
ዶ/ር አብይ የኦህዴድ ጽ/ቤት አላፊ በነበሩበት ወቅት ኦህዴድ ሁሉንም ሰላም ወዳድ ዜጋን ያስደሰተ ጥሪ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጪ ላሉ ተቃዋሚዎች አቅርቦ ነበር። ይህ ጥሪ ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ የቀረበ በመሆኑ አንዳንድ በኦሮሞ ስም የሚታገሉ በውጪም በውስጥም ያሉ ተቃዋሚዎች በደስታ የተቀበሉት ነበር። ነገር ግን ይህ የኦህዴድ ጥሪ ምንም ያህል ለሀገሪቱ ሰላም ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለው ቢሆንም ያለ ኢህአዴግ አሺታ ሊሳካ እንደማይችል የገመቱ ነበሩ።
ዶ/ር አብይ ወደ ስልጣን በመጡ የመጀመሪያዋ ቀን በፓርላማው ተገኝተው ባደረጉት ንግግር ኦህዴድ ለተቃዋሚዎች ካቀረበው ጥሪ ጋር ተመሳሳይነት ያለውን ሃሳብ ተናግረው ነበር። ጠቅላይ ሚንስተሩ በኢትዮጵያ ጉዳይ “በተለያየ መልኩ” ከሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ሀይሎች ጋር አብሮ ለመስራት እንደሚፈልጉ ጠቅሰው ነበር።
የዲስፖራው ፖለቲካ
ብዙውን ጊዜ ከኢህአዴግ ቤትና ደጋፊዎቹ በሆኑ “አክቲቪስቶች” እንደሚወራው የሀገራችን አብዛኛዎቹ የፖለቲካ ትኩሳት አባባሹና ለተከሰቱ ተራ ችግሮች የተለየ ትርጓሜ የሚሰጠውና የሚያቀጣጥለው ዲያስፖራው ነው። በእነዚህ ሰዎች “እምነት” ዲያስፖራው ዶላርና ዩሮ እየተቀበለ ሀገሪቱን በማተራመስ የውጪ ሃይሎች ማስፈጸሚያ ሆንዋል።
የዲያስፖራ ፖለቲካ በሀገራችን መታየት የጀመረው ሀገራችን የአውሮፓ ትምህርትን አካሄድ መከተል ከጀመረችበት 20ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ እንደሆነ የታሪክ ድርሳናት ይናገራሉ። ቀ/ኃይለ ስላሴ ከሸዋ መሳፍንት ይደርስባቸው የነበረውን ተግዳሮት ለመቋቋም ዲያስፖራውንና ከውጪ የተመለሰውን አውሮፓ ቀመስ ምዑር ወጣት (በዘመኑ ትንሽ ቁጥር ቢኖረውም) እንደተጠቀሙና ውጤታማም እንደነበሩ ታሪክ ያወሳናል። ይህ በዲያስፖራውና በንጉሱ መካከል የተጀመረው ጥሩ ግንኙነት ሀገሪቱን ወደተሻለ ምዕራፍ ሊያስኬዳት ቢችልም ብዙም አልዘለቀም ነበር። በ1956 ዓ.ም የተካሄደውም መፈንቅለ መንግስት ጨምሮ ሌሎችም ስር ነቀል እንቅስቃሴዎች በዲያስፖራውና ከዲያስፖራ ተመላሽ ወጣቶች የተቀነባበሩ ነበር።
ከንጉሳዊው ስርዓት ግብአተ መሬት በኃላም ቢሆን ደርግ ለዲያስፖራው (በተለይ በምዕራቡ አለም ላሉት) ቀና የሆነ አመለካከት አልነበረውም። ሁሉም በአድዓሪና አናርኪስት አይን ያያቸው ነበር። በዘመነ ደርግና ኢሰፓ የበዙ ወጣቶች በፖለቲካ አመለካከታቸው ምክንያት ከሀገር በስደት ወጥተዋል።
የትግራይ ህዝብን ብሶት በመያዝ ደርግን ለመናድ በረሃ የወረደው ህወሃት ምንም እንኳን በረሃ በነበረበት የመጀመሪያዎቹ አመታት ከዲያስፖራው ጋር ጥሩ ግንኙነት ነበረው ማለት ቢቻልም ኢህአዴግ/ህወሃት 4 ኪሎ ከገባባት ሰአት ጀምሮ ግን ይህ ግንኙነት ጥሩ ባልሆነ መልኩ ተቀይሯል።
ባለፉት 100 አመታት ሀገሪቱን ያስተዳደሩት መንግስታት በመጀመሪያ የስልጣን ዘመናቸው ከዲያስፖራው ጋር ጥሩ ሊባል የሚችል ግንኙነት ቢኖራቸውም ዘላቂ ግን አይደለም። ሁሉም ማለት በሚያስችል መልኩ ዲያስፖራውን በአንድ አይነት መልካም ያልሆነ አመለካከት ነበር የሚመለከቱት። ይህ መሆኑ ደግሞ ሀገሪቱን እጅጉ ጎድቷታል።
ነገር ግን በ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ያለው የአለም ነባራዊ ሁኔታ ዲያስፖራውን የትም ሆኖ እንደልቡ በሀገሩ አጠቃላይ ጉዳይ ያለምንም ፍራቻ እንዲሳተፍ አስችሎታል። ይህ ዲያስፖራው ያለው ጥሩ አጋጣሚ (የቴክኖሎጂ፣ እውቀትና የነጻነት) አሁንም በሀገሪቱ ሁኔታ ከማንም በላይ ተሳታፊ እንዲሆንና በሀገር ውስጥ ያለውን ህዝባዊ ብሶት እንዲቀጣጠል አስችሎታል። ስለዚህ በሀገሩ ጉዳይ የሚሳተፈውን ዲያስፖራው እንደ ሀገር ጠላትና ከሃዲ በማየት የሀገሪቱን ሰላም ማምጣት ከባድ ነው።
ተስፋ ያሣጡ የሀገር ውስጥ ተቃዋሚዎች
በዲሞክራሲያዊ ስርኣት ስልጣን ሊገኝ የሚችለው በሰላማዊ መልኩ በሚደረግ ፉክክርና ምርጫ ብቻ ነው። እንዳለመታደል ሆኖ ለዚህ ኢትዮጵያውያን የታደልን አይደለንም (በቅርቡ የተደረገው የስልጣን ሽግግር በአንድ ፓርቲ ውስጥ እንጂ የስርአት ለውጥ አይደለም)። በዲሞክራሲያዊ መልኩ ለመወዳደርና ስልጣን ለመያዝ የበዙ ጉዳዮች መሟላት አለባቸው። ከእነዚህ ጉዳዮች ዋናው ግን ህዝብ በተቃዋሚዎችና በስልጣን ላይ ባለው ፓርቲ ላይ ያለው አመኔታና ድጋፍ ነው።
ኢትዮጵያ በአለም ደካማ የፖለቲካ ፓርቲ ስርአት ካላቸው ሀገራት ግንባር ቀደሟ ነች። መረጃዎች እንደሚጠቁሙት አንዳንድ በሰላማዊ መልኩ በሀገራችን የሚንቀሳቀሱት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ከመስራቾቹ ቤተሰብ በቀር ምንም ድጋፍ የሌላቸው፣ አንዳንዶቹ እስከነ መኖራቸው እንኳን በህዝብ የማይታወቁ፣ በቅጡ አባልና አማራጭ ፖሊስም ሆነ እስትራቴጂ የሌላቸው፣ አብዛኛዎቹን ደግሞ የኢህአዴግ ሰዎች እራሳቸው በእጅ አዙር የሚያሽከረክሯቸው መሆናቸው የአደባባይ ሚስጥር ነው። ይህ ሁኔታ ህዝቡ በተቃዋሚዎቹ ተስፋ ቆርጦ በዲያስፖራውና ውጪ ባሉት ተቃዋሚዎች ተስፋ እንዲያደርግ ያስገደደው ይመስላል።
ለዘላቂ ሰላም ሁሉን አሳታፊ ውይይት
ባለፉት ጥቂት አመታት ወዲህ በሀገራችን በተለያዩ አካባቢዎች የታዩት ክስተቶች እንደጠቆሙት በስልጣን ላይ ያለው አካል እንደ ከዚህ ቀደሙ በማስፈራራት ወይም ስም በመስጠት የፖለቲካ እድሜን ማራዘም የሚቻለው አይደለም። ዶ/ር አብይ እንዳሉትና በአንዳንድ ሀቀኛ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ሲባል እንደነበረው ሁሉን የፖለቲካ ሃይሎች ያካተተ ውይይት በተለያዩ ሀገራዊ ጉዳዮች በፍጥነት ሊካሄድ ይገባል።
ዶ/ር አብይ ሊያደርጉት የሚገባው እንደ ከዚህ ቀደሞቹ የኢህአዴግና የተቃዋሚዎች የይስሙላ ውይይቶች ሳይሆኑ ትክክለኛ ያልሆነ ታርጋ የተለጠፈባቸውን ጨምሮ በውስጥም በውጭም ከተደራጁ ሃይሎችና ስለዚህች ሀገር ጉዳይ ይመለከተናል ከሚሉ አካላት ጋር መሆን ይኖርበታል።
ዳንኤል መኮንን ይልማ
በወልቂጤ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካል ሳይንስ መምህር
ኢሜል፦ yalewyalew3@gmail.com
“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ። ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ™ አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው።
Leave a Reply