
በምሥራቅና በምዕራብ የተገኘው ድል በመሐል ሀገር እንደሚደገም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ገለጡ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይሄንን የተናገሩት በሦስተኛው ቁልፍ ግንባር ተገኝተው ከሠራዊቱ ጋር በመከሩበት ጊዜ ነው።
ከሰሞኑ በሚሠሩ ኦፕሬሽኖች በወራሪው አሸባሪ የተያዙ ተጨማሪ ከተሞች ነጻ እንደሚወጡ የገለጡ ሲሆን ለወረራ የገባው አሸባሪ ምንም ነገር ይዞ እንዳይወጣ ሕዝቡ ተደራጅቶ ማስቀረት እንዳለበት ጥሪ አድርገዋል።
ጠላት ፈርሷል፤ ተበትኗል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ፣ አሁን ጠላት ያለው አማራጭ የሰረቀውን አስረክቦ እጁን መስጠት ነው ብለዋል።
የሰረቀውን አስረክቦ እጁን ከሰጠ ምርኮኞችን ተከባክቦ መያዝ የጀግና ባህላችን ነው ብለዋል።
ከአሸባሪው ሕወሓት ነጻ በወጡ አካባቢዎች በአስቸኳይ መስተዳድሩን በቶሎ መልሶ ማቋቋም እንደሚገባ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሳስበዋል።
ኢትዮጵያውያን አንድ ሆነዋል። ወታደሩ በከፍተኛ ሞራል ላይ ነው ሲሉም የወገን ኃይል ያለበትን ገልጠዋል።
ሕዝቡ እስካሁን ላደረገው ተሳትፎ ምስጋና ያቀረቡ ሲሆን አንድነታችን የተጠበቀ ይሁን፤ የአሉባልታ ወሬ ወጀብ አይውሰደን፤ አንድ ሆነን የማትደፈር ሀገር ለልጆቻችን እናስረክብ ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ መልእክት አስተላልፈዋል።
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ
ይገርማል። ሰው ረጋ ብሎ የሃገራችን የኋላ ታሪክ ለመዘነ ይበልጡ የሽብርና የመገዳደል ታሪክ ነው። ይህን የተረዱ ይመስለኛል የቀድሞው መሪ ኮ/መንግሥቱ ሃ/ማሪያም እንዲህ በማለት አንድ ወቅት ላይ የተናዘዙት። ” አያቴ ሰላምን አያውቅም፤ አባቴ ሰላምን አያውቅም፤ እኔ ሰላምን አላውቅም፡፤ ምን አልባትም ልጆቼ” በማለት ምጽአታዊ እይታቸውን የተናገሩት። ይሁን እንጂ ሞልቶ የሚፈስን ግፍ ለመታገል የሚደረገው የሞት ሽረት ውጊያ አማራጭ የሌለው ነው። የወያኔን ግፍ ሰው ሁሉ አሁን ስለነቃበት በቀረርቶ፤ በዘፈን፤ በግጥም፤ በጽሁፍ፤ በድራማና በሌሎችም ልዪ ልዪ መንገዶች እየተጋፈጡት ይገኛል። የከተማውን ልተውና በገጠር ከተባሉ ጥቂት ስንኞች ላካፍላችሁ።
ግርምም ይለኛል ድንቅ ያደርገኛል ያሰብኩት እንድሆን
ሰው በገዛ ሃገሩ ተፈናቃይ ሲሆን።
ሌላው የወያኔን ዘራፊነት ለማሳየት
መጫን ቢቻል ኑሮ ውሃን በመኪና መቀሌ በገቡ አባይና ጣና።
ታዲያ በዚህና በዚያም የፓለቲካ ግርግር ውስጥ ሚዛናዊ ሆኖ ዘርና ቋንቋን ወይም ሃይማኖትን ተገን ሳያረጉ ሰው ለሆነ ሁሉ ሰው ሆኖ መቆም እየከበደ ሂዷል። ዝተት ሃሳብ ይዘው የሚወላገድትን ከነሸክማቸው በመተው በእውነት ለሃገር እናስባለን የሚሉትም ቢሆኑ የሚያሰሟቸው አንዳንድ ድምጾች ከእውነት የራቁና አክራሪነት የታከለባቸው ናቸው። ዝንተ ዓለም ንገስ በሚል ህብረተሰብ መካከል ተወልደን ሰው ዘላለማዊ እንዳለሆነ መረዳት ይከብደናል መሰል የመሪ አምልኮ እናበዛለን። አሁን ህልም አየሁ፤ ትንቢት መጣልኝ፤ ከፈጣሪ ትላንት የተቀበልኩት ራዕይ ይህ ነው እያሉ ጠ/ሚሩን ቋሚ ሃውልት አስመስለው የሚያገዝፉ ሁሉ ቱልቱላዎች ናቸው። ጠ/ሚሩ ስጋና ደም ያለው እንደ እኛ ሰው ነው። ይሳሳታል፤ በጎና መልካም ነገርም ያደርጋል። እነዚህ የነገን ዛሬ ላይ ቆመን እናውቃለን የሚሉት አጭበርባሪዎች እንኳን የነገን ይቅርና ጧት ላይ የበሉት ቁርስ እንኳን ተረስቷቸዋል። ዝም ቢሉ እንዴት ይመረጥ ነበር። ለዚህ ማስረጃው በዋይት ሃውስ ነብይት ብርቱካን ከያኔው ፕሬዚደንት ትራምፕ ጋር ያደረገቸው የጸሎትና የወደፊት አመላካች ነገር ዋና ማሳያ ነው። አንድም አልሰመረም።
አሁን እንሆ ራሳቸው በለኮሱት የመከራ እሳት የሚለበለቡት የወያኔ ወራሪ ሃይሎች ይህ ሁሉ ክፋት ከመድረሱ በፊት ተው ተብለው አልመከረም በማለታቸው የደረሰ የጋራ የመከራ ዶፍ ነው የሚወርድብን። አንዲት በመንግስት ተማረከች የተባለች የ 14 ዓመት ልጅ በግድ ነው ከቤት የወሰድኝ ስትል ጋዜጠኛው እናትሽ ምን አለች ሲሏት አለቀሰች ነው ያለቸው። ወያኔ ለትግራይ ህዝብ ከፍታ ቆሟል ብለው የሚያምኑ የትግራይ ልጆች እብዶች ናቸው የምለው ለዚህ ነው። የትግራይ እናቶችና አባቶች እንባ የአፋርና የአማራ እናቶችና አባቶች ከሚያነቡት እንባ አይለይም። ተያይዞ ማልቀስ ነው። ወይ ማን አያይዞን አይፈቀድልን፤ በርቀት በያለንበት ማንባት ነው። የእብዶች ፓለቲካ ውጤቱ እብደትን በሌላ እብድ መተካት ነው።
አሁን በተሰመረው የፓለቲካ አሰላለፍ ላይ በጭፍን ዶ/ር አብይን የሚጠሉ ሰዎች በተለይም የፕሮቴስታን ወይም የኦርቶዶክስ አማኝ ነን የሚሉ የሚያናፍሱትን ሳነብና ስመለከት እብደታችን ጣራ መድረሱን እረዳለሁ። እኔ ማንም ምን ቢል አቶ ሽመልስም ሆነ የአዲስ አበባ ከንቲባዋ፤ ወይም ሌሎች አመራር ላይ ያሉ ኦሮሞዎች ሆን ብለው አማራን ያስገድላሉ ብዬ አላምንም። ይመስለኛል ጦርነቱ ከወያኔ ጋር ብቻ አይደለም። ከፕሮቴስታንት እምነት አጥባቂዎችና፤ የኦርቶዶክስ እምነት አክራሪዎችም ጭምር እንጂ። ሲጀመር prosperity gospel እና prosperity party አይገናኙም። በወንጌል የተሰለፉት አጭበርባሪዎችና አውሮጵላን ይገዛልኝ የሚሉ የምድር ኗሪዎች ሲሆኑ የፓለቲካው ፓርቲ ደግሞ የድሃ ቤቶችን የሚጠግን፤ ከሃገር የተፈናቀሉትን የሚረዳ፤ ሃገሩንና ወገኑን ከልባቸው ሊያገለግሉ የተነሱ የሰዎች ስብስብ ነው። በዚህ ስብስብ መካከል እሾህ አይኖርም ግን አልልም።
በዚህ ዙሪያ ላይ ዶ/ር ደረጀን ከበደን ለማስጠንቀቅ በየሥፍራውና በተለያዪ ሰዎች የተሰጠውን አይቻለሁ፤ አንብቤአለሁ። ችግሩ ሰዎቹ የተጣሉት ከሰውዬው ጋር እንጂ ከሃሳቡ ጋር አለመሆኑ ነው። በእኔ እይታ ዶ/ር ደረጀ በጠ/ሚሩ ላይ ያለውን ጥላቻ በመረጃ ቢያቀርብ የሚሻል ይመስለኛል። ለእኔ አማራ አማራ የሚለው የአንድ ወገን እይታውና በጠ/ሚሩ ላይ ያለው አጠቃላይ አመለካከቱ አይዋጥልኝም። ለሰማይ ያደረ ሰው በዘሩና በቋንቋው አይሰለፍም። ከዚህ በላይ ግን የሚያስገርመኝ መልስ ሰጪዎቹ ናቸው። ለምሳሌ መስፍን ጉቱ ወንድ ከሆንክ ለምን እዚህ አትመጣም ብሎ ሲናገር ስሰማ እውነትም አለሙ ሁሉ ገምቷል ነው ያሰኘኝ። ቀጥሎም ከአሁን በህዋላ ጠላቶችህ እኛ ነን ሲል ደግሞ እጅግ መውረድን ያሳያል። የኬፋ፤ የሶፊያና የሌሎችንም ወንጌል ሰባኪና ሌላም ነን የሚሉትን አይቸዋለሁ። እግዚኦ ያሰኛል። ዶ/ር ደረጀ ለዘመናት ህይወትና ኑሮውን ለአገልግሎት የሰጠ፤ በሰቆቃ የኖረና ያን ያለፈ ለመሆኑ የሚያውቁት ይመሰክራሉ። አሁን በሽምግልና ዘመኑ እንዲህ በሰው ላይ መረባረብ ምን ይባላል። ግን እንኮ በዚህም በዚያም የሚንጫጫውና ሃሳቡን ሳይሆን ዶ/ር ደረጀን ለማጥቃት ያሰፈሰፈው ሁሉ ራሱን ዞር ብሎ ቢመለከት ማፈር በቻለ ነበር። ጊዜው ያስረሽ ምችው ነው። prosperity party እና prosperity gospel ልዪነት እንዳላቸው እንኳን የማይገባቸው ናቸው የሚለፈልፉብን። የብልጽግና ወንጌል ምዕመናኑን አምጡ፤ አውሮፕላን ግዙልኝ፤ ያን ካረጋችሁ ያላችሁ ይበዛል፤ በሚሉ አታላዪች የተሞላ ነው። ልብ ላለው ሁለቱ አይገናኙም። መቼ ይሆን ሰውን ከማስፈራራት፤ ከመሳደብና የሌለ ስም ከመስጠት የምንቆጠበው። አሁን ሥራዋን በመተው የወያኔን ሴራ ከዘሯ በተሻገረ እይታ አይታ ለዓለም በማሳየት ላይ ያለችው ሄርሜላ አረጋዊን መሳደብ፤ እንደበድብሻለን ዋይ እንገልሻለን፤ አልፎ ተርፎም በቤተሰብ ግፊት እይታዋ እንዲቀየር የሚሞክሩ ሁሉ የዚህ የሙታን ጥርቅም አካሎች ናቸው። በቅርቡ ጋዜጠኛው ለነበራቸው ቃለ ምልልስ ካመሰገናት በህዋላ የማንን ዘፈን ላዘፍንሽል ሲላት “የዘሩባቤል ሞላን – ምንድን ነው ዝምታሽ” በማለቷ ፈልጌ አዳመጥኩት። የገባት ልጅ መሆኗ ያኔ ደግሞ ለእኔም ገባኝ።
በመዝጊያ መፈለግ ያለበት መፍትሄ ከዘመን ዘመን በየምክንያቱ የሚያገዳድለን ነገር እንዴት ነው መቆም ያለበት ነው። የዛሬው ድል የነገ ሌላ የጦርነት ጊዜ ነውና። እውቁ አሜሪካዊ ጄኔራል Smedley Darlington Butler – war is a racket በተሰኘው መጽሃፉ ላይ ጦርነት እንዴት የሸማቾችና የአትራፊዎች ገቢያ እንደሆነ ያሳየናል። እንዴት ሰው ሆኖ ቆሞ የሚሄድ በየመን ላይ የሚዘንበው መከራ ትምህርት አይሆነውም? እንዴት የሶማሊያ ለሶስት መከፋፈል ትምህርት አያገኝም። በነጭና በዓረብ እየተነድ እስከ መቼ ነው እንዘጥ እንዘጥ የሚለው ህዝባችን እየደማና እየተራበ? አይበቃም እብደቱ? የምስራቅና የምዕራቡ ድል በማህል ሃገርም ይደገማል? ቤቱ የተቃጠለበት አንድ ገበሬ ሥራ ውሎ ሲመጣ ቤትህ እኮ ተቃጠለ ቢሉት አይ “የቤቴ መቃጠል ለቱሃኑ በጀ” አለ ይባላል። እንዲህ ነው። የእኛ ነገር ትልቁን ቤት አፍርሰን ሜዳ ላይ ለመተኛት ያለን ናፍቆት። ኸረ ተው መገዳደል ይብቃ? አሜሪካና ጃፓን እንኳን ታርቀው በሰላም እየኖሩ አይደል እንዴ። እንዴት በፈጠራ ጥላቻ እንዲህ ሰው ይለቅ። ክራራይሶ ያሰኛል። በቃኝ!