![](https://www.goolgule.com/wp-content/uploads/2016/01/14-Copy.jpg)
“ጥምቀትን በጎንደር መታደም መባረክ ነው” ይህ የብዙሃኑ የእምነቱ ተከታዮች የምስክርነት ቃል ነው፡፡ ጥምቀትና ጎንደር የገጠሙ እለት እንኳንስ ለጎብኝዎች ለነዋሪዎችም ታይተው አይጠገቡም፡፡ የጎንደር ጥምቀት በዓል ከመላ ኢትዮጵያ አከባበር የሚለይባቸው በሁለት ተያያዥ ምክንያቶች ይመስለኛል፡፡ ከቀድመው የመሳፍንት እና የአፄዉ ስርዓት ጋር በተያያዘ ከተማዋ ለረዥም ዓመታት መናገሻ ከተማ ሆና መቆየቷ፣ በጊዜው የነበረው ኃይማኖታዊ መንግስት በመሆኑ አብዛኛው ነዋሪ ጥብቅ የኦርቶዶክስ ክርስትና ኃይማኖት ተከታይ ከመሆኑ ጋር በተያያዘ ከሌላው አካባቢ (ከተማ) በተለየ መልኩ “የአርባ አራቱ ታቦታት” መገኛ መሆኗ የመጀመሪያው ምክንያት ሲሆን፤ ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ በአስራ ሰባተኛው መቶ ክፍለ ዘመን አጋማሽ ከአፄ ፋሲል ቤተመንግሥት ምስረታ በኋላ ከቤተ መንግሥቱ በስተ ምዕራብ በኩል አራት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በ18 ሺህ ካሬ ሜትር ምድረ ግቢ ውስጥ በግሩም የስነ ሕንፃ ውበት ለጥምቀተ ባህር መዋኛና ታቦታት ማደሪ ተብሎ በአፄ ፋሲል የተሰራው የፋሲለደስ መዋኛ መገኘቱና ለበዓሉ ድምቀት የጎላ ተፅዕኖ ማሳደሩ የጎንደርን የጥምቀት በዓል የተለየ ያደረገው ይመስላል፡፡ የፋሲለደስ መዋኛ ስፋት 50 ሜትር በ30 ሜትር ሲሆን፣ ጥልቀቱ ደግሞ 2.5 ሜትር ይሆናል፡፡ እንደዚህ አይነት ስፋት ያለው መዋኛ ገንዳ በዛ ዘመን መገንባቱ በራሱ ድንቅ ነው፡፡
በዓሉን በከተማዋ ለማሳለፍ ብዛት ያላቸው የአገር ውስጥና የባህር ማዶ ጎብኝዎች በበዓለ ጥምቀቱ ላይ መታደማቸው ከላይ ከተጠቀሱት ምክንያቶች በተጨማሪነት የጎንደርን ጥምቀት ከሌላው አካባቢ አከባበር የተለየ ያደርገዋል፡፡ በእናቱም የጥምቀት በዓል የአደባባይ በዓል በመሆኑ ጎንደሬዎች ለአደባባይ በዓል የተመቹ ናቸው፡፡ ለዚህም ይመስላል የሰሞን ልጅ በረከት ፋታ ከሚነሳው የፓርቲው የሴራ ፓለቲካ ለአፍታም ቢሆን ተነጥሎ በዓለ ጥምቀትን በየዓመቱ በጎንደር የሚያልፈው፤ ምናልባት የማርክሰን ንድፈ ሀሳቦች ማነብነብ ከመጀመሩ በፊት በልጅነቱ ያየው የነበረው የጥምቀት በዓል ትዕይንት ውል እያለበት ይሆናል በዓሉን በጎንደር የሚያሳልፈው፡፡ በዓሉ ላይ ማንነቱን ፈልጎ ባያገኘው እንኳ የልጅነት ትወስታውን የሚያጣው አይመስልም፡፡ የበረከት ማንነት በአብዮታዊ ዴሞክራሲ ጉድጓድ ላይመለስ የተቀበረ ቢሆንም የልጅነቱ ትውስታው ግን ጨለጨል በሆነ እይታ ጥምቀትን አስታኮ የሚያየው ይመስላል፡፡
በነገራችን ላይ በጎንደር አካባቢ ሁሌም ቢሆን ሦስት ነገሮች በጉጉት ይጠበቃሉ፡፡ በዓል ጥምቀት፣ የሰሊጥ ምርትና ዶላር፡፡ ሦስቱም ነገሮች ለጎንደርና አካባቢው ነዋሪዎች የነፍስም የስጋም እርካታን የሚያጎናፅፍ በረከቶች ናቸው፡፡ በጣም የታደለው የክርስትና ኃይማኖት ተከታይ ሦስቱም ነገሮች ይኖሩታል፡፡ በከፊል የታደለው ደግሞ ከሦስቱ ሁለቱን አያጣም፡፡ በጣምም ሆነ በከፊል ከታደከሉት መሀል የሌለበት የክርስትና ኃይማኖት ተከታይ “ጥምቀት” የተባለ የአደባባይ በዓል ይኖረዋል፡፡
ግማሽ ደርዘን የሚሆን የቤተሰቦቿ አባላት ሰሜን አሜሪካ አለያም እስራኤል ውስጥ የሚኖሩ ተጧሪ ልጃገረድም ሆነች በአስር ሺህ ሄክታር መሬት ላይ በየምርት ዘመኑ የሰሊጥ ምርት የሚያመርተው የናጠጠ ሃብታም አባወራ …. ቤሳ ቤስቲን ከሌለው መናጢ ደሃ ጋር እኩል እየተጋፉ የሚያከብሩት የአደባባይ በዓል ጥምቀት ብቻ ይመስለኛል፡፡የመስቀል በዓል የአደባባይ በዓል ቢሆንም ጎንደርና አካባቢው ላይ የጥምቀትን ያህል የሚደምቅ አይደለም፡፡ ኃይማኖት ያዛመዳቸው አማኞች ከከተራ በዓል እስከ ጥምቀት ባህር መልስ (የሚካኤል ንግስ) ድረስ ታቦቱን አጅበው ይጓዛሉ፡፡ በያሬዳዊ ዜማም አምላካቸውን ያመሰግናሉ፡፡ በዓለ ጥምቀትን አስታከው የሚመጡ ለዘብተኛን ኢ-አማኞች ደግሞ ልጃገረዶችን አጅበው ይተማሉ፡፡ ስለ ልጃገረዶቹ ጡትና ዳሌ ስጋዊ ዜማ ያሰማሉ፡፡ ከሁለቱም የሌሉበት በሺዎች የሚቆጠሩ የባህር ማዶ ጎብኝዎች ደግሞ ትዕይንቱን እየተከታተሉ በካሜራና በብርሃን አሰናስለው ይቀርፃሉ፡፡ በግል ማስታወሻቸውም ይከትባሉ፡፡
ኃይማኖት ያዛመዳቸው አማኞች በቡድንና በተናጠል ጧፍ፣ ዘቢብና መሰል ስጦታዎችን በታቦቱ ፊት ሲጥሉ፣ የነርሱ ተቃራኒዎች ደግሞ በልጃገረዶች ደረት ላይ ሎሚ መወርወር ይቀናቸዋል፡፡ በአጭሩ ጥምቀት ለኃይማኖቱ ተከታዮች ከኃጢያታቸው የሚነፁበትና አምላካቸውን የሚያመሰግኑበት ኃይማኖታዊ በዓል፣ ለለዘብተኞችና ኢ-አማኞች ደግሞ መልካም የስሪያ አጋጣሚ፣ ለባህር ማዶ ጎብኝዎች ታይቶ የማይጠገብ ልዩ ባህለ- ኃይማኖታዊ የትዕይንት መድረክ ነው፡፡
የጎንደርን ጥምቀት በልዩ ድምቀት ከሚያከብሩ የፊት መስመር ተሰላፊዎች ውስጥ የሚመደቡት ያለም አጫዋቾች (አዝማሪዎች) ሲሆኑ፣ የበዓሉ ቀን እግዚሃርን የሚያመሰግኑ ዘለሰኛ ግጥሞችን ቢጫወቱም የማታ ማታ የማህበራዊ ሞገድ ሰለባ ናቸውና እግዚሃርን ባመሰገኑበት መሰንቆ ስለ ሽንጥና ዳሌ ሲገጥሙ ሌሊቱን ያጋምሳሉ፡፡ ቀን ለነፍስ፣ ማታ ለስጋ ይሉሃል ይሄ ነው፡፡
ያም ሆነ ይህ፣ ጥምቀትን አስመልክቶም ሆነ አላስመልክቶ ወደ ጎንደር የምትዘልቁ የአገር ውስጥም ሆነ የባህር ማዶ ጎብኝዎች የጎንደር አዝማሪ ቤቶችን እንድትጎበኙ ይመክራል፡፡ አልያማ ስለ ከተማዋ ሙሉ ምስል ልታገኙ አትችሉም፡፡ ነዋሪዋም ቢሆን ጭፍራ ነፍሱ ነው፡፡ ዘመነኛ የሸገር ልጃገረዶች ሁለት አይነት ሆቢ አላቸው፡፡ ሳልሳ ዳንስ መደነስና ሾፒንግ፡፡ የጎንደር ልጃገረዶችም “ድስቃና ዋንጫ ልቅለቃ” የተባሉ የባህላዊ ውዝዋዜ ሆቢዎች አሏቸው፡፡ ይብዛም ይነስም የሸገር ልጃገረዶች ሆቢያቸውን የሚፈጽሙት የወንድ ልጅ ኪስ በማጠብ ነው፡፡ የጎንደር ልጃገረዶች ስለ ሆቢያቸዉ ላብን እንጂ ኪስ አያራግፉም፡፡ ‹ላቤን ጠብ አድርጌ እጨፍራለሁ› የሚል ጎረምሳ ወደ ጎንደር ጥምቀት ይዝለቅ፡፡ ከአንዷ ልጃገረድ ጋር ዋንጫ ልቅለቃውን ይሞክረ፣ እርሱ ባይሆንለት እንኳ ድሰቃው አለለት፡፡ ድሰቃን ሞክሮ ያልተሳካለት የጥምቀት ጎረምሳ ከቶ ያለ አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም ለድሰቃ ላብህን እንጅ ኪስህን ማራገፍ አይጠበቅብህም፡፡
ከልጅነት እስከ አስተውሎት ዘመኔ ድረስ ስታዘበው የኖርኩት ባህለ – ኃይማኖታዊ ክዋኔዎችን በወግ መሰል ትርክት ቁንፅል በሆነ መልኩ ለመግለጽ ሞከርኩ እንጂ፣ የጎንደር ጥምቀት በዓል አከባበር ትልቅ ጥራዝ ሊወጣው የሚችል የአደባባይ በዓል ነው፡፡ ለሁሉም ለመንፈሳዊያኑ መልካም በዓል፣ ለስጋዊያን ደግሞ መልካም የዋንጫ ልቅለቃና የድሰቃ ጊዜ ይሁንላችሁ፡፡ በነገራችን ላይ “ዋንጫ ልቅለቃና ደሰቃ” የባህል ጭፈራ ዓይነት መጠሪያዎች ብቻ ሳይሆኑ የዘመኑን መንፈስ የሚገልጡ የውስጠ ወይራ አንጓዎች ናቸው፡፡ አሁን ማን ይሙት ከጥቂት ለነፍሳቸው ካደሩ ገዳማዊያን መነኮሳት ውጭ ጥምቀትን ዋንጫ ሳይዝና ሳይለቀልቅ የሚያሳልፍ “ኃይማኖተኛ” ቀርቶ የኃይማኖት መሪ አለ?! ድሰቃን በዋዛ የሚያሳልፉትስ ስንቶች ናቸው?! የሎሚ ውርወራው ተከታይ ድሰቃ መሆኑ ከማን የተሰወረ ነው?! … ግን የእየሱስ ክርስቶስ የጥምቀት በዓል ላይ በ”መተጫጨት” ስም የስሪያ መድረክ ማዘጋጀት ተገቢነት አለው? ኃይማኖታዊ ይዘቱንስ አያጎፈድዉም? … ለዚህና መሰል ጥያቄዎች የኃይማኖት ሊሂቃኑ ምላሽ እስኪሰጡን ድረስ የቻልን በአርምሞ ያልቻልን ግን በዋንጫ ልቅለቃና ድሰቃ በዓሉን እናሳልፍ፡፡ (ፎቶዎቹን የላኩልን ጸሃፊው ናቸው)
“ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡
Leave a Reply