
በጋምቤላ ክልል የኦነግ አባላት ናችሁ በሚል እና ህወሀትን ትረዳላችሁ በሚል የታሰሩ ዜጎች በአፋጣኝ እንዲፈቱ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን አሳሰበ። ኮሚሽኑ በጋምቤላ ክልል የእስረኞች አያያዝ እና የፖለቲካ ፓርቲዎች እንቅስቃሴ ሊሻሻል እንደሚገባም አሳስቧል።
ኮሚሽኑ ለኢትዮ ኤፍ ኤም በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው በጋምቤላ ክልል ያለው የእስረኞች አያያዝ እና የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎችን በነጻነት የመንቀሳቀስ መብት ሊረጋገጥ ይገባል ብሏል።
ኮሚሽኑ በታኅሣሥ ወር በጋምቤላ ከተማ እና በአኝዋህ ዞን በመገኘት፣ በአካባቢው ስላለው የሰብአዊ መብቶች ጥበቃ ክትትል አድርጎ ከክልሉ ኃላፊዎች ጋር መወያየቱን ገልጿል።
ኮሚሽኑ በጎበኛቸው የክልሉ ማረሚያ ቤቶች በእስር ላይ የሚገኙ ሰዎች አያያዝና ሰብአዊ መብቶች ጥበቃ ሁኔታ በአፋጣኝ ሊሻሻል የሚገባው ነው።
በተለይም በኦነግ ሸኔ አባልነት ተጠርጥረው በጋምቤላ ከተማ ማረሚያ ቤት ከታኅሣሥ መግቢያ ጀምሮ በእስር ላይ የሚገኙ ሁለት የ 11 እና የ 12 ዓመት ሕፃናት ወንዶች፣ እንዲሁም አንድ የ14 ዓመት ሕፃን ሴት በአፋጣኝ ከእስር እንዲለቀቁ አሳስቧል።
በተጠርጣሪዎች ሕፃናት ወንዶች ላይ ከፍተኛ ድብደባ ያደረሱ የፀጥታ አባላት ላይ አፋጣኝ ምርመራ በማካሄድ ተገቢው እርምጃ እንዲወሰድም ኮሚሽኑ ጠይቋል።
ይህ ሪፖርት እስከወጣበት ጊዜ ድረስ ሕጻናቱ በእስር ላይ መሆናቸውን ገልጿል።
በተጨማሪም “ሕወሓትን በገንዘብ እና በተለያየ መንገድ ይረዳሉ፣ በክልሉ ውስጥ በሕዝብ መካከል ግጭት የመቀስቀስ ዓላማ ይዘው ተንቀሳቅሰዋል” በሚል ምክንያት፣ ከጥቅምት 25 ቀን 2013 ዓ.ም. ጀምሮ በአቦቦ ከተማ፣ በአኝዋህ ዞን ማረሚያ ቤት 20 ሰዎች፤ እንዲሁም በጋምቤላ ከተማ ማረሚያ ቤት 70 ሰዎች፣ በአጠቃላይ በአብዛኛው የትግራይ ተወላጅ የሆኑ 90 ሰዎች፣ በክልሉ ፖሊስ ቁጥጥር ስር ይገኛሉ።
በኢሰመኮ ጉብኝት ወቅት፣ በእነዚህ 90 ተጠርጣሪዎች ላይ በፌዴራል ፖሊስም ሆነ በክልሉ ፖሊስ በኩል የተጀመረ የወንጀል ምርመራ ሂደት አለመኖሩ በመገለጹ፣ ኮሚሽኑ ይህንኑ አሳሳቢ ጉዳይ ለሚመለከታቸው የክልሉ ኃላፊዎች አሳውቆ በተጠርጣሪዎቹ ላይ በአፋጣኝ ምርመራ እንዲጀመርና የዋስትና መብታቸው ተጠብቆ ከእስር እንዲለቀቁ አሳስቧል።
ይህ ሪፖርት እስከወጣበት ጊዜ ድረስም እነዚህ ዜጎች በእስር ላይ የሚገኙ መሆናቸው ታውቋል።
በሌላ በኩል፣ ኮሚሽኑ በጉብኝቱ ወቅት በክልሉ የሚንቀሳቀሱ የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮችን አነጋግሯል።
ኢሰመኮ ያነጋገራቸው ፖለቲካ ፓርቲዎች ‘የምርጫ ሥነ ምግባር መግባቢያ ሰነድ’ የፈረሙ መሆናቸውን ገልጸው፣ ቢሮና የመሳሰሉ አገልግሎቶችን ለማግኘት፣ በክልሉ ልዩ ልዩ አካባቢዎች ተንቀሳቅሶ ለመስራትና፣ የፓርቲያቸውን ዝግጅቶችን ለማድረግ እንግልት እንደሚገጥማቸውና በአንዳንድ አባላቶቻቸው ላይ ዛቻና ማስፈራሪያ መድረሱን እንደገለጹለት ኮሚሽኑ በመግለጫው ጠቁሟል።
በተጨማሪም አንድ የፖለቲካ ፓርቲ በተለያየ ወቅት 35 አባላቱ በተለያዩ የክልሉ ከተሞች ለእስር መዳረጋቸውን ገልጿል።
እንዲሁም የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ አባል ቤተሰብ በመሆናቸው ከመንግስት ስራ የታገዱ እና ያለፈቃዳቸው ‘ለብልጽግና ፓርቲ መዋጮ’ በሚል ከደሞዛቸው ላይ የመዋጮ ክፍያ የተቆረጠባቸው ሰዎች መኖራቸውን አስረድተዋል።
የፖለቲካ ፓርቲዎቹ በክልሉ የሚገኙ የምርጫ ወረዳ ተወካዮች ብዛት አወሳሰን ዙሪያ ያላቸውን ቅሬታ ለክልሉ ባለሥልጣናት ቢያሳውቁም፣ ምላሽ አለማግኘታቸውንም ለኮሚሽኑ አሳውቀዋል።
ኢሰመኮ በእነዚህና ሌሎችም የሰብአዊ መብቶች ጉዳዮች ላይ ከክልሉ ከፍተኛ ኃላፊዎች ጋር በተወያየበት ወቅት፣ የክልሉ ኃላፊዎች ለሰብአዊ መብቶች መሻሻል በጎ ምላሽ ሰጥተው፣ በተለይም የገዢው ፓርቲ አባል ካልሆኑ የመንግስት ሰራተኞች ላይ ሲሰበሰብ የነበረው የፓርቲ አባልነት ክፍያ በተመለከተ አስፈላጊው የእርምት እርምጃ እንደተወሰደ ገልጸዋል። (ኢትዮ ኤፍ ኤም)
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
ነገሩ በሃበሻ ምድር የተገላቢጦሽ ነው እያለን ለዘመናት የኖረነው ከምናየውና ከምንሰማው ተነስተን ነው። አልፎ ተርፎም ኑረንበት ነበርና ነው። ግን የሚሰማ የለም። በመሰረቱ ሃበሻ ሲባል ምቀኛ፤ ተጠራጣሪ፤ በሁለት ቢለዋ የሚበላ አንድም ነገር ከአፉ የማይደርስ ለሌላውም እንዳይደርስ በምቀኝነት የሚንቀሳቀስ ህዝብ የሚበዛባት ምድር ናት። ሰው እያለቀሰ ስለ ህዝብ መበደል ሲናገር የሚስቁ፤ የሚቀልድ በብሄራቸው ካለሆነ በስተቀር የሰው ህይወት ምንም የማይመስላቸው ድርቡሾች የፈሉባት ሃገር ናት። በቆንጨራና በእሳት፤ በጥይትና በግርግር ሰውን እያፈናቀለና እየገደለ ዙሮ ተመልሶ ራሱ መልሶ ማቋቋም ይልና እርዳታው እጅ ሲገባ ይነግድበታል። ባጭሩ ስብዕና የሌላቸው የዘርና የክልል አውሬዎች የሚራወጡባት ይህች የሃበሻ ምድር ገና እልፍ ፈተና ይጠብቃታል። ቀልደኛው የወያኔ ካድሬ እንዳለው ነው። “እኔ ሱዳንና ግብጽ የሚያደርጉትን የህግ ማስከበር ዘመቻ በሙሉ ልቤ እደግፋለሁ” ይህ አይነት አስተሳሰብ እኔ ካልኖርኩ እሳት ይብላው በመሆኑ ዝርፊያው ግድያው መፈናቀሉ፤ በተገኘው ሚዲያ ላይ መዘነጣጠሉ ሁሉ ይቀጥላል። ሙት ይዞ ይሞታልና! ልፊያው አያባራም።
የሰው ልጅ ሰቆቃ ሙዚቃው ከሆነ ወገን ጋር እንዴት ነው ስለ ፍትህና ስለ አብሮነት መስራት የሚቻለው? የደነዘዘ ትውልድ ቢቆነጥጡት አይሰማም። ጫቱ፤ ሲጋራው፤ ዝሙቱ (ሴት ከሴት/ወንድ ከወንድ ጭምር)፤ ያበለዘው አዕምሮ የዛሬን እንጂ የነገን ማየት አይችልም። በየከተሞቹ በሴት እህቶቻችን ላይ የሚፈጸመው ግፍ ለዚህ ዋንኛ ማሳያ ነው። አባት ልጅን እናት ልጆቿን፤ ልጆች ወላጆቻቸውን የሚክድበትን ዘይቤ እያየን ነው። የክልል ፓለቲካ የዘር ተኮር እይታ ገና ስንቶችን አይን ያጠፋል። ለጉራ የሰው ዘር መገኛ እያልን እናቅራራለን። የሰው ልጅ ማፈሪያ ብንል ይሻል ነበር። አሮጊቶችን በእሳት፤ በጥይት፤ በስለት እንደ እንስሳ የሚገድል የውጭና የውስጥ ቅጥረኛ በሚራወጥባት ምድር ስለ ሰው ልጆች መብትና ነጻነት በመድረክ ላይ ቢለፉት ዋጋ ቢስ ነው።
አሁን በጋምቤላ ወያኔንና ኦነግ ሸኔን ትረዳላችሁ ተብለው የታሰሩ ሰዎች እንዲፈቱ መጠየቁ ከሴራው ጋር የቀኑ አለቆች ምን ያህል ትስስር እንዳላቸው አመላካች ነው። አዙሪቱ በወረፋ የዛሬን ገዳይና አስገዳይ፤ የዛሬን የአደባባይ ደስኳሪዎችና አራጊ ፈጣሪዎች መልሶ አፈር ያለብሳቸዋል። ታሪካችን የሚያሳየው ይህኑ ነው። ጉረኞችና ያለ እኛ ማን አለ የምንል መሆናችን ዋናው ማሳያ የወያኔ በአለቀ ሰአት የሰሜኑን ጦር ማጥቃት ነው። ልብስ ያወለቀ የአማኑኤል እብድ እንኳን አያስበውም። ግን አረጉት፤ ተደረጉ፤ እየተደረጉም ነው። የሃበሻው ፓለቲካ አዙሪት ነው የምለውም ለዛ ነው። በዚሁ የግል ሽኩቻና ቀዳዳ ሱዳንና ግብጽ ሌሎችም የፓለቲካ ወሬ አናፋሾች እሳት ጭረው እየቆሰቆሱ መከራችን ያራዝሙታል። እኛም አውቀን ሳንታለል በዘርና በቋንቋ ተሰልፈን እያገዝናቸው ነው። ኦ በዚህ የስርግብ ትግል ግን አትራፊ አይኖርም። ትላንት ሻቢያንና ወያኔን በማስታጠቅና መጠለያ በመስጠት ሃገሪቱ እንድትፍረከረክ ያደረጉት እነዚያ ሃይሎች ከሞላ ጎደል የኢትዮጵያን ግባዕተ መሬት አሁን ይሻሉ። የውጭ ሃይልን መክቶ የውስጥን ለማረጋጋት አንድ መሆን አስፈላጊ ነበር። ግን በወያኔ የ 45 ዓመት ሴራ ዛሬ አንድነት የለም። በቋንቋዬ ካልተናገርክ እቃ አልሸጥም የሚል ደንቆሮ ያለበት ሃገር ላይ ተቀምጦ ሰለ ህብረ ብሄራዊነት ማውራት አይቻልም። ብቻ ሃበሻ ለራሱም ለሃገርም በውጭ ያለውም ሆነ በሃገር ያለው አይጠቅምም። ምቀኛ ነው። እሳቱ አናቱ ላይ ካልወጣ በስተቀር የሌላው ጉዳት ጉዳቱ አይደለም። አዎን 100 ሚሊዪን ህዝብ በላይ አላት የምትባለው ይህች ምድር ላይ የሚርመሰመሰው ሁሉ አንድ ነው እያልኩ አይደለም። ግን ዝምታም ከክፋት ጋር እንደመተባበር ይቆጠራል። የዘር፤ የጎሳ፤ የቋንቋ ፓለቲካ እስካልሞተ ድረስ ሃገሪቱ በውጭ ሃይሎችና በውስጥ አጥፊዎች በእሳት መለብለቧ አያቋርጥም። የፓለቲካው ጡዘት መልክና ስሙን እየቀየረ ይነጉዳል፤ በመንገድ ላይ ያለውንም ይጠርጋል። ሰው በሰውነቱ መሰላቱ ቀርቶ በዘረፈው ሃብትና በዘሩ ይተመናል። ጥቂቶች ፈንጭተው እልፎች እያለቀሱባት ያለች ሃገር ላይ ሰላምና መረጋጋትን እናስከብራለን ማለት ከጅምሩ ዋሾ መሆን ነው። በቃኝ!