
አንደ ሻማ ነው ማንባት፣
ቀልጦ ጠብ እንደሚለው፤
የነፍሳችንን ስቃይ፣
ይሉኝታ ሳይጋርደው፤
ማስመሰል ሳያርቀው፡፡
እንደ ሻማ ነው መቅለጥ፣
በነበልባል ነዶ በግኖ፤
ሰብእናን በህይወት ጣር፣
ሰርቶ በማደር ፈትኖ፡፡
እንደ ሻማ ነው መብራት፣
ማለቅም እንደ ሻማ፤
ለሌላም ባይሆን ለነፍስ፣
አብርቶ የእውነትን ፋና፡፡
በድሉ ዋቅጅራ (ዶ/ር) ፣ /ፍካት ናፋቂዎች፤1999ዓ.ም/
ባለፈው ሁለት ግጥሞችን አቅርበን ነበር፡፡ “ቅኔ” እና “የማይጠፋ ፍቅር” በሚል ርዕሶች ለቀረቡት ግጥሞች ጨዋታውን በማድመቅ የተቀኛችሁትን እና ማብራሪያም የሰጣችሁትን ተሳታፊዎቻችንን በለው፤ YeKanadaw Kebede፤ አሥረዳው፤ እስከመቼ እና ዱባለ ልባዊ ምስጋናችን ይድረሳችሁ፡፡
ለዛሬው ደግሞ በግጥም ልተንፍሥ ከተባለ የፌስቡክ ገጽ ይህንን ግጥም አግኝተን ለጨዋታ አቅርበነዋል፡፡ “እንደ ሻማ”ን እነሆ! ተቀኙበት፤ ቅኔ ዝረፉበት፤ …
*************************
አይ አንቺ ‘ሻማ’ እራስሽን መስዕዋት ያደረገሽ
መብራት በጠፋ ቀን ሁሉ የሚያበሩሽ
እነሱ ሲደሰቱ አንቺን እየለኮሱሽ
ሀዘንም ሲገጥማቸው አንችው ተቃጥለሽ
ከቶ ማነው አንቺ ቀልጠሽ! አንብተሽ!
ለሌላውን ብርሃን ሁኚ ብሎ የፈረደብሽ ?
***ሻማ !
ምን ነበር ታዲያ ከአንቺ የሰው ልጅ ቢማር
ውጭ ሄዶ ከሚቀልጥ ከሚያነባ ከሚማረር
እንዳይሆን የጋን መብራት እንዳይጠፋ ሳያስተምር
እንደሻማ ተለኩሶ በርቶ እየታየ ለህዝብ ቢናገር
ስንት የጨለመባቸው ፍንትው ብሎ በታያቸው ነበር !!።
*****************
ከምስጋና ጋር፣ ከሀገረ ካናዳ በለው!
“እንደ ሴቴ ሸረሪት ጽንስ
ራሴን በራሴ መዋጤ”
የገዛ ብርሃኔን አስኳል
እኔው በእኔው መሰልቀጤ፡
ፍቅር ቢፈልቅ ብዬ እኮ ነው
ከአለት ልብህ አንዳች ጥጋት
ጀንበር ቢቀድ ብዬ እኮ ነው
በልቦናህ የጎህ ንጋት፡
አንተም ታዲያ ሲደርስ ቀኑ
ሻማ እንድትሆን ለጭቁኑ
ለድምፅ አልባው ለምስኪኑ!
ጧፍ እንድትሆን ልክ እንደኔ
አፍ እንድትሆን ለወገኔ፡፡
( ለእስክንድር ነጋ)
እንደ ሻማ ቀልጦ ብርሀን መስጠት
ራስን ሰውቶ መሆን ትሩፋት
ጀግና መሆን በጎ ለሁሉም በረከት
የሰው ልጅ ምሳሌ መሆን በትጋት
ለግለሰብ ኣቅም ይሰጣል ብርታት
ለብዙሀኑ ግን ስንፍና ያወርሳል
የግል ሀላፊነት እኋላ ይቀራል
የራሱን እጅ ኣጥፎ የሌላውን ያያል
ለዚህ የሚበጀን ችቦ መሆንን ነው
እንጨትን ሰብስቦ በልጥ ማያያዝ ነው
ሁሉም የየራሱን መሀል መቆለል ነው
የራስን ለኩሶ ሌላ ማቀጣጠል
ብርሀን ያበዛል
ደስታውም ይደምቃል
ዘላቂም ይሆናል
ችግር ይቀረፋል
ሸክምም ይቀላል::