
ቁጥራቸው 16 የሆኑ በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ውስጥ የነበሩ የህወሃት መኮንኖች ወደ ጅቡቲ ቢኮበልሉም ጅቡቲ ለኢትዮጵያ መንግሥት ተላልፈው እንደተሰጡ ተነገረ።
የጅቡቲ ዜና ወይም Les Nouvelles de Djibouti በድረገጹ ይፋ ያደረገው ዜና ርዕስ “የትግራይ ተወላጅ የሆኑ ወታደሮችን ጅቡቲ ለኢትዮጵያ አሳልፋ ልትሰጥ ነው” የሚል ነበር።
ይህ አሳልፎ የመስጠት ስምምነት የተፈረመው እኤአ በመጋቢት ወር 2017 ነበር። በወቅቱ ኢትዮጵያን ይጎበኙ በነበሩት ፕሬዚዳንት ኢስማኤል ኦማር ጉሌህና ጠቅላይ ሚኒስትር በነበረው ኃይለማርያም ደሳለኝ መካከል ነበር።
በስምምነቱ መሠረት ማንኛውም “ወንጀለኛ፣ አሸባሪ” ተብሎ የተጠረጠረና ከአንዱ አገር ወደሌላው ጥገኝነት ለመጠየቅ የሄደ አገራቱ አሳልፈው እንዲሰጡ የሚያደርግ ነበር።
ይህንን ስምምነት በዋንኛነት የፈለገው ራሱን የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጪ ግምባር በማለት የሚጠራው የበረኻ ወንበዴዎች ቡድን ነበር። ቡድኑም በአገር ወስጥ የሚነሳበትን ተቃውሞ በማፈን በእጅጉ የተካነ በመሆኑ ከአገር ውስጥ አምልጠው ወደ ጎረቤት አገራት የሚሄዱትን በቁጥጥሩ ሥር ለማዋል ያደረገው እንደነበር ይታወቃል።

በዚህ ስምምነት ምክንያት የፖለቲካ አቋማቸው ከወንበዴው ህወሃት ጋር ያልተስማማ ተቃዋሚዎች በሙሉ እየተያዙ ተላልፈው ሲሰጡ መቆየታቸው ይታወቃል። ህወሃት በተመሳሳይ የኬንያን ድንበር በመጣስ ተመሳሳይ ተግባራት ሲፈጽም እንደነበር ይታወቃል።
ከሁለት ቀናት በፊት (ማክሰኞ) የፖለቲካ ጥገኝነት ለመጠየቅ ወደ ጅቡቲ የሄዱት 16 የህወሃት ወታደሮች መካከል አንድ ኮሎኔል፣ አንድ ኮማንደር እና 12 ሌፍተናንቶች እንደሆኑ ዜናው ሲዘግብ ሁሉንም የትግራይ ተወላጆች መሆናቸውን በመጥቀስ ነበር።
ግለሰቦቹ ወደ ጅቡቲ ከገቡ በኋላ በጅቡቲው የሰነድና ደኅንነት አገልግሎት ምርመራ የተካሄደባቸው ሲሆን በነጋታው ማለትም ረቡዕ ማምሻው ላይ በጅቡቲ አየር ኃይል ተጭነው ወደ ኢትዮጵያ ተላልፈው ሲሰጡ ድርጊቱን ተቃውመው እንደነበር ዜናው ዘግቧል።
ጅቡቲ ኒውስ ዘገባውን ሲያጠናቅቅ “እነዚህ ግለሰቦች አዲስ አበባ የነበሩና ከህወሃት ጋር ሲሠሩ የቆዩ” መሆናቸውን በመጥቀስ ነበር።
አስራ ስድስቱ ከሃዲዎች ረቡዕ ዕለት አመሻሹ ላይ ወደ አዲስ አበባ ተጭነው በመጡበት ወቅት በጅቡቲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሙሀመድ አሊ ዮሱፍ የተመራ ከፍተኛ የልኡካን ቡደን ረቡዕ ማምሻውን አዲስ አበባ መግባቱን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መዘገቡ ይታወሳል።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply