• Skip to primary navigation
  • Skip to content
  • Skip to primary sidebar

Goolgule

Ethiopian News

  • ስለ እኛ/about
  • አስፈንጣሪዎች/links
  • ቤተ መዝገብ/archives
  • አድራሻችን/contact
Header Banner Image
  • Home
    ዋና ገጽ
  • Editorials
    ርዕሰ አንቀጽ
  • News
    ዜና
  • Socio-Political
    ማኅበራዊ-ሽከታ
  • Religion
    ሃይማኖታዊ
  • Interviews
    እናውጋ
  • Law
    የሕግ ያለህ
  • Opinions
    የኔ ሃሳብ
  • Literature
    ጽፈኪን
    • Who is this person
      እኚህ ሰው ማናቸው?
  • Donate
    ለባለድርሻዎች

ቴሌን ደህና ሰንብት?

January 5, 2013 03:39 am by Editor 1 Comment

የቀድሞው የኢትዮጵያ ቴሌኮሙኒኬሽን ኮርፖሬሽን ስሙን ቀይሮ “ኢትዮቴሌኮም” በሚል ከተሰየመ በኋላ አስተዳደሩን ለፈረንሳዩ ፍራንስ ቴሌኮም ማስረከቡን ተከትሎ ኢህአዴግ ለወደፊቱ ያቀደውን እቅድ ይፋ የሚያደርጉ መረጃዎች ለንባብ በቅተዋል። በዛሬው እለት የመገናኛና የኢንፎርሜሽን ሚኒስትር ዶ/ር ደብረጽዮን ገ/ሚካኤል “ቴሌ ከዚህ በኋላ ለውጪ ካምፓኒ አይሰጥም። በአገር ውስጥ ባለሙያዎች ይቀጥላል” ሲሉ የማሳረጊያ ንግግር አሰምተዋል። የሚኒስትሩን ንግግር ያደመጡ “ቴሌን ህወሃት ጠቀለለው” የሚል አስተያየት ሰጥተዋል።

የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ “አዲሱ ቴሌና ኢንሳ” በሚል ርዕስ ከወራት በፊት ለንባብ ባበቃው ጥናታዊ ጽሁፍ እንዳስታወቀው ቀደም ሲል “አዲሱ ቴሌ” በሚል አሮጌው ቴሌን የሚረከቡ የህወሃት ሰዎች የበዙበት፣ ለማዛነቂያ ከተለያዩ ብሄሮች በጣም ጥቂት ተተኪዎችን በማካተት ስልጠና ሲያካሂድ ነበር።

በህወሃት ሰዎች የሚመራውን የብሄራዊ መረጃና ደህንነት ተቋም (NISS) ዘመናዊ ለማድረግ ኢንሳን ሲያቋቁም ዋናው ዓላማው ከቴሌ ጋር በማቆራኘት ነበር። በጥናቱ እንደተገለጸው አሮጌው ቴሌ ውስጥ ያሉት አገር ወዳዶች ለተፈለገው የስለላ ስራ የሚታመኑ ባለመሆናቸው ሰራተኞቹን በሲቪል ሰርቪስ ማሻሻያ ስም ተጠራርገው እንዲወጡ ተደርጓል።

የፈረንሳይ ቴሌኮም ቴሌን እንዲረከብ ስለመደረጉ “ህወሃት አዲሱ ቴሌ በሚል እያሰለጠነ ያዘጋጃቸው የራሱ ሰዎች አሮጌውን ቴሌ ባደባባይ እንዲረከቡ ማድረግ የሚያስነሳውን ተቃውሞ በጥራትና በአገልግሎት ኋላቀርነት እንዲሁም በውጪ ካምፓኒ አሳብቦ ለመስጠት የማመቻቸት ስራ ለመስራት” መሆኑ አካሄዱ የገባቸው የቴሌ የበላይ ሃላፊዎች ውስጥ ውስጡን የሚያወሩት ጉዳይ ነበር።

ከፍተኛ በጀት መድቦ በአሜሪካን አገር ባለሙያዎች ስልጠና ሲሰጣቸው የነበሩት የአዲሱ ቴሌ ምልምሎች ዝግጅታቸው ከተጠናቀቀ በኋላ መረጃዎች በማፈትለካቸው፣ አዲሱ ቴሌ “ኢትዮቴሌኮም” በሚል ተቀይሮ ለፈረንሳይ ኩባንያ አስተዳደሩ በኮንትራት እንዲሰጥ ተደረገ። በወቅቱ ውሉ በየሁለት ዓመቱ እንደሚታደስ ይፋ ተደረገ። ከሰባት ሺህ በላይ የአሮጌው ቴሌ ሰራተኞች እጣ ፈንታ ፍርድ ቤት መመላለስ ሲሆን፣ አዳዲሶቹ የፈረንሳዩን ኩባንያ እየታከኩ ቴሌን እንዲወሩ መደረጉን ሰለባዎቹ ይፋ አደረጉ። መንግስት ውሳኔው አስተዳደሩን የያዘው አካል እንደሆነ በመጥቀስ “የተባረሩት ሰራተኞች ተደራጅተው መስራት ከፈለጉ አደራጃቸዋለሁ” አለ።

“መተካካቱ” ከተጠናቀቀ በኋላ ፍራንስ ቴሌኮም ስራ እንደጀመረ በስራው ጥራት የሌለው፣ ደካማ ምዘና እንዳለውና ካላስተካከለ ውለታው ሊሰረዝ እንደሚችል ማስጠንቀቂያ ይሰጠው ጀመር። በተለይም ከስድስት ወር በፊት የቦርድ ሰብሳቢው ዶ/ር ደብረጽዮን ኩባንያው ሊባረር እንደሚችል አስረግጠው ተናገሩ። አስቀድሞ ለተጠና ምክንያት እና ቴሌን ከኢንሳ ጋር በማጋባት በቴሌኮሙኒኬሽን ዘርፍ (ስልክ፣ ኢተርኔት፣ …) ከፍተኛ የስለላና የቁጥጥር መረብ ለመዘርጋት በታሰበ ዕቅድ ፍራንስ ቴሌኮም ሽፋን እንዲሆን መጠቀሚያ መደረጉ እየታወቀ ዶ/ር ደብረጽዮን ይህንን መሰሉን ነቀፋ መሰንዘራቸው የሙያውን ባለቤቶች በወቅቱ ያስደመመ ጉዳይ ነበር፡፡ ይህንኑ የድብብቆሽ ሥራ በተመለከተ የአኢጋን ጥናታዊ ዘገባ አዲሱ ቴሌ ለማዋቀር በሚል የፍራንስ ቴሌኮም እንዴት የሽፋን መጠቀሚያ እንደሆነ አስቀድሞ በዝርዝር አስረድቷል፡፡

አርብ ታህሳስ 26፤ 2005 ዓም ኢቲቪ በዜናው እንዳረጋገጠው ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎትና ጥራት ያለው አገልግሎት ለመስጠት፣ በእውቀት ሽግግር በኩል ውጤታማ መሰረት በመጣሉ በዛሬው ዕለት ኢትዮ ቴሌኮም በአገር ልጆች እንዲመራ በተወሰነው መሰረት ርክክብ መፈጸሙን ይፋ አድርጓል።

ዶ/ሩ በመጀመሪያ አድንቀው “በሞባይልም ሆነ፣ በኢንተርኔት ጥራት ተገልጋዩ የረካበት ሁኔታ የለም” በማለት ቅር መሰኘታቸውን አስታውቀዋል። አያይዘውም “የእኛ ልጆች ውጪ ሄደው ተምረዋል። እዚህ ሆነውም ስራውን አውቀዋል። ከዚህ በኋላ ኢትዮ ቴሌኮም ለውጪ ኩባንያ አይሰጥም” ብለዋል። በዘገባው እንደተገለጸው ከፈረንሳይ ከመጡት 24 ባለሙያዎች መካከል ዋና ስራ አስኪያጅና ምክትላቸው አዲሶቹን አመራሮች ለመርዳት እንዲቆዩ ሲደረግ፣ የተቀሩት ወደ አገራቸው ተሰናብተዋል። ጎልጉል ያነጋገራቸው የቀድሞ ቴሌ ሠራተኛ በጉዳዩ ላይ ዝርዝር ከመስጠት ይልቅ ዶ/ር ደብረጽዮን “የእኛ ልጆች” ያሏቸው እነማን እንደሆኑ ቢዘረዝሩ የተሻለ ነበር በማለት ንግግሩን አጣጥለውታል፡፡

ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑ ምንጮች ለጎልጉል እንዳሉት “ቴሌን ፕራይቬታይዝ የማድረግ ጥያቄና ምላሹ በቅርቡ ይፋ ይሆናል። የመጀመሪያው ባለድርሻ ኤፈርት እንደሚሆን ጥርጥር የለውም። ይህ ሲሆን የኢትዮጵያ ቴሌኮሙኒኬሽን ባለሥልጣን መጨረሻ ይሄው ነው” ብለዋል። ኤፈርት አሁን ከጀመረው የማዕድን ዘርፍ እንቅስቃሴ በተጨማሪ በቴሌኮም ስራ ለመሰማራት እቅድ እንዳለው በተለያዩ መገናኛዎች መዘገቡ አይዘነጋም።

ርክክቡ ይፋ ከመደረጉ ሁለት ቀን በፊት ሪፖርተር እንደዘገበው ፍራንስ ቴሌኮም በሁለት ዓመታት ጊዜ ውስጥ የተጠቀሱትን በመንግሥት የታለሙ ግቦች ለመምታት የሚያስችል ብቃት ያለው መሆኑ በመረጋገጡ እንደተመረጠ በወቅቱ ይፋ የተደረገ ሲሆን፣ 30 ሚሊዮን ዩሮ ለኩባንያው መክፈል ደግሞ ከመንግሥት የሚጠበቅ ኃላፊነት ነበር፡፡

የሁለት ዓመታት የኮንትራት ጊዜው እ.ኤ.አ. ታኅሳስ 23 ቀን 2012 ያጠናቀቀው ፍራንስ ቴሌኮም በተጠቀሱት ዓመታት ውጤታማ ሥራዎችን ማከናወኑ ቢነገርም፣ ከኢትዮጵያውያን ባለሙያዎች በእጅጉ የተለየ ሚና እንዳልነበረው ሲተች ቆይቷል፡፡ ይሁን እንጂ በመንግሥት በኩል ኢትዮ ቴሌኮምን በውጭ ኩባንያ አማካይነት በማስተዳደር ስለተገኘው ውጤት በይፋ የተገለጸ ነገር የለም፡፡ በኮንትራት ስምምነቱ ሰነድ መሠረት ፍራንስ ቴሌኮም በሚያስመዘግበው ውጤት የኮንትራት ጊዜው እንደሚራዘም ይገልጻል፡፡ በዚህም መሠረት ኩባንያው ጥያቄውን ለሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ቢያቀርብም ተቀባይነትን አላገኘም፡፡ ከዚህ ይልቅ ኢትዮጵያውያን ባለሙያዎች አስተዳደሩን እንዲረከቡ በመንግሥት መወሰኑን ሰሞኑን በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የተሾሙት ዶ/ር ደብረፅዮን ገብረሚካኤል ከዚህ ቀደም ለሪፖርተር መግለጻቸው ይታወሳል።

ከመቶ ዓመት በፊት አጼ ምኒልክ ለኢትዮጵያ የቴሌኮሙኒኬሽን ጥበብን ቢያስተዋውቁም እስካሁን ድረስ ኢትዮጵያ በዘርፉ ተገቢውን ዕድገት ሳታካሂድ ቀርታለች፡፡ ዓለማችን በ21ኛ ክፍለዘመን ፈጣን የቴሌኮሙኒኬሽን ምጥቀት እያሳየ ባለበት ባሁኑ ወቅት በህወሃት/ኢህአዴግ አገዛዝ ከሁለት ዓስርተ ዓመታት በላይ የተገዛችው ኢትዮጵያ አገር ከሌላት ሶማሊያ ሳትሻል በመገኘቷ እጅግ በርካታ ወገኖች አገር ውስጥም ሆነ ውጪ በሚታተሙ የሚዲያ ውጤቶች ቁጭታቸውን ሲገልጹ ቆይተዋል፡፡ ከዚህም አንጻር ህወሃት/ኢህአዴግ በአገዛዝ በቆየባቸው 21ዓመታት ለበርካታ ጊዜያት ቴሌ ወደ ግል ይዞታ እንዲቀየር (አገዛዙ ውስጥም ባሉ ጭምር) ጥያቄ  ቢቀርብም ኢህአዴግና አቶ መለስ የቴሌን ጉዳይ እስካሁን ይዘው የቆዩት የስለላ መረቡን እና ታማኝ ተዋናዮቹን በሙያው አሰልጥኖ እስኪያዘጋጅና በትርፍ በኩል ደግሞ ኤፈርት ተጠቃሚ እንዲሆን ለማድረግ በቂ ጊዜ ሲያመቻች መቆየቱን በአኢጋን ዘገባ የተጠቀሰ ሲሆን ቴሌ በበኩሉ ደረጃውን በማሻሻል እድገት ማስመዝገቡን ይናገራል። ኢህአዴግ ቴሌን “የምትታለብ ላም” እያለ እንደሚጠራው ይታወሳል።


ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ®ንብረት ናቸው፡፡ ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (https://www.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን፡፡

Print Friendly, PDF & Email
facebookShare on Facebook
TwitterTweet
FollowFollow us

Filed Under: News Tagged With: Full Width Top, Middle Column

Reader Interactions

Comments

  1. በለው ! says

    January 6, 2013 07:06 pm at 7:06 pm

    ከመንገድ ሥም እስከ አካሄድ… ከክፍለ ሀገር እስከ ቀበሌ.. ከግለሶች ሥም እስከ ድርጅት ምን ያልተቀየረ ያልፈረሰ አለ? ሲፈርስ እና ሲቀየር የሚያመጣው ፋይዳ መበተን, ማጋጨት, ማተራመስ, የጥቂት ቡድኖችን ባለቤትነት ማንገስ የሥርዓቱ ጠቃሚና ታማኝ ጫጩቶችን ፈልፍሎ ማራባት ብቻ ነው። የቀድሞው የኢትዮጵያ ቴሌኮሙኒኬሽን ኮርፖሬሽን ስሙን ቀይሮ “ኢትዮቴሌኮም”ሲሆን በህወሃት ሰዎች የሚመራውን የብሄራዊ መረጃና ደህንነት ተቋም (NISS) ዘመናዊ ለማድረግ ሳይሆን ቃሉ እራሱ (እኩሌታ ድረሻ )ማለት እንደሆነ እንረዳ!?ይህ የተደረገው የባለቤትነት (የአስተዳደር)ለውጥ ኢትዮጵያ በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ በቂ ባለሙያዎችን አፍርታ ከፈረንሳይ ባለሙያዎች የተሻለ ሥራ የሚሠሩ የኢህአዴግ አባላት አሜሪካ ተገኙ የሚለው ቱማታ… ዶክተሩ ከወዲሁ “ዶከኩ”። እርግጠኛ ነኝ ከተባረሩት ነባር የቴሌ ሠራተኖች ውስጥ አደለም።ግን የዚች ሁለት ዓመት ኮንትራትና የኮንትራት ማቋረጥ ዓላማ ነገሩ ሌላ ነው አስተዳደርን(ባለቤትነትን) በመለወጥ(…) ነባር ሠራተኛን ለፓርቲው ካልተገዛ ማብረር፣ ከጡረታ፣ ከአገልግሎት ዘመን መቀነስ፣ ከሚስጥር ዕውቀት ማግለል፣ ከሙያ ተካፋይት ማራቅ፣ከሥራ ልምድና ዕድገት ማሸሽ፣ለሥርዓቱ ታማኝ የሆነን ቤተሰብ, ዘርና ነገድን መሠረት ያደረገ አንድ ወጥ (ህገ መንግስቱ) እንደሚጠቅሰው ‘በአንድ የፖለቲካ ጥላ ሥር የመሰባሰብ አሠራር…በሁሉም ታላላቅ ኩባንያ ድርጅቶችና ተቋማት ሁሉ ለገዢው ፓርቲ የሥልጣን ማስቀጠያ የንፁሀን ዜጎችን ማቃጠያ ማዋቀር።ለዚህም ‘በክላስተር’ አሠራር ሳይሆን “ክላስተር ቦምብ”ማጥመድ ይሆናል!።

    ከሰባት ሺህ በላይ የአሮጌው ቴሌ ሰራተኞች እጣ ፈንታ ፍርድ ቤት መመላለስ ሲሆን፣ አዳዲሶቹ የፈረንሳዩን ኩባንያ እየታከኩ ቴሌን እንዲወሩ መደረጉን ሰለባዎቹ ይፋ አደረጉ። መንግስት ውሳኔው አስተዳደሩን የያዘው አካል እንደሆነ በመጥቀስ “የተባረሩት ሰራተኞች ተደራጅተው መስራት ከፈለጉ አደራጃቸዋለሁ” አለ። ሰባት ሺህ ሠራተኛ እያንዳንዱ ቢያንስ ከትዳር አጋርና ከአንድ ልጅ ጋር ሲሠላ…በአንድ የፈረንሳይ ኩባንያ በተሰጠው ውል በ፳፬ ባለሙያዎችን ወደ ሀገር በማስገባት ፳፩ ሺህ ኢትዮጵያዊ ዜጋን እንዲተካ ተደርጓል ማለት ነው!።አሁንም አበክሬ እደግመዋለሁ “የብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ሲል”…’ብሔር’ ማለት(አውራው ፓርቲ ጤፍ መብላት ስኳር መላስ ያስተማረህ ማለት ነው!።) ‘ብሔረሰቦች’ ማለት ጥንት ያልነበሩ ማንነታቸው ያልታውቀ ኢህአዴግ ፈልጎ ያገኛቸው ዘፈንና መጨፈር ተነፍገው የነበሩ አሁን የአጫፋሪነትንም(አዳማቂ)ሆነው የሚያገለግሉ ‘ሆድአደር’ የሚሏቸው ቀለም ቆጠሩን ያካትታል። ‘ሕዝቦች’ መጀመሪያ በውጭው ዓለም ማጭበርበርን መስረቅን መግደልን መዝረፍን በደንብ የተካኑ “ዲያስፖራ”(ፈላሽ) ሆነው ወደ ድሃውና የዋሁ ሕዘብ አስጨብጭበውና አስጨፍረው ሊግጡት የተመለሱ ሲሆኑ ሌሎች ተከትለው የሚመጡ አዛኝ ቅቤ አንጓች በንግድ፣ በግብርና፣ በቴክኖሎጂ፣ በጤና፣ በትምህርትና በሕክምናው ዘርፍ ((ከጥቂት ልበ ብርሃን በቀር))አብዛኛዎቹ ነዋሪውን ዜጋ ከመተካት እስከማጥፋት በማጅራት መቺነት የተሰማሩ ወሮበሎች ይሆናሉ። እንግዲህ “ቤታቸውን ሳይዘጉ ሰው ሌባ ይላሉ” የሚለው በእኛ ደርሷል ወጣቱ ትውልድ “እንቢኝ በሀገሬ!”… “እንቢኝ በመብቴ!” ሊል ግድ ነው… እንቢኝ ባለ ነው መይሳው! እንቢኝ ባለ ነው ምን ይልክ! ሸዋ ንቃ በለው!! በቸር ይግጠመን ከሀገረ ካናዳ

    Reply

Leave a Reply Cancel reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *

Primary Sidebar

በማኅበራዊ ገጾቻችን ይከታተሉን

Follow by Email
Facebook
fb-share-icon
Twitter
Tweet

Recent Posts

  • የሲኖዶሱ ውዝግብ አካሄድና መጪው የአፍሪካ ኅብረት ጉባዔ February 6, 2023 02:03 am
  • የእሁዱ ሰላማዊ ሰልፍ ተራዘመ፤ ተጠባቂው ዕርቅ ፍንጭ እያሳየ ነው February 3, 2023 05:17 pm
  • የብላቴ: የውጊያ ማርሽ ቀያሪ ሠራዊት መፍለቂያ ማዕከል February 3, 2023 10:06 am
  • በኢትዮጵያ 27 በመቶ የሚሆነው የአእምሮ በሽተኛ ነው ተባለ February 3, 2023 09:47 am
  • “አስደንጋጭ”! 1 ሚሊዮን ከሚጠጋ ተፈታኝ ተማሪ ወደ ዩኒቨርሲቲ የሚገባው 30 ሺህ (3.3%) ብቻ ነው  January 27, 2023 09:11 am
  • የማይዘነጋዉ የኢትዮጵያዊያኖች የጀግንነት ተጋድሎ ታሪክ፡- ኮሎኔል ባጫ ሁንዴ (ታጠቅ) January 27, 2023 06:12 am
  • ጎርጎራ – የመጻዒው ዘመን ሙሽራ! የዉበት ፈርጥ! January 17, 2023 04:18 pm
  • ሁለተኛው መስቀል አደባባይ January 17, 2023 04:13 pm
  • በአቡዳቢ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን January 17, 2023 04:08 pm
  • በንፋስ ስልክ ላፍቶ ስምንት የመሬት ሌቦች ተያዙ January 16, 2023 11:36 am
  • ሺሻ ሲያስጨሱ በተገኙ ሆቴሎችና የምሽት ጭፈራ ቤቶች ላይ እርምጃ ተወሰደ January 16, 2023 08:50 am
  • በሐሰተኛ መታወቂያ የደኅንነት አባል ነን ብለው ሲያጭበረብሩ የነበሩ ተያዙ January 13, 2023 02:03 pm
  • ተሽከርካሪ ወንበር ለትግራይ – “ናይ ኣካል ጉዱኣት ተሽከርካሪ ዘለዎ ወንበር” January 12, 2023 07:17 pm
  • የአማራው ኩራት፣ የኢትዮጵያ ዘብ፣ የትህነግን ቅስም ሰባሪ! January 12, 2023 04:00 pm
  • በኢትዮጵያ ላይ የተጣሉ ማዕቀብ እና ሌሎች አስገዳጅ ሕጎች ሙሉ ለሙሉ ተሰረዙ January 12, 2023 01:52 pm
  • የቻይና ዕዳ ስረዛ “Payday Loan Diplomacy” ወይስ ኢትዮጵያን ያዳነ ተግባር? January 12, 2023 11:00 am
  • የአዲስ አበባ አስተዳደር ከቋንቋ ጋር በተያያዘ ውሳኔ አስተላለፈ January 12, 2023 10:46 am
  • “አምባሳደሩ” የቀድሞ ጌቶቻቸውን እንዲያቋቁሙ ተሾሙ January 11, 2023 03:47 pm
  • መከላከያ ሸኔን የሚዋጉ ሚሊሻዎችን አሠልጥኖ አስመረቀ January 10, 2023 05:37 pm
  • በሰባት ተጠርጣሪዎች ላይ ከባድ የሙስና ወንጀል ክስ ተመሰረተ January 10, 2023 03:36 pm
  • የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አቅጣጫ January 6, 2023 03:26 pm
  • “ከዕብሪቱ አስተንፍሰነዋል” – ኢሳያስ January 2, 2023 07:29 pm
  • [ኢትዮጵያን] “አስታክኮ ኤርትራን መውጋት ለሚፈልግ ኃይል አንተባበርም” January 2, 2023 07:11 pm
  • የ፰ ወር ሕጻንና ጨቅላ ወንዶች የሚደፈሩባት ትግራይ December 14, 2022 02:49 pm

ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣን በኢሜይል ለማግኘት ይመዝገቡ Subscribe to Golgul via Email

ከዚህ በታች ባለው ሣጥን ውስጥ የኢሜይል አድራሻዎን ያስገቡና “Subscribe” የሚለውን ይጫኑ፡፡
Enter your email address to receive notifications of new posts by email.

Copyright © 2023 · Goolgule