
ኦቦ ለማ መገርሳ ህወሃት ያጎራቸውን 2,345 እስረኞች ነጻ አወጡ የሚለውን ዜና በቀኝ እየሰማን፣ የገዱ አንዳርጋቸው መግለጫ ደግሞ በግራ በኩል ብቅ አለ። ሰበር ጋዜጣዊ መግለጫ። በርግጥም “ወገብ የሚሰብር”። ልዩ መግለጫው ተከባብዶ ሲነገረን “ገዱ ደግሞ ስንት ሺህ አማሮችን ከእስር አስለቀቀ” እያልን በጉጉት ባንጠብቅም “የኢትዮጵያ ሕዝብ እና ሕዝቦች ሆይ በወልድያ እና በቆቦ ለተፈጸመው እልቂት ተጠያቂው እኔ የምመራው ብአዴን ነው” ብሎ አረፈው።
ይህቺ ሃላፊነት የመውሰድ ዲስኩር ደግሞ አዲስዋ ቅኝት መሆነዋ ነው። ለትርጓሜዋ ቱርጁማን የማያሻት ቅኝት። ማራቶን ያሉት የአራቱ ድርጅቶች ስብሰባ እንዳበቃ አይቴ ደብረጽዮን ገብረ-ሚካኤልም ረገጥ ዓድርጎ ብሏታል። የናቴ ቀሚስ አድናቅፎኝ … ምናምን የምንለው ነገር የለም። ለጠፋው ጥፋት ሁሉ ሃላፊነቱን ወስደናል። ብሎ ተነግሯል። ይህንን የተናገረው በህልም ሳይሆን በውን ነበር። በአለም መገናኛ ስንሰማ ያደግነው፤ ሰላማዊ ዜጋ ላይ እንዲህ አይነት አደጋ ሲደርስ ሃላፊነት የሚወስዱት እነ ሙጃህዲን፣ እነ አልቃይዳ እነ አይሲስን ነበሩ።
ደብረጽዮን በኢቢሲ ቀርቦ ለእልቂቱ እና ለውድመቱ ተጠያቂዎቹ “እኛ ነን” ብሎናል። የጥልቅ ተሃድሶው ጥልቅ ድፍረት! ንቀትም ነው። ታድያ የፍትህ ስርዓቱን እነ ዳኛ ዘርዓይ ባይይዙት ኖሮ፣ ለጥፋቱ ተጠያቂ መሆናቸውን ያመኑት ሁሉ ማእከላዊ (ሙዝየም) ገብተው በሕዝብ ይጎበኙ አልነበር?
ገዱ አንዳርጋቸውስ ይህን ለማለት ምን ያንሰዋል? ቅርቃር እንደገባች አይጥ እየተቁለጨለጨ ሃላፊነቱን እወስዳለሁ ብሎ ሲናገር ሰማነው። በእርግጥ የደብረጽዮን እና የገዱ አገላለጽ የተለያዩ ናቸው። የደብረጽዮን “ገድለናል። ምን አባክ ታመጣለህ” አይነት ቅኝት ያለ የተረገጠ አነጋገር ሲሆን ገዱ ግን እየረገጠ ሳይሆን እየተረገጠ የሚናገር ነው የሚመስለው። ከካሜራ ጀርባ ወይ ላውንቸር፣ አልያም የስኳር ደብተር ያለመኖሩንስ ማን አየ?
ቴሌቭዝኑ ላይ ወጥቶ እንዲህ አይነት አስገራሚ መግለጫ የሚሰጠው “ገዱ ነው ወይንስ ደብረጽዮን?” ብሎ ያልተጠራጠረ ቢኖር፣ የፍራንስ ፋነንን “black skin white mask” የሚል መጽሃፍ ያነበበ ብቻ ነው። ሃብትና ንብረቱን፣ አለፍ ሲል ደግሞ አካሉን እና አእምሮውን የተሰለበ ሰው ስነ-ልቦና።
ይህ የመግለጫ ገቢር፣ ገዱ አንዳርጋቸው ከ”በላይ” አካል ተጽፎ የተሰጠውን ይህን መግለጫ ለማንበብ ሲጨናነቅ በግልጽ ያሳየናል። ወረቀቱ ሲዝረከረክበት የሚያሳየውን ቦታ እንኳን ሳያርሙ ነው የለቀቁት። ምንም ያህል ስኳር ቢልስ፣ ምንም ያህል ያልተከፈለ እዳ ቢኖርበት፣ ሰውዬው በዚህ ደረጃ ይጃጃላል ብሎ ማሰብ ግን ይከብዳል። ለእልቂቱ ሃላፊነቱን ይውሰድ፣ ግን ጽላት ላይ በድፍረት የማስተኮስ ሃላፊነትን መውሰድ ከጤነኛ ሰው ይጠበቃል?
የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ለሰራተኞቹ በለቀቀው የውስጥ መልእክት ግድያውን “የትግራይ ወታደሮች” መፈጸማቸውን በግልጽ አስቀምጦታል። የወልድያው እልቂት በተባበሩት መንግስታት ድርጅት መወገዙ ሰዎቹን ብርክ አንዳስያዛቸው ቢታወቅም፣ ይህንን “የኒዮ ሊብራሎች ሴራ” ለማፍረስ፣ ገዱ አንዳርጋቸው ለመስዋእትነት እንደቀረበ ከብት በአደባባይ ወጥቶ ሂሱን ውጧል። ገዱ ያለ ሃጥያቱ የወንጀለኞቹን መስቀል ለመሸከም የመፍቀዱ ምስጢር ግን ግልጽ አይደለም። አንዱ የበላውን ሌላው እንዴት ይውጠዋል?
እኚህ ሰው ልብ ገዝተው ከህወሃት ሰዎች ጋር እኩል መናገር ሲጀምሩ፣ “ወፌ ቆመች…” ብለን ሳንጨርሳት፣ ይኸው ደግሞ ሃሞት እንደሌለው ሰው ሲልፈስፈሱ አየን።
ደብረጽዮን፣ “ሁሉንም ሳይሆን ትምክህተኛውን አማራ፣ ሁሉንም ሳይሆን ጠባቡን ኦሮሞ እየነጠልን መምታት ነው ያለብን!” ብሎ በትግርኛ ትዕዛዝ ካስተላለፈ ወር አልሞላውም።
ከዚህ ቀደምም በአማራው ላይ ጦርነት ሲያውጅ እንዲህ ነበር ያለው “… መከላለያ ሃይላችን እንኳንስ ለ30 ሚሊዮን (የአማራ) ሕዝብ አይደለም፤ መላው አፍሪካን ለመደምሰስ አቅም እንዳለው የተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማት ያረጋገጡት ሃቅ ነው። … የመከላከያ ኃይላችን በሙሉ ትጥቅ በመሆን ብጥብጡ ወደከፋባቸው አካባቢዎች በመሄድ አስፈላጊውን እርምጃ ሁሉ እንዲወስድ በጠቅላይ ሚኒስትራችን ታዟል።”
አካባቢው የተጠራቀሙ ችግሮች አሉ ተብለናል። ችግሩን ለመፍታትም ልማታዊው መንግስት ብዙ ይሰራልም ብለዋል። “ይሰራል” የሚለውን ቃል የተናገሩት ተሳስተው ካልሆነ በቀር ከደብረጽዮኑ ድንፋታ ጋር የሚጋጭ ነው። እናም ድርጅታቸው ብዙ ይሰራል የሚለው ቃል ብዙ “ይገድላል” ነው የሚሆነው። ለችግሮች እና ለጥያቄዎች ሁሉ መፍትሄያቸው አፈሙዝ ስለሆነ!
ገዱ ሃላፊነቱን ወሰደም አልወሰደ፣ በነባራዊው እውነታ ላይ የሚለወጥ ነገር አይኖርም። ያልበላውን ማከኩ ግን ራሱን ምን ያህል ለህወሃት ተገዥ እንዳደረገ ያሳየናል። በወሎ ለፈሰሰው ደም ተጠያቂው ማን እንደሆነ ወንዙ ላይ ስንደርስ እናወራዋለን። የመከላከያ ሚኒስትሩን የሚመራው ሲራጅ ፈርጌሳ እና አዛዥ ነኝ የሚለው ሃይለማርያም ደሳለኝም ቢሆኑ በዚያን ግዜ “ግድያውን እኛ አላስፈጸምንም። በቦታው እንደ አሻንጉሊት ነው የተቀመጥነው… እትት እትት” ቢሉ ማንም አይሰማቸውም። የኑረንበርጉን ችሎት ያስተውሏል!
ግን አንድ ነገር ልብ እንበል። ወያኔ ፊቱን ወደ ወሎ ሲያዞር የተሳሳተ ቁልፍ ነው የነካው። ሰላም ባስ ዛሬ ከአዲስ አበባ በአፋር ዞራ ትግራይ ትገባ ይሆናል። ነገ ደግሞ በሱዳን…
ክንፉ አሰፋ
“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ። ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ™ አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው።
መቼም ሰዎች!! ወፍ ስትጮህ ንጋትን ታበስራለች ይባል ነብር። ሌሊት ማለቴ ነው!!! የቁራ ጩኸት ግን ግራ እያጋባን ወፍ ትሆን?? ኧረ ሌቱ ነጋ እያልን ነው!!!ቂቂቂቂቂቂ!!!!!!
* ህወሓት/ኢህአዴግ ተሰብስበው ለጦመሩም ይሁን፡ ለዘመሩ፡ ወይም ድማፃቸውን ላሰሙ ‘ተመጣጣኝ እርምጃው’ ግንባርና ደረቱን በአልሞ ተኳሽ ማስበርቀስ ነው።ድሮስ የተናቀ ሠፈር..!የመጀመሪያ ሞታችን ወደብ አልባ እንደከብት ስንከለል።
*የአማራና ኦሮሞ ወጣት ወንድምና እህቱ ከጎኑ እንደቅጠል ሲረግፍ የሚሰጠው ተመጣጣኝ እርምጃ …የካድሬና የክልል(ባንዳ) ተላላኪ ጣራ በድንጋይ ደበደቡ ነው። ቢያንስ ድሃ ተቀጠሮ የሚሰራበትን አቃጥሎ ዓመድ ከመታቀፍ፡ በሕገወጥ የሚዘዋወር የሙሰኛና ልዩ ተጠቃሚ ንብረትን ወርሰው ለድሃ አከፋፈሉ የሚለው እጅጉን ይመረጣል!።
የሁለት ታዛዦች ወግ….
*የአማሮች ርዕሰ መስተዳደር አቶ ገዱ አንድአርጋቸው በወሎ ከፍለ ሀገር ወልዲያ ከተማ “የተፈፀመው ጥፋት ነው” “ከሕዝብ ጋር ተወያይተናል፣ ችግሮችን በየደረጃው እንፈታለን” የጭፍጨፋው ምክንያት ባሻገር ሕዝብ በርካታ ችግር እንዳለበት፣ እሱም በየደረጃው መፈታት እንደሚገባው ገልፀዋል።”
* የሰሜን ወሎ ዞን ፖሊስ መምሪያ ኃላፊ ኮማንደር አማረ ጎሹ “ያጠፋነው አጥፊዎችን ነው፣ አሁንም እናጠፋቸዋለን” “ጦር እየተጨመረልን ነው፣ አሁንም እንገድላቸዋለን” አይነት መግለጫ ይሰጣል። የችግሩ ምንጭ የፖለቲካ አላማ ያላቸው አካላት ናቸው። መፍትሄው “መደምሰስ” ነው።
*******************
“ወልዲያ ውስጥ የተፈጠረው የከተማዪቱን ማኅበራዊ ስብጥርና ግንኙነቶች የማያንፀባርቅ አሣዛኝ ሁኔታ መሆኑን በሰሞኑ ግርግር የንግድ ተቋማቸውና መኖሪያ ቤታቸው ሙሉ በሙሉ እንደወደሙባቸው በጓደኛቸው ልጅ ሞት ያዘኑት “ከእኔ ንብረት የሰው ሕይወት ይበለጣል” የኃይላይ ሕንፃ ባለቤት አቶ ኃይላይ ንጉሴ።
__________________________________________
”ተገዳይ ወንድሜ ገብረመስቀል ጌታቸው እንዳይተርፍ ነው ፭ ጊዜ በጥይት የመቱት” ሲል በምሬት ይናገራል። ኪዳኔ ዕለቱን ሲያስታውስ ”ግርግር እንደተነሳ ደጋግሜ ስልክ ደወልኩለት አያነሳም። ብጠብቀውም መልሶ አይደውልም። በጣም ስለተጨነኩኝ ወደ ሆስፒታል ልፈልገው ሄድኩኝ፡ አንገቱ ላይ፣ ደረቱ ላይ፣ ሆዱ ላይ እና ብልቱ ላይ አምስት ጊዜ በጥይት የተመታ እና በደም የተሸፈነውን የወንድሜን አስከሬን ሆስፒታል ውስጥ አገኘሁ”ኪዳኔ ጌታቸው
—————————————————
“የኢትዮጵያ ሕዝብ እና ሕዝቦች ሆይ(!?) በወልድያ እና በቆቦ ለተፈጸመው እልቂት ተጠያቂው እኔ የምመራው ብአዴን ነው” ብሎ አረፈው።”ገዱ አንድ አድርጋቸው
** በመጀመሪያ መታሰር ያለበት የሰሜን ወሎ ዞን ፖሊስ መምሪያ ኃላፊ ኮማንደር አማረ ጎሹ ነው::
(፩) የወጣቱን ነባር ችግሮች እያወቀ ለክልሉ መስተዳድር ጉዳዩን አቀርቦ አልፈታም።
(፪) ደንገተኛና አነስተኛ የችግር አፈታት እና ማረጋጋት ብቃት የለውም።
(፫)ችግሮችን በማባባስ ወጣቱ እንዲበረግግ መሳሪያ የታጠቀ ወታደር አሰማርቷል።
(፬) ልዩ ኅይል በማያስፈልግበት ሁኔታ የፌደራል ጦር ጠርቶ ሰው እንዲሞት ፈቅዷል።
(፭)ሕዝቡ ችግር አልነበረም እያለ የሰው ሕይወት እንዲቀጠፍ መመሪያ ሰጥቷል።
(፮) ለዘመናት የሚከበር ዓመታዊ የጥምቀት ክብረበዓል በውጭ ሀገራት በተሽከርካሪ ሞተር የፖሊስ አጃቢ የሚፈቀድለትን ታቦት አዋርዶ በአስለቃሽ ጭስ እንዲረከስ፡አድርጓል።
(፯) ከሙሰኛ፡ አድርባይ፡ አወርቶአደር፡ ጓዶቹ ጋር በመመሳጠር የሌሎችን መብትና ልዩ ጥቅም ለማስከበር፡የተመደበበትን ሥራ የቆመለትን የአማራ ሕዝብ ማንነትና ክብር አስደፍሯል፡ የአማራን ደም በከንቱ እንዲፈስ አስደርጓል። ይቀጣል! ይወገዳል!
ስለዚህ አንድአርጋቸው ይህንን አርሞ ካልተገኘ ‘በትናቸው’ ነው ማለት ይቻላል።አራት ነጥብ።