በፍጹም መሆን እንደማይችሉ በግልጽ ያስቀመጠ ነው። ለሁለት ጌታ መገዛት አይቻልም የሚልም እንደምታ አለው።
በአሜሪካ ምን ያህሉ ዜጋ ጣምራ ዜግነት እንዳለው ባይታወቅም፤ ከአስር እስከ ሃያ ሚሊዮን የሚሆነው ጣምራ ዜጋ እንደሆነ ይገመታል። አንዳንዶች ግምቱን እስከ አርባ ሚሊዮን ያደርሱታል። በዚህም ምክንያት ረቂቅ ሕጉ አይጸድቅም የሚል አስተያየት ይሰጣሉ። ለአብነትም የሦስት አገር (አሜሪካ፣ ደቡብ አፍሪካና ካናዳ) ዜግነት ያለውን ባለሃብቱን የቴክ ሰው ኤሎን መስክን ያነሳሉ። ሕጉ ከጸደቀ እንደ መስክ ያሉ ሰዎችን ከጨዋታ ውጪ ያደርጋቸዋል ይላሉ።







ሌላው የጣምራ ዜጋና ባለሃብት ጀርመናዊው ፒተር ቲይል ነው። በመዝናኛው ኢንዱስትሪ ውስጥ የታወቁ ሰዎች ጣምራ ዜግነት ያላቸው ሲሆን ቶም ሐንክስ (ግሪክ)፣ ሳልማ ሃዬክ (ሜክሲኮ)፣ ናታሊ ፖርትማን (እስራኤል)፣ አርኖልድ ሽዋዝኒገር (ኦስትሪያ)፣ ወዘተ ጥቂቶቹ ናቸው።
የፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ባለቤት ሜላኒያ ትራምፕ ከአሜሪካዊ ዜግነታቸው በተጨማሪ የስሎቬኒያ ተወላጅ እንደመሆናቸው የጣምራ ዜግነት ባለቤት ናቸው።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ



Leave a Reply