መቼም እኔና አንቺን ሲፈጥረን
ጉዳችሁ አይለቅ ያለን ነን
የኛ ብለን ክብር ሰጥተን
ያመነው ሰው ደ’ሞ ከዳን።
ይሄን ሰማሁ ይሄውልሽ
አንቺም ሰሚው አይቅርብሽ
እንደው ቢገርመኝ እንጂ ነገሩ፥ይሄማ ምኑ ይወራል
የኛ ያሉት ሲከዳ፥ቃሉ ለአፍ ይመራል
ብቻ ምን ይደረግ? ”ውሻ በቀደደው…” ይባል የል
የሱስ መክደት ምን ይደንቃል?
እንደው ግን ለነገሩ፤ እየገደሉ እያያቸው
በደም ተጨማልቆ እጃቸው
ከነሱ ጋር አብሮ
እየደለቀ ከበሮ
የተለጠፈው ውስጣቸው
ምን አግኝቶ ምን አጥቶ ነው?
በምኑስ ላይ ምን ሊጨምር?
መች አነሰው? ንዋይ ክብር
በይ ተይው ግድ የለም፤ መቼም-እኔና አንቺን ሲፈጥረን
ጉዳችሁ አይለቅ ያለን ነን።
እንግዲህ ካልሰማሽም ስሚ፤ ከሰማሽም-ቻልአድርጊው
እኛን ያልከዳን ማን አለ? የበደለን እኮ ብዙ ነው
አረ! ብዙ ነው የተጫነን ሊጫነንም የተነሳ
በስቃያችን የወፈረ በረሃባችን ያገሳ
እንተወው ግድ የለም! ምን ያደርጋል ቁጥሩ
ምን ሊሰራልን ስፍሩ
ስሙንም ተይው ማንም ይባል
ስሙ ከክዳት መች ያድናል
ታዲያ ይሄንን በልቦናሽ እያወቅሽ
ስምና ክብሩ ምን ሊበጅሽ?
ይሄው አታይም ደፋ ቢልብን ቀኑ
ከዘፋኙ፣ ከደራሲው፣ ከገጣው፣ ከካህኑ
ከሯጩ ሳይቀር ከጋዜጠኛው፣ ከዶክተሩ
ከተዋኒው፣ ከተማሪው፣ መምህሩ
ማል ሳንለው ምሎ
በል ሳንለው ብሎ
ባነጋገሩ ፈሊጥ አታሎ
ራሱን ከኛ ጋር ሸምልሎ
አናምነው የለን አምነነው
ልባችንን ከፍተን ሰጥተነው
ሲተሻሸን ሲያሸተን ከርሞ
አፍንጫውን እንደውሻ አቁሞ
ስንቱ ከድቶናል እባክሽ
መክዳትማ ብርቅ እንዳይሆንብሽ
አንዳንዴ ግን-ክህደቱ ሲጠናብኝ
ነገሩ ሆዴ ገብቶ ሲያማስለኝ…
ብቻዬን መሆኔን ፈትሼ
አንገቴን ደፍቼ አይኔን መልሼ
የታሪክ ዘርፋችንን ጉዞ ሚስጥር
በልቦናዬ እያገዋለልኩ ስመረምር
ይሄ ሁሉ የቤታችን ጋሬጣ
ይሄ ሁሉ የውጪ ባላንጣ
ጨርሰናቸዋል ብሎ ሊቀብረን ሲመጣ
እንደገና ቀና ብለን
ዓይናችንን ከፍተን ያየን
ማንም ችሎ ያላጠፋን
በዘር በቂም የማንፋጅ
ታሪካችን የማያረጅ
አለ መሪ አለዳኛ
የምንኖር እናው በኛ
ከግዜሩ ቃል የማንርቅ
በይቅርታ ምንታረቅ
መልከ መልካም ጨዋ ደጎች
ሰላም ፍቅር ፈላጊዎች
መሆናችችንን ሳስብ
የኛነታችንን ልክ ስገነዘብ
ይች የአሁኗ ክዳት
ይች ያሁኗ ዘረኝነት
ይች ያሁኗ ጭካኔ
ይቺ ያሁኗ ሁሉን ለኔ
እንኳንስ የአንድነታችንን ችካል
አቅም ኖሯት ልትነቃቅል
እንኳንስ የታሪካችንን ሀቅ
አቅም ኖሯት ልትነቀንቅ
እንኳንስ የባንዲራችንን ቀለም
መልኩን ሽራ ልታጨልም
እንኳንስ የቃል ኪዳናችንን ተስፋ
አቅም ቋጥራ ልታጠፋ
እንኳንስ በወሬ ስፍር ክምር
የኢትዮጵያዊነታችንን ልትሸረሽር
እንኳንስ ልትመርዘን፤ ልትበርዘን ይቅርና
ለራሷንም አይኖራት እርባና
ለዘመናት የደረጀን የባህል ውርስ
በደማችን የታተመን የታሪክ ቅርስ
የኢትዮጵያዊነታችንን ጽኑ መንፈስ
ማንም አይችል ለመደምሰስ
ይሄንን ተረጂልኝ፤ ፊትሽ አይጥቆር- እባክሽ
በስንቱ አዝነሽ ትችያለሽ
ይልቅስ ለከዳን ነው የሚታዘንት
ህዘብ ፍቅሩን ላነሳበት
ዝና ክብሩን ለሻረበት
ስራው በቁም ለሞተበት
ለሱነው ማዘን ለስሙ
ለጠወለገችበት አለሙ
ለሱ ነው ሀዘን የሚአስፈለገው
ቀብሩን በቁሙ ላደኸየው
አዎን! ለሱ ነው ማዘን አይዞሽ
ደጋግሜ እንደነገርኩሽ
እኛማ ምን እንሆናለን ብለሽ?
በዘር በቂም የማንፋጅ
ታሪካችን የማያረጅ
አለ መሪ አለዳኛ
የምንኖር እኛው በኛ
ቀሩ ሲሉን የቀደምን
ሞቱ ሲሉን የተነሳን
ስንቱ ክህደት ያላጠፋን
ታምረኛ ብቻ ሳንሆን
እኔና አንቺ ታምርም ነን!
***
እኔና አንቺ … ፩ ለማንበብ እዚህ ላይ ይጫኑ
Leave a Reply