
የአርሲ ዞን ሙኔሣ ወረዳ የእስልምና እምነት ተከታዮች ለኦርቶዶክስ ሃይማኖት ተከታዮች ቤተክርስቲያን ማሠሪያ 3 ሚሊዮን ብር እና 20 የቀንድ ከብቶች አሰባስበው አበርክተዋል።
በወረዳው የእስልምና እና የክርስትና እምነት ተከታዮች ለዘመናት በመከባበር እና በመቻቻል በፍቅር አብረው እየኖሩ መሆኑን የሁለቱ ሃይማኖቶች ተከታዮች ገልጸዋል።
የሁለቱም እምነት ተከታዮች አንዳቸው ለሌኛው በየተራ መስጂድ እና ቤተክርስቲያን ተባብረው እያሠሩ በክፉ እና በደጉ አብረው ቆመው እስከ አሁን ደርሰዋል።
የሁለቱ እምነት ተከታዮች አንዱ ለአንዱ ቤተ እምነት መሥራት የቆየ ከአባቶቻችን የወረስነው እሴት ስለሆነ እኛም ይህንኑ እያስቀጠልን ነው ብለዋል።
የሥርዓት ለውጥም ሆነ የፖለቲካ ችግር ሀገሪቷን በገጠማት ወቅት ምንም ዓይነት የሃይማኖት ግጭት በወረዳው ተከስቶ አያውቅም ያሉት ነዋሪዎቹ፣ በወራዳችን ሃይማኖት የመቻቻል እና የአብሮነት ምንጭ እንጂ የግጭት መንሥኤ ሆኖ አያውቅም ብለዋል።
የክርስትና እምነት ተከታዮች በበኩላቸው የሙስሊም ማኅበረሰብ ላደረጉላቸው ድጋፍ አመስግነው፣ ይህን የቆየ የአባቶቻችንን እሴት አጠናክረን እናስቀጥላለን ብለዋል።
የሙኔሣ ወረዳ አስተዳዳር አቶ አማን ሻቁሮ ደግሞ በወረዳዋ መቀመጫ ቀርሣ ከተማ የመጀመሪያው መስጅድ የተሠራው በክርስትና እምናት ተከታይ የሀገር ሽማግሌ ነበር ብለዋል።
የከተማው ትልቁ መስጅድ መርካዝ የሚባለውም በክርስትና እምነት ተከታዮች ትብብር የተሠራ ነው።
ይህ በየተራ ቤተ እምነት አንዱ ለአንዱ የመሥራት ባህልም ተጠናክሮ እንደቀጠለ ነው ማለታቸውን ኦቢኤን ዘግቧል።
ምስጋና ለጎልጉል ድረ ገጽ አዛጋጆች በሙሉ፤
ከሁሉ በማስቀደም በአንድ ቀን ቢዘገይም እንኳን ለዓልም የሴቶች ቀን አደረሳችሁ። ጨርሶ ከሚቀር ዘግይቶ መደረጉ ክፋት የለውም ይላል እንግሊዝ (better late than never)።
ከሃገር ቤት መልካም ዜና መስማት እጅግ በናፈቀን ስዓት አልፎ አልፎ መልካም ስንሰማ የምንፈነድቅ ብዙዎች ነን። በተለይ እውነትም ሆነ ሃሰት እንደ ቆሎ የሚዘገንበት ዮቱብ እንዳሸን የፈሉት ሁሉ ግራ ተጋብተው ጋር በተጋባንበት ጊዜ ጎልጉል የተባለው የመረጃ መድረክ በድረ ገጹ ላይ የሚከተሉትን መልካም ዜናዎች አብስሮልናል።
አንደኛው ዜና “ራሱ አቡክቶ፣ ራሱ አሟሽሾ፣ ራሱ ጋግሮ በሰዓት 460 እንጀራ የሚያወጣ ፈጠራ ” በአንድ ወጣት ተማሪ የተገኘውን የፈጠራ ግኝት በዓለም የእናቶች ቀን ሲነግረን እጅግ አስደስቶናል። ይህ ፈጠራ የእናቶችን ድካም ብቻ ሳይሆን የሚቀንሰው፤ የደን መጨፍጨፍን የቀንሳል፤ የእናቶችን ጤንነት ያሻሽላል፤ ባህላዊ አሰራርን ያዘምናልና ወደ ተግባር የሚውልበትን ቀንና ጊዜ ብታሳውቁን ደስ ይላል።
የህዳሴው ግድብ ሃይል ማመንጨት በጀመረበት ጊዜ በመምጣቱ ፈጠራውን ወቅታዊ ያደርገዋል። በተለይ እኛ በዳያስፖራ የምንገኝ ሰዎች ማሽኑን እየገዛን አነስተኛ ገቢ ላላቸው እናቶች በስፖንሰርሽፕ ይሁን በስጦታ መልከ ገዝተን ማበርከት የሚቻል ይመስለኛልና አጣርታችሁ አሳውቁን። ሌላው ይህ ወጣት ዓላማውን ተግባራዊ ለማድረግ የሚፈልገው እርዳታ ካለ ብታሳውቁ ብዙ መርዳት የሚፈልጉ ሰዎችና ግለሰቦች ሊኖሩ ይችላሉ።
ይህ ፈጠራ በቀላሉ እንዳይታለፍና የአንድ ሳምንት ዜና ማሞቂያ ሆኖ እንዳይቀር አስፈላጊው ሁሉ ጥንቃቄ ይደረግበት። እንደዚህ ጻሐፊ እይታ ከሆነ የወጣቱ የምርምር ውጤት በመንግስት ደረጃ እውቅና ቢቸረው መልካም ነው። አነስታይን ፈጠራውን ወደ ተግባር በመቀየር ነው ዓለምን የቀየረው። የዚህ ወጣት ፈጠራም እንዲሁ ከተበረታታ ውጤቱና ጥቅሙ ለወጣቱ፤ ለሕዝባችንና ለሃገር ነውና እንደግፈው። እራስን በራስ የመቻል ማሳያም ነውና በቸልታ መታለፍ የለበትም።
ኢትዮጵያ ለማያስፈልግ ሰው ሰራሽ ጸጉር ከውጪ ለማስገባት የምታወጣውን የውጭ ምንዛሬ ሲታሰብ ያስደንግጣል። ይህን ከንቱ ወጪ ወደዚህ ፈጠራ አዙራ ብታስፋፋውና በተግባር ብታውለው ጠቀሜታው ለሃገሪቱ እንጅ ለማንም አይደለምና ይታሰብበት።
በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ድረገጻችሁ”በአርሲ ሙስሊሞች ለቤ/ክ ማሠሪያ 3 ሚሊዮን ብርና 20 የቀንድ ከብት ሰጡ ” የሚል ዜና አስነብቦናል።
እኛ ስለሃገራችን በየእለቱ የምንጨነቅ በተለይ በውጭ ሃገር ለምንገኝ ዳያስፖራዎች ትልቅ ዜና በመሆኑ የዚህ ኣይነቱን ዜናና መረጃ ያብዛልን። ኢትዮጵያችን በበቂ ደምታለች። ሳያስፈልግ ተስቃይታለች። በሚአሳዝን ሁኔታ ተፈትናለች። ዛሬ ታመመች፤ ነገ ፈረሰች እያልን የምጨነቅ ብዙዎች ነን። ስለዚህ የኢትዮጵያንና የኢትዮጵያዊያንን መከራ እንቀንሰው።
በተለይ የዩ ክሬን ሁኔታ ያየ፤ የታይዋንን ጭንቀት በየቀኑ የሰማ፤ የሶሪያን ቀውስና ውድምት በዓይኑ ያየ ትምህርት መውስድና ስህተትን ማስተካከል አያቅተውም። ሌላው አማራጭ የውድመትና የጥፋት ነውና ሁላችንም አድብ እንግዛ።
እስላምናና ክርስቲያን ተቻችሎ በሚኖርባት ኢትዮጵያ እንዴት የሃይማኖት ግጭትና ቀውስ ሃገራችንን ይፈትናት። እውነት ለመናገር ይህን ቀውስ፤ ችግርና ፈተና በሕዝባችንና በሃገራችን ላይ የሚአደርሱት እጅግ ትቂቶች ናቸው። ከ92% በላይ የሚሆነው ሕዝብ ቀውስን፤ የጎሳና የሃይማኖት ጠብንና ትርምስን እንደማይፈልገው ያለፉት ሃምሳ ዓመታት የፖለቲካ ጉዟችን ዋቢ ምስክሮች ናቸው።
ለማንናውም እንዚህን ሁለትት ጥሩ ዜናዎች ያጋርን ጎልጉል ድሕረ ገጽ ሰፊ ምስጋን ይድረሰው። ለወድፊቱም እንደዚህ ሕዝብን ሊአቀራርቡ የሚችሉ የመልካም ዜናዎችን አፈላልጋችሁ እንደምታሰሙን ተስፋ በምድረግ ለአሁን ፈጣሪ አብዝቶ ይስጥልን።
ከአክብሮት ምስጋን ጋር፤
ሰማነህ ታምራት ጀመረ
ኦታዋ ካናዳ
ሰኞ፤ ሚያዝያ1 ቀን 2014
ውድ ሰማነህ ታምራት ጀመረ
በቅድሚያ ጊዜዎን ወስደው ይህንን የመሰለ ምላሽ ስለላኩልን ከልብ እናመሰግናለን። እርስዎ እንዳሉትም ሁለቱም የዜና ዘገባዎች በጣም ጠቃሚና የሚያስደስቱ ናቸው።
የሚያሳዝነው እጅግ መልካም እና የሚያስደስት እሴት ያላት አገራችን ብዙ ሊወራላት የሚገባ ነገር እያላት ጠላቶቻችን በሚሰጡን አጀንዳ እርስበርስ እየተናቆርን መጥፊችንን በግድ የምንደግስ መሆናችን ያሳዝናል። ሆኖ ደግሞ እንደ እርስዎ ያለ እሾኹን ብቻ ሳይሆን አበባውንም የሚያይ አንድ ሰው መገኘቱ እጅግ ተስፋ የሚሰጥ ነው።
በእርግጥ እርስዎ በዚህ ልክ ጻፉልን እንጂ በዝምታ ደግሞ ያገራቸውን ሁኔታ የሚከታተሉና መልካሟን የሚመኙ እንደ እምነታቸው የሚጸልዩ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ እናቶች፣ አባቶች፣ እህቶችና ወንድሞች አሏት። ለዚህ ነው ኢትዮጵያ የተዓምር አገር የሆነችው።
ለመልካሙ አስተያየትዎ በድጋሚ ልባዊ ምስጋናችንን እናቀርባለን።
አርታኢ