
በመንግሥት ባለቤትነት ሥር ከሚገኙት 13 ስኳር ፋብሪካዎች ውስጥ አሥሩ ለግል ባለሀብቶች ተሸጠው፣ ከሽያጩ የሚገኘው ገቢ በከፍተኛ የዕዳ አጣብቂኝ ውስጥ ናቸው ተብለው ለተለዩ ሰባት የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ዕዳ ክፍያ ጥቅም ላይ እንዲውል ተወሰነ።
ሪፖርተር ያገኘው መንግሥታዊ መረጃ እንደሚያመለክተው ሰባቱ የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ካለባቸው አጠቃላይ ዕዳ ውስጥ፣ አመዛኙ እንደ አዲስ ወደ የሚቋቋመው ኮርፖሬሽን እንዲዘዋወር ተወስኗል።
አዲስ የሚቋቋመው ተቋም “የዕዳና ሀብት አስተዳደር ኮርፖሬሽን” የሚል ስያሜ የተሰጠው ሲሆን፣ ኮርፖሬሽኑን ለማቋቋምም የሚያስችል ደንብ ከጥቂት ሳምንታት በፊት በሚኒስትሮች ምክር ቤት መፅደቁ ይታወቃል።
ኮርፖሬሽኑ ከፍተኛ የዕዳ ጫና ውስጥ ወድቀዋል ተብለው ከተለዩት ሰባት የመንግሥት ልማት ድርጅቶች አጠቃላይ ዕዳ ውስጥ፣ ኮርፖሬሽኑ አመዛኙን በመውረስ ዕዳቸውን የመክፈል፣ እንዲሁም ድርጅቶቹን ከዕዳ አስተዳደር ወጥተው ትርጉም ያለው ኢኮኖሚያዊ ተልዕኮ እንዲወጡ የማስቻል አስተዳደራዊ ሚናም ተጥሎበታል።
በመንግሥት የተለዩት ሰባቱ የመንግሥት ልማት ድርጅቶች የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት፣ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን፣ ኢትዮ ኢንጅነሪግ ግሩፕ (የቀድሞው ሜቴክ)፣ ኬሚካል ኢንዱስትሪ ኮርፖሬሽን፣ የኮንስትራክሽን ሥራዎች ኮርፖሬሽንና ስኳር ኮርፖሬሽን ናቸው።
እነዚህ ድርጅቶች ከአገር ውስጥ አበዳሪዎች በዋናነት ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክና ከውጭ አበዳሪዎች ተበድረው ያልመለሱት አጠቃላይ ዕዳ 780 ቢሊዮን ብር ወይም 19.5 ቢሊዮን ዶላር እንደሆነ፣ ገንዘብ ሚኒስቴር ሰሞኑን ይፋ ያደረገው መረጃ ያመለክታል።
አዲስ የሚቋቋመው ኮርፖሬሽን ሰባቱ ድርጅቶች ካለባቸው 780 ቢሊዮን ዶላር ውስጥ 570 ቢሊዮን ብሩን ወርሶ የመክፈልና የማስተዳደር ኃላፊነት ተጥሎበታል።
ኮርፖሬሾኑ የሚቋቋመው ራሱን በቻለ የንግድ ተቋም አደረጃጀት እንደሚሆን፣ ኃላፊነቱን ለመረከብ የሚያስፈልገው የመጀመርያ ካፒታልም ከመንግሥት በጀት ውጪ እንደሚሆን መረጃው ያመለክታል።
በመሆኑም አሥር የመንግሥት ስኳር ፋብሪካዎችን በመሸጥ የሚገኘው ገቢ ኮርፖሬሽኑ ለሚያስፈልገው የመጀመርያ ካፒታል ፈሰስ እንዲደረግ የተወሰነ ሲሆን፣ ከስኳር ፋብሪካዎቹ ሽያጭ ከሚገኘው ገቢ በተጨማሪ በቅርቡ ለውጭ ኩባንያዎች ከሚሰጠው የቴሌኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት ፈቃድ ክፍያ፣ እንዲሁም ከኢትዮ ቴሌኮም ከፊል ሽያጭ የሚገኘው ገቢ ትልቅ ድርሻ ወደ ኮርፖሬሽኑ ፈሰስ እንዲደረግ መወሰኑ ታውቋል።
መንግሥት በመጀመርያ ይዞት የነበረው ዕቅድ 13 ስኳር ፋብሪካዎችን ለመሸጥ የነበረ ሲሆን፣ ይህንንም ወደ ተግባር ለመቀየር የሁሉም ፋብሪካዎች አጠቃላይ ሀብትና ንብረት በገለልተኛ የኦዲት ኩባንያ እንዲገመት አድርጓል።
ይህንን የሀብትና ንብረት ግመታ እንዲያከናውንም ቡከር ቴት የተባለ የእንግሊዝ ኩባንያ ተቀጥሮ የግመታ ሥራውን ከዓመት በፊት አጠናቆ፣ ሪፖርቱንም ለመንግሥት እንዳቀረበ የተገኘው የሰነድ መረጃ ያመለክታል።
ኩባንያው ባካሄደው የግመታ ሥራ የ13 ስኳር ፋብሪካዎችን አጠቃላይ ሀብትና ንብረት ከዓመት በፊት በነበረ ዋጋ መሠረት 88 ቢሊዮን ብር ገምቷል።
ይሁን አንጂ በተመሳሳይ ወቅት የነበረው የስኳር ፋብሪካዎቹ አጠቃላይ የአገር ውስጥ ዕዳ ወለድን ሳይጨምር ብቻውን 81.6 ቢሊዮን ብር የነበረ ሲሆን፣ በዚህ ተመሳሳይ ወቅት የፋብሪካዎቹ አጠቃላይ የውጭ ዕዳ መጠን ወለድን ሳይጨምር 2.1 ቢሊዮን ዶላር ነበር።
በመሆኑም የ13 ስኳር ፋብሪካዎች አጠቃላይ የአገር ውስጥና የውጭ ዕዳ ወለድን ሳይጨምር፣ በአሁኑ ወቅት ባለው የውጭ ምንዛሪ ተመን ሥሌት 165.6 ቢሊዮን ብር ይሆናል። ይሁን እንጂ ይህ ግመታ ከተከናወነ በኋላ መንግሥት ተጨማሪ ወጪዎች በስኳር ፋብሪካዎች ላይ በማፍሰሱ የምርት ማሻሻያ ሥራዎችን፣ እንዲሁም የተመረጡ ፋብሪካዎችን የግንባታ ደረጃ የማሻሻል ጥረቶችን ያደረገ በመሆኑ፣ በቀደመው የሀብት መጠን ላይ ለውጥ እንደሚያመጣ መረዳት ይቻላል።
መንግሥት ከ13 ፋብሪካዎች ውስጥ አሥር ፋብሪካዎች እንዲሸጡና የሚገኘው ገቢም የዕዳ ክፍያን ለማስተዳደር ወደ የሚቋቋመው ኮርፖሬሽን ሙሉ በሙሉ ፈሰስ እንዲደረግ በመወሰኑ፣ አሥሩ ፋብሪካዎች በተገመቱበት የሀብት መጠን ብቻ ቢሸጡ፣ ኮርፖሬሽኑ ከ100 ቢሊዮን ብር በላይ መቋቋሚያ ካፒታሉን ከስኳር ፋብሪካዎች ሽያጭ ሊያገኝ ይችላል።
ከስኳር ፋብሪካዎቹ ሽያጭ በተጨማሪ ከቴሌኮሙዩኒኬሽን ዘርፍ ገቢ ከፍተኛ ድርሻ ለኮርፖሬሽኑ ፈሰስ የሚደረግ ሲሆን፣ የቴሌኮሙዩኒኬሽን ዘርፉን ለውጭ ገበያ ለመክፈት በተወሰነው መሠረት፣ ለሁለት የውጭ ኩባንያዎች የቴሌኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት ፈቃድ ለመሰጥት የተጀመረው የጨረታ ሒደት ተጠናቆ፣ በመጪዎች ጥቂት ሳምንታት አሸናፊዎቹ ኩባንያዎች ይፋ እንደሚደረጉ ይጠበቃል።
ጨረታውን የሚያሸንፉት ሁለት ኩባንያዎች እያንዳንዳቸው ለ15 ዓመታት የቴሌኮሙኒኬሽን አገልግሎት ፈቃድ የሚያገኙ ሲሆን፣ ከሁለቱ ኩባንያዎች የፈቃድ ክፍያ በትንሹ በአማካይ መንግሥት ሁለት ቢሊዮን ዶላር የሚጠጋ ገቢ ሊያገኝ እንደሚችል የዘርፉ ባለሙያዎች ይገምታሉ።
ለሁለት የውጭ ኩባንያዎች የቴሌኮሙኒኬሽን አገልግሎት ፈቃድ ለመስጠት በመካሄድ ላይ ካለው የጨረታ ሒደት ጎን ለጎን፣ መንግሥት በኢትዮ ቴሌኮም ላይ ያለውን 45 በመቶ ድርሻ ለመሸጥ ዝግጅት እያደረገ መሆኑ ይታወቃል።
የኢትዮ ቴሌኮም ከፊል ሽያጭን አስመልክቶ እስካሁን ከተደረጉት ዝግጅቶች መካከል የተቋሙ አጠቃላይ ሀብትና ንብረት ግመታ፣ በውጭ የኦዲት ኩባንያ ተሠልቶ መጠናቀቁና ለመንግሥት መቅረቡ ይገኝበታል።
የኢትዮ ቴሌኮም ከፊል ሽያጭ እስኪጠናቀቅ ድረስ የተካሄደው የሀብትና ንብረት ግመታ ውጤት በሚስጥር መጠበቅ ያለበት በመሆኑ ይፋ አልተደረገም፡፡ ነገር ግን የኢትዮ ቴሌኮም ሀብት በመንግሥት ከተገመተው 42 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱ ተገልጿል።
ይህንንም ተከትሎ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ከጥቂት ወራት በፊት የኢትዮ ቴሌኮምን የተከፈለ ማቋቋሚያ ካፒታል ከ40 ቢሊዮን ብር ወደ 400 ቢሊዮን ብር ማሳደጉ ይታወሳል። (ሪፖርተር)
ጎልጉል፤ የድረገጽ ጋዜጣ
Leave a Reply